Thursday 26 December 2013

ለኢትዮጵያ ሰማያዊ ፓርቲ ምስክርነት

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም
ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

ሰማያዊ ፓርቲን እንደፖለቲካ ድርጅት/ፓርቲ ለምን እንደምደግፈው፣


እ.ኤ.አ ዴሴምበር 15/2013 ከዋሽንግተን ዲሲ ወጣ ብላ በምትገኘው አርሊንግተን ከተማ የስብሰባ አዳራሽ በተዘጋጀው የሰማያዊ ፓርቲ የመጀመሪያ ስብሰባ ላይ ተገኝቼ  ንግግር እስካደረግሁባት ዕለት ድረስ በበርካታ ጥያቄዎች እወጠር ነበር፡፡ አንደኛው ተደጋግሞ የሚጠየቀው ጥያቄ ለበርካታ ዓመታት ገለልተኛ ሆኘ እና ከማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ወይም ቡድን ጋር ሳልወግን ከቆየሁ በኋላ በአሁኑ ጊዜ ለሰማያዊ ፓርቲ ለምን ያልተቋረጠ ድጋፍ በመስጠት ላይ እንደምገኝ በሚቀርብ ጥያቄ ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡


በኢትዮቱብ ድረገጽ/ethiotube.com በሰጠሁት ቃለ ምልልስ በግልጽ እንዳስቀመጥኩት ለሰማያዊ ፓርቲ ቀጣይነት ያለው ድጋፍ የምሰጥበት ዋና ምክንያት የኢትዮጵያ ትኩስ ወጣት ኃይል የሀገሩን መጻኢ ዕድል የመወሰን እና በሰላማዊ የትግል ሂደት በመሳተፍ ለውጥ ለማምጣት ዝግጁ ነው የሚል ሙሉ እምነት ያለኝ በመሆኑ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ከኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ ከ35 ዓመት የዕድሜ ክልል በታች የሚገኘው የህብረተሰብ ክፍል 70 በመቶ ይሸፍናል፡፡ እንዲሁም በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ውስጥ በአብዛኛው የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ ሰለባ ሆኖ የሚገኘው ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ አብዛኛው የወጣት ህብረተሰብ ክፍል የኢትዮጵያ የማጎሪያ እስር ቤቶች የፖለቲካ ጭቆና እና ማስፈራራት፣ ከህግ አግባብ ውጭ በዘፈቀደ በቁጥጥር ስር የመዋል እና እስራት፣ የስቃይ፣ የመብት እረገጣ እና ከህግ አግባብ ውጭ የእስር ቤት አያያዝ ሰለባ ዒላማ ሆኖ ይገኛል፡፡ አብዛኞቹ የኢትዮጵያ ወጣቶች ስር በሰደደ የስራ አጥነት ወጥመድ ተጠፍረው እና ጥራት ያለው የትምህርት ዕድል እና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት መብታቸውን ተነፍገው በሀገራቸው ላይ የበይ ተመልካች ሆነው ይገኛሉ፡፡ እዚህ ላይ የእኔን “አስረጅ” ምሰክርነት ለማስመዝገብ እንዲሁም ለሰማያዊ ፓርቲ ‘ምስክርነት’ ለመስጠት ያህል  በማያወላውል መልኩ የኢትዮጵያ ወጣቶች የቆሸሸውን የጎሳ ፖለቲካ፣ አስፈሪውን የኃይማኖት ጥላቻ  እና በውሸት ድር እና ማግ የተደወረውን የቅጥፈት ተምኔታዊ ፖለቲካ በጣጥሰው በመጣል “ፍቅር የነገሰበት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ” የሚባል አንጸባራቂ ከተማ ከተራራው አናት ላይ እንደሚገነቡ ያለኝን የማይታጠፍ እምነት ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡ ይህ የተቀደሰ ተግባር የዛሬው ወጣት ትውልድ ቋሚ ታሪካዊ ዕጣ ፈንታ ነው የሚል ጽኑ እምነት አለኝ፡፡


የእኔ “አስረጅ” ሆኖ መቅረብ የእራሴን ሀሳብ እና አስተያየት ከመግለጽ ባለፈ በምንም ዓይነት መልኩ የሰማያዊ ፓርቲን፣ የአመራሩን ወይም የአባላቱን ያለፈውን፣ የአሁኑን እና የወደፊቱን ድርጅታዊ እና ድርጅታዊ ያልሆነ አቋም አይወክልም፡፡ በሰማያዊ ፓርቲ ላይ ምንም ዓይነት ሚና የለኝም፡፡ ያለኝ ብቸኛ ሚና ቢኖር “የሰማያዊ ፓርቲ ቁጥር 1 አድናቂ” መሆኔን በኩራት መግለጼ ብቻ ነው፡፡ እዚህ ላይ የእኔ ለሰማያዊ ፓርቲ ‘በአስረጅነት’ በጽናት መቆም ቅንድቦችን ከፍ ሊያደርግ ይችላል፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ጠንካራ ደጋፊ በመሆኔ ከአንዳንድ ወገኖች ህብረተሰቡን በእድሜ እየለያየ የሚል ትችት ሲሰነዘር ሰምቻለሁ፡፡ እኔ በእድሜ በመከፋፈል መረጃ የመስጠት ጨዋታ ተጫወትኩ እንጅ በስልጣን ላይ ያለው ገዥው አካል እንደሚያደርገው ሁሉ በዘር ወገኔን በመከፋፈል የቁማር ጨዋታ አልተጫወትኩም፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ወጣቱ ኃይል ብይን እንዲሰጥበት በአክብሮት እጠይቃለሁ፡፡ ጆርጅ ኦርዌል እንዳሉት ‘ዓለም አቀፋዊ ማጭበርበር ተንሰራፍቶ በሚገኝበት በዚህ ዘመን ስለእውነት መናገር አብዮታዊ ድርጊት ነው‘፡፡ በአሁኑ ጊዜ የፖለቲካ አጭበርባሪነት፣ የሞራል ዝቅጠት እና አታላይነት ተንሰራፍቶ በሚገኝበት ሁኔታ እኔ ስለሰማያዊ ፓርቲ እየሰጠሁት ያለው ‘አስረጅነት’ እንደ ‘አብዮታዊ ድርጊት’ ይቆጠራል የሚል ዘርፈ ብዙ አመለካከት አለኝ፡፡


የሰማያዊ ፓርቲ ቁጥር: 1ኛ  አድናቂ ለምን ሆንኩ?


በመጀመሪያ ደረጃ ሰማያዊ ፓርቲን የምደግፍበት ምክንያት ከወጣቶች፣ በወጣቶች፣ ለወጣቶች፣ የተቋቋመ የፖለቲካ ፓርቲ ስለሆነ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የአብዛኛውን የኢትዮጵያን ህብረተሰብ ፍላጎት እና ጥቅም ሊወክል የሚችል ፓርቲ ስለሆነ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ከኢትዮጵያ ህዝብ ከ35 ዓመት የዕድሜ ክልል በታች ያለው የህብረተሰብ ክፍል 70 በመቶውን ይሸፍናል የሚለውን ሀቅ ላሰምርበት እፈልጋለሁ፡፡ (የሚቀርበውን መረጃ ታሳቢ በማድረግ በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ አማካይ የህይወት እድሜ ከ49 – 59 ዓመት ነው፡፡)


የኢትዮጵያ የአቦሸማኔው ትውልድ (ወጣቱ ትውልድ) ብዙሀኑን የኢትዮጵያ ህዝብ ለመወከል የሚያስችል የራሱን የፖለቲካ ፓርቲ ማቋቋም ይፈልጋል፡፡ የአቦሸማኔው ትውልድ ለራሱ/ሷ መናገር፣ ለራሱ/ሷ መቆም፣ ለሴቶች፣ ለወንዶች መቆምን ይፈልጋሉ፡፡ የእራሳቸውን እና የአገራቸውን ዕጣ ፈንታ ሊወስኑ የሚችሉት እራሳቸው ወጣቶቹ ብቻ ናቸው፡፡


የጉማሬዎቹ ትውልድ (የእኔ ትውልድ) የፖለቲካ ፓርቲዎች በጉማሬዎቹ፣ ለጉማሬዎቹ የተቀመሩ እና በእነርሱ የአስተሳሰብ ንፍቀ ክበብ ውስጥ የታጠሩ ፍልስፍናዎች ስለሆኑ ከእረፍትየለሾቹ የኢትዮጵያ አቦሸማኔዎች (የወጣቱ ትውልድ) ህልሞች፣ ውስጣዊ ፍላጎቶች፣ ዓላማዎች እና የጋሉ ስሜቶች የስምምነት እምነቶች ንፍቀ ክበብ ውጭ ናቸው፡፡ እኛ የኢትዮጵያ የጉማሬዎች ትውልድ (የእኔ ትውልድ) የአቦሸማኔዎችን ትውልድ (የወጣቱን ትውልድ) ፍልስፍናአና አስተያየት አንረዳውም፡፡ ይህም በመሆኑ ብዙዎቻችን በጎሳ እና በክልል (“ባንቱስታን” ወይም “ክልላዊ”) የፖለቲካ ጭቃ፣ በሚያጣብቅ የጎሰኝነት ዝቃጭ ቆሻሻ፣ እና በታሪካዊ ምክንያተቢስ ጥላቻ  ውስጥ ለበርካታ ዓመታት ተዘፍቀን ስንዋኝ የቆዬን ስለሆነ ለስኬታማነት የማንበቃ የተሽመደመድን የህበረተሰብ ክፍል ነን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የኢትዮጵያ የአቦሸማኔ ትውልዶች (የወጣቶች ትውልድ) የጥንቱ ወይም የኋላቀር ፋሽን የጎሳ ማንነት ፖለቲካ እስረኛ መሆን አይፈልጉም፣ እንዲሁም ከጥንት ጊዜ ጀምሮ ከእራሳቸው ጋር በጥብቅ ተቆራኝቶ በታሰረ የታሪክ ክስተት መንገድ ላይ ለመራመድ አይፈልጉም፡፡ እንዲሁም ነጻነታቸውን በማወጅ እና የእራሳቸውን ዕጣ ፈንታ ለመምረጥ በመወሰን የእራሳቸው የሆነቸውን ኢትዮጵያ መፍጠር ይፈልጋሉ፡፡


“የኢትዮጵያ የጉማሬ ቡድን” ታማኝ አባል እንዳለመሆኔ መጠን የኢትዮጵያ የአቦሸማኔ ትውልድ ከኢትዮጵያ የጉማሬ ትውልድ በጣም ልዩነት አለው የሚለውን እውነታ ለመቀበል እቸገራለሁ፡፡ ለእኔ እና ለእኔው የጉማሬ ትውልድ የዱላ ቅብብሎሹን ለአቦሸማኔው ትውልድ በማቀበል ከጎን ሆነን የአቦሸማኔውን ትውልድ በትህትና የምናግዝበት የመጨረሻው ጊዜ እየደረሰ መሆኑን ለመቀበል እቸገራለሁ፡፡ ለዚህም ነው እራሴን ከጉማሬ ትውልድ ወደ “አቦ -ጉማሬ” ትውልድ ያሸጋገርኩት፡፡ ይህንን ሽግግር “የአቦ – ጉማሬ ትውልድ መነሳሳት” በሚለው ትችቴ ላይ መዝግቤ ማስቀመጤ የሚታወስ ነው፡፡


በሁለተኛ ደረጃ የወደፊቱ የኢትዮጵያ ወጣት ዕጣ ፈንታ በጥልቅ ያሳስበኛል፡፡ ከጥቂት ዓመታት በፊት ለማስታወስ እንደሞከርኩት ሁሉ “ደስታ የራቀው እና በመጥፎ ሁኔታ ላይ የሚገኘው የኢትዮጵያ ወጣት በጊዜ ቀመር ተሞልቶ ለመፈንዳት በመጠባበቅ ላይ የሚገኝ የሰው ቦምብ የመሁኑን ሀቅ ያመለክታል፡፡ የወጣቱ ተስፋ መቁረጥ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ደስታ እየራቀው መሄድ፣ በቅዠት ህይወት ውስጥ መኖር እና ለብዙ ጊዜ በሚቆይ የኢኮኖሚ ቀውስ በመደቆስ ጥንካሬን ማጣት፣ የኢኮኖሚ ዕድሎችን እና ተጠቃሚነትን ያለማግኘት እና የፖለቲካ ጭቆና በገፍ ተንሰራፍቶ መገኘት ሊፋቅ የማይችል አስተማማኝ መረጃ ነው፡፡ ወጣቱ ለነጻነት ያለው ጥልቅ ፍላጎት እና የለውጥ ፈላጊነት ስሜት በእራሱ ማረጋገጫ ነው፡፡ እዚህ ላይ ሊነሳ የሚችለው ብቸኛ ጥያቄ የሀገሪቱ ወጣቶች ለውጥን ሊያመጡ የሚችሉት እየጨመረ በመጣው ወይም በሌላ በሰላማዊ የለውጥ አማራጮች…የሚለው ነው፡፡” ሰማያዊ ፓርቲ ተስፋ ያጣውን የወጣት ኃይል ወደ ሰላማዊ ሽግግር በማምጣት በኢትዮጵያ ውስጥ ወሳኝ ሚና ይጫወታል የሚል እምነት አለኝ፡፡


ሦስተኛ በወጣት ኃይል አድራጊ እና ፈጣሪነት ላይ በሙሉ ልቤ እተማመናለሁ፡፡ የወጣት ሀሳብ እና ጥልቅ የለውጥ ፈላጊነት ስሜት ልብን፣ አዕምሮን እና ሀገርን የመለወጥ ኃይል አለው፡፡ የወጣት ኃይል በዓለም ላይ ከሚገኙ ጠብመንጃዎች፣ ታንኮች እና የጦር አውሮፕላኖች በላይ የበለጠ ኃይል አለው፡፡ የአሜሪካ የሲቪል መብቶች እንቅስቃሴ የተካሄደው በወጣቶች ኃይል በተከፈለ የጉልበት መስዕዋትነት አማካይነት ነው፡፡ አብዛኞቹ በአመራር ቦታ ላይ የነበሩት እና የመብት ተሟጋቾች ወጣቶቹ የህብረተሰብ ክፍሎች ነበሩ፡፡ ዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ በቢርሚንግሀም አላባማ የተካሄደውን የሲቪል መብቶች ሰላማዊ እንቅስቃሴ ሲመሩ የ26 ዓመት ወጣት ነበሩ፡፡ በዚያን ጊዜ ጆን ሌዊስ የ23 ዓመት ወጣት የነበሩ ሲሆን 24 ጊዚያት ታስረዋል፣ እንዲሁም ድርጊቱን ሊያስታውሱት በማይችሉት መልኩ በብዙ አጋጣሚዎች ሰውነታቸው ድቅቅ እስከሚል ድረስ ተደብድበዋል፡፡ እ.ኤ.አ በሜይ 6/1963 በበርሚንግሃም ከ2000 በላይ የሚሆኑ አፍሪካ አሜሪካውያን የሁለተኛ፣ የመለስተኛ ሁለተኛ እና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ተማሪዎች የዘር መድልኦን በመቃወም ሰልፍ በመውጣታቸው ብቻ ለአሰቃቂው እስር ተዳርገዋል፡፡


ወጣት አሜሪካውያን በቬትናም ላይ በእብሪት በመነሳሳት የተካሄደውን ጦርነት እንዲቆም አድርገዋል፡፡ በካሊፎርኒያ የዩኒቨርስቲ የተጀመረው የመናገር ነጻነት እንቅስቃሴ በአሜሪካ የመናገር ነጻነትን እና የዩኒቨርስቲ አካዳሚ ነጻነትን አጎናጽፏል፡፡ ያለወጣቱ ድምጽ መስጠት ባራክ አቦማ ለፕሬዚዳንትነት መመረጥ አይችሉም ነበር፡፡ ኮሚኒስታዊ ገዥዎችን እና በቅርቡም በሰሜን አፍሪካ እና በመካከለኛው ምስራቅ አገሮች ለመለወጥ አስቸጋሪ ናቸው ተብለው ይታሰቡ የነበሩትን ርህራሄየለሽ አምባገነኖች በሰላማዊ ትግል አንኮታኩቶ በመጣሉ እረገድ ወጣቱ ኃይል ወሳኝ የሆነ ሚና ተጫውቷል፡፡


በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ በስልጣን ወንበር ላይ ተፈናጥጠው የሚገኙት ገዥዎች የንጉሳዊውን አገዛዝ እና አምባገነናዊውን የወታደራዊ መንግስት በትጥቅ ትግል ለማንበርከክ ሲፋለሙ የነበሩ ወጣት “አብዮተኞች” ነበሩ፡፡ በእርጅና የእድሜ ጊዚያቸው ግን ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ከኢትዮጵያ ምድር ለማስወገድ ሲፋለሙት የነበረውን ጭራቅ ሆነው ተቀምጠዋል፡፡ ከዚህ አንጻር በኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ህብረተሰብ ለመመስረት ለበርካታ ዘመናት መስዕዋትነትን በመክፈል የእራሳቸውን ድርሻ በመወጣት ላይ ባሉት የኢትዮጵያ ወጣቶች ኃይል ላይ ሙሉ እምነት አለኝ፡፡ እ.ኤ.አ በ2005 አሁን በስልጣን ላይ ያለው የኢትዮጵያ ገዥ አካል ታጣቂዎች እንደ አበደ ውሻ በአዲስ አበባ መንገዶች ላይ በመክለፍለፍ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችን በጥይት ጨፍጭፈዋል ገድለዋል፣ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩትን ደግሞ ለእስራት ዳርገዋል፡፡ (በዚያን ጊዜ በሰው ልጅ ህይወት ላይ በጣም አስደንጋጭ እና አስፈሪ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ ወንጀል በማየቴ በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ተሟጋችነት አንደቀላቀል ተገድጃለሁ፡፡) በአሁኑ ጊዜም እንኳ የኢትዮጵያ ወጣቶች ለዴሞክራሲ፣ ለህግ ልዕልና፣ ለነጻነት እና ለሰብአዊ መብት ጥበቃ ሲባል የደም፣ የላብ እና የእንባ መስዕዋትነት በመክፈል ላይ ይገኛሉ፡፡ የኢትዮጵያ ምርጡ እና ብሩህ አዕምሮ ያለው ወጣት እየተቀጣ፣ ፍርደገምድል ፍርድ እየተበየነበት፣ እየታሰረ፣ እና ጸጥ እረጭ ብሎ እንዲገዛ እየተደረገ ነው፡፡ ከእነዚህ የወጣት ዝርዝር የመጀመሪያው እረድፍ ላይ የሚገኙት ብርቱካን ሚደቅሳ፣ እስክንድር ነጋ፣ አንዷለም አራጌ፣ ርዕዮት ዓለሙ፣ በቀለ ገርባ፣ አቡበካር አህመድ፣ ውብሸት ታዬ፣ ኦልባና ሌሊሳ፣ አህመዲን ጀቤል፣ አህመድ ሙስጣፋ፣ ተመስገን ደሳለኝ፣ በቅርቡ ከህይወት የተለየው የኔሰው ገብሬ እና ሌሎች ለቁጥር የሚያታክቱ ትንታግ የኢትዮጵያ ወጣቶች ናቸው፡፡


በመጨረሻ ሆኖም ግን አስተዋጽኦው ቀላል ካልሆነው ከሰማያዊ ፓርቲ ፕሮግራም ጋር ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በደንብ አስቦበት እና የሀገሪቱን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመቅረፍ የሚያስችል ተግባራዊ ፕሮግራም ነድፎ የሚንቀሳቀስ ፓርቲ ነው፡፡ ከእኔ ልዩ አተያይ እና ስጋት አንጻር በፍትሀዊ አስተዳደር፣ በሰብአዊ መብቶች እና በህግ የበላይነት አተገባበር ላይ ትኩረት በማድረግ የፓርቲውን ፕሮግራም ስገመግመው በጠንካራ መሰረት ላይ የተዋቀረ ልዩ ፓርቲ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ ፓርቲው ሙሉ በሙሉ ነጻ የሆነ እንዲሁም ከፖለቲካ ተጽዕኖ እና ጣልቃገብነት ፍጹም ነጻ የሆነ እና ብቃት ያለው የፍትህ ስርዓት በሀገሪቱ እንዲመሰረት ድጋፍ ያደርጋል፡፡ ዳኞች ሲያጠፉ መከሰስ ያለባቸው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ በሙያቸው በቋሚነት ጡረታ እስከሚወጡበት ጊዜ ድረስ ተቀጥረው እንዲሰሩ ያደርጋል፡፡ ፓርቲው ህገመንግስታዊ ፍርድ ቤት ከነሙሉ ስልጣኑ ጋር እንዲቋቋም ድጋፍ ያደርጋል፡፡ ኢትዮጵያ ፈርማ ባጸደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ውሎች እና ስምምነቶች ለመገዛት እና ለተግባራዊነታቸውም ዕውን መሆን ፓርቲው ጠንክሮ እንደሚሰራ ቃል ገብቷል፡፡ የግለሰብ መብቶችን ጥበቃ የመናገር እና የእምነት ነጻነቶችን ጨምሮ ተግባራዊ እንደሚያደርግ ፓርቲው ቃል ገብቷል፡፡ መንግስት እና ኃይማኖት በግልጽ መለያየት እንዳለባቸው ፓርቲው በጽኑ ያምናል፡፡ ፓርቲው ማንኛውንም በብዙሀን መገናኛ ዘዴዎች ላይ የሚደረግን ቅድመ ምርመራ አጥብቆ ይቃወማል፣ እንዲሁም ከህግ አግባብ ውጭ የሲቪክ ማህበረሰብ ድርጅቶች እና ማህበራት እንዳይዘጉ ያደርጋል፡፡ የሀገሪቱ የጦር እና የደህንነት ኃይል ታማኝነቱ ለሀገሪቱ ህገመንግስት መሆን እንዳለበት እና በምንም ዓይነት መልኩ ለፖለቲካ ፓርቲ፣ ለጎሳ ቡድን፣ ለክልል ወይም ለሌላ አካል ታማኝ መሆን እንደሌለበት ፓርቲው በፕሮግራሙ ላይ አጽንኦ በመስጠት አስፍሮታል፡፡ የፓርቲው የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካ፣ የማህበራዊ እና የባህል ጉዳዮችም እንደዚሁ በተመሳሳይ መልኩ ትኩረትን በጣም የሚስቡ ናቸው፡፡


ሰማያዊ ፓርቲን  እንደ  ንቅናቄ እና የኢትዮጵያ የአቦሸማኔዎች (ወጣቶች) ትውልድን እውነተኛ ድምጽ ለምን እንደምደግፍ፣


እንደ እራሴ ሀሳብ ሰማያዊ ፓርቲ እንደማንኛውም ተወዳድሮ ስልጣን በመያዝ ወደ ስልጣን ቢሮ ከሚገባ  የፖለቲካ ድርጅት የበለጠ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ እንደፖለቲካ ድርጅት እራሱን ቢያዘጋጅ እና በተለመደው መልክ ምርጫ ቢያሸንፍ እና የፓርላማ ወንበር ቢይዝ ምንም አዲስ የማገኘው ነገር የለም፡፡ ከ80 በላይ “የተመዘገቡ ፓርቲዎች” ባሉባት ሀገር (በጣም አብዛኞቹ ለይስሙላ የተቋቋሙ የጎሳ የፖለቲካ ፓርቲዎች) እና ገዥው “ፓርቲ” በ99.6 በመቶ በሚያሸንፍበት ሁኔታ ከግማሽ ነጥብ በመቶ ያነሰ ድምጽ ለማግኘት እንደሰማያዊ ፓርቲ ሁሉ ሌላ ፓርቲ ተመዝግቦ ለዚህች በጣም በጣም ትንሽ ለሆነችው ድምጽ ለመወዳደር የመሞከሩን አስፈላጊነት ትርጉምየለሽ ያደርገዋል፡፡ ለዚህም ነው ሰማያዊ ፓርቲን በኢትዮጵያ ከወጣቶች፣ ለወጣቶች፣ በወጣቶች የተቋቋመ የወጣቶች ንቅናቄ ነው የሚል እምነት ያለኝ፡፡


“የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄን” የኢትዮጵያ ወጣቶች ለእራሳቸው እና ለወደፊቱ ትውልድ የሚተላለፍ ህልማቸውን እና ሀሳቦቻቸውን የሚተገብር ድርጅታዊ ተቋም አድርጌ እወስወደዋለሁ፡፡ እንደ ንቅናቄ ሰማያዊ ፓርቲ በብዙ የአቅም ደረጃዎች ላይ በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡ የኢትዮጵያን ወጣቶች ስለብዙው የሀገራቸው ታሪክ፣ ልማዶች እና ባህሎች እንዲያውቁ የሚያደርግ “የትምህርት” ተቋም ነው፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች የማትከፋፈል የአንዲት ኢትዮጵያ፣ ኃያል ወራሪውን የአውሮፓ ኃይል አሸንፋ እና አሳፍራ የመለሰች የኩሩ አርበኞች ዘር የትውልድ ሀረግ መሆናቸውን ያስተምራል፡፡ እንደ አሁኑ ሳይሆን በአንድ ወቅት ኢትዮጵያ በዓለም እና በአፍሪካ ለሚኖሩ ጥቁር ህዝቦች የኩራት ፈርጥ ነበረች፡፡ የአሁኑ የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ የቀደመውን ኩራታችንን እንደገና መልሶ ለኢትዮጵያውያን ህዝቦች የማጎናጸፍ ዓላማን ሰንቆ ተነስቷል፡፡


“የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄን” ዋና ዋና ዕሴቶች እጋራለሁ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ገዥዎችን እና ኢፍትሀዊነትን በሰላማዊ የትግል ስልት መንገዶች የማስወገድ እምነት አለው፡፡ በዓለም ላይ በየትኛውም ቦታ ገዥዎችን እና ኢፍትሀዊነትን በሰላማዊ የትግል ስልቶች በመጠቀም ለማስወገድ እሰብካለሁ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በኢትዮጵያ ወጣቶች የሽግግር ኃይል ላይ እምነት አለው፡፡ ባለፉት ሰባት ዓመታት በኢትዮጵያ “እና በአፍሪካ” ላይ ወጣቶች የጻፍኳቸውን የሰኞ ዕለታዊ ትችቶች በሙሉ መልክ በማስያዝ በጥራዝ ቢዘጋጁ የኢትዮጵያ ወጣቶችን የሽግግር ኃይል በተጨባጭ የሚያመላክት ማስረጃ ይሆናልሉ፡፡ የእኔ መፈክርአሁንም በፊትም ወደፊትም ፣ “የኢትዮጵያ ወጣቶች ተባበሩ፣ በፍጹም እጅ እንዳትሰጡ፣ ኃይል ለኢትዮጵያ ወጣቶች!” ነው፡፡


የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ አንድ ግብ ብቻ አለው፣ “ፍቅር የነገሰበትን የኢትዮጵያ ማህበረሰብ” መፍጠር፣ ልክ ዶ/ር ማርቲን ሉተር ኪንግ በረዥሙ የትግል ጉዟቸው በአሜሪካ የሰብአዊ እና የሲቪል መብቶችን በማለም “ፍቅር የነገሰበት ማህበረሰብን” ለመመስረት እንዳደረጉት ተጋድሎ ሁሉ፡፡ ዶ/ር ኪንግ እንዲህ ብለው አስተማሩ፣ “የሰላማዊ ትግል ማህበራዊ ለውጥ መጨረሻው ዕርቅ ነው፣ መጨረሻው ኃጢያትን ተናዝዞ ንስሀ መግባት ነው፣ መጨረሻው ፍቅር የነገሰበትን ማህበረሰብ መመስረት ነው፣ እንግዲህ ይህ ዓይነቱ አስተሳሰብ እና ፍቅር ነው በባላንጣነት የሚተያዩትን ወገኖች ወደ ጓደኝነት የሚያመጣው፡፡” “ፍቅር የነገሰበት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ“ ከክልላዊነት (ባንቱስታን) አመድነት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚወጣ እምነቴ የጸና ነው፡፡


“ፍቅር የነገሰበት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ” የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ መሰረቱ አንድነት፣ ሰላም እና ተስፋ ነው፡፡ “ፍቅር የነገሰበት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ” ሰው በመሆኑ ብቻ አንድ ይሆናል፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከከፋፋይ የጎሰኝነት እና ከአፍቅሮ የጎሰኝነት ስሜት ነጻ ይሆናል፡፡ ይህ ዓይነቱ ማህበረሰብ እኩልነት፣ ፍትሀዊነት እና ተጠያቂነት ያለው ህብረተሰብ ለመመስረት ጥረት ያደርጋል፡፡ “ፍቅር የነገሰበት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ“ ከእራሱ እና ከጎረቤቱ ጋር ሰላም ፈጥሮ የሚኖር ህብረተሰብ ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ከጎሳ አለመቻቻል እና ጥላቻ ነጻ የሆነ እንዲሁም ከፍርሃት፣ ጥልቅ ጥላቻ እና ከገዥዎች እና ከጨቋኞች ነጻ የሆነ ማህበረሰብ ይፈጥራል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ደኃ እና ሀብታም፣ ወጣት እና ሽማግሌ፣ ወንድ እና ሴት፣ ክርስቲያን እና ሙስሊም… ለማለም ነጻ፣ ለማሰብ ነጻ፣ ለመናገር፣ ለመስማት እና ለመጻፍ ነጻ፣ ከጣልቃገብነት ነጻ ሆኖ ለማምለክ፣ ለመፍጠር ነጻ፣ ለመስራት ነጻ እና ነጻ ለመሆን ነጻ የሆነ ዓላማ ይዞ ነው የተነሳው፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ ሰላምን በአግባቡ በመጠቀም ጥላቻን፣ የጥላቻ መንፈስን፣ ለመጣላት መቸኮልን፣ ወደ ጓደኝነት፣ መተሳሰብ እና መከባበር በማሻጋገር ለኢትዮጵያ ህዝብ ሰላምን ያመጣል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ንቅናቄው ከመራራ ትችት በውይይት፣ ከመቃረን በስምምነት፣ ከጥላቻ በፍቅር፣ እና ጭካኔን፣ ወንጀለኝነትን እና ታጋሽየለሽነትን ለማሸነፍ የሰው ልጅን ክብር ከፍ የሚያደርጉትን መርሆዎች እንደሚከተል እምነቴ የጸና ነው፡፡ “ፍቅር የነገሰበት የኢትዮጵያ ማህበረሰብ“ “የተስፋ እና የህልሞች መሬት” ነው፡፡ ይህ ማህበረሰብ ወጣቶች ለእኩል ዕድሎች፣ ለእኩል መብት እና ፍትህ እንዲያስቡ የሚያደርግ ነው፡፡ ይህ ማህበረሰብ የኢትዮጵያ ወጣቶች ነጻ ሆነው ተስፋዎቻቸውን እና ህልሞቻቸውን በጋራ መካፈል እንዲችሉ የሚያበቃ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ወጣቶች የማይገታ ተስፋ አንዳላቸው ጽኑ እምነት አለኝ፡፡


ለሰማያዊ ፓርቲ ምን ማድረግ እንዳለብን እንጠይቅ፣


ሁሉም ኢትዮጵዊ በተለይም የእኔ የጉማሬው ትውልድ ከሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ ጎን እንድንቆም  አበረታታለሁ፣ እማጸናለሁም፡፡ አውቃለሁ፣ ብዙዎቻችሁ ቀደም ሲል ድጋፋችሁን ለመስጠት በሞከራችሁበት ጊዜ በተፈጠረው ያልተሳካ የትግል ውጤት ምክንያት ተገቢነት ያላቸው ጥያቄዎች፣ ብዥታዎች፣ እና ጥርጣሬዎች ሊኖሯቹህ እንደሚችሉ እገነዘባለሁ፡፡ “እነዚህ ወጣት እና የአመራር ልምድ የሌላቸው ሰዎች ትክክለኛውን ነገር የሚሰሩ ለመሆናቸው ምን ማስተማመኛ አለን?“ በማለት ተጠይቂያሁ፡፡ እኔም እንዲህ የሚል መልስ ሰጠሁ፣ “ልምድ ያለን እና እምነት የሚጣልብን የጉማሬው ትውልድ አመራሮች የሆንነው ከዚህ ቀደም እንዴት ሰራን?“ አፍሪካ በማያቋርጥ አምባገነናዊ የአገዛዝ መዳፍ ስር ወድቃ ስለምትገኝ የወጣቱን የህብረተሰብ ትኩረት የሚስቡ በርካታ ነገሮች እየተፈጠሩ ነው፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ አመራሮች፣ አባላት እና ደጋፊዎች ስብዕናዎቻቸው ከምን ከምን ነገሮች እንደተዋቀሩ አሳይተውናል፡፡ የተዋቀሩባቸው የመሰረት ድንጋዮች በዝርዝር ሲታዩ የሚከተሉትን ያካትታል፡ ድፍረት፣ የሞራል ጽናት፣ ስነስርዓት፣ ብስለት፣ ጀግንነት፣ ክብር፣ የመንፈስ ጽናት፣ ፈጣሪነት፣ ትህትና፣ ሀሳብ አፍላቂነት እና እራስን ለመስዋዕትነት ማዘጋጀት ናቸው፡፡ ስብዕናዎቻቸውን በማክበር ላለመንበርከክ ሲሉ በቁጥጥር ስር ውለዋል፣ ታስረዋል፣ እንዲሁም ተደብድበዋል፡፡ ሰላማዊ ትግሎቻቸውን አላቋረጡም፡፡ እኛን በማሳመን ሙሉ ድጋፋችንን ከማግኘታቸው በፊት ሌላ ምን ተጨማሪ መስዕዋትነት መክፈል ይኖርባቸዋል? ወጣቶች እና አዲስ ነገር ለማምጣት ጥልቅ ፍላጎት ያላቸው ናቸው፣ በሰላማዊ ትግል ለውጥ ለማምጣት ተገቢው ልምድ ያላቸው ሲሆን ይህንኑ ልምዳቸውን እስከመጨረሻው ይቀጥሉበታል፡፡


አንዳንድ ሰዎች ሰማያዊ ፓርቲ ለገዥው አካል ወይም ለሌላ ድብቅ ዓላማ ላላቸው ኃይሎች ተቀጣሪዎች ላለመሆናቸው ምን ማረጋገጫ አለ በማለት ይጠይቃሉ፡፡ ይህንን ጉዳይ አስመልክቶ የምለው ነገር ቢኖር የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች፣ አባላት እና ደጋፊዎች የገዥው አካል ታማኝ ሎሌዎች ናቸው ብለን የምናስብ ከሆነ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም፣ ፕሮፌሰር ያዕቆብ ኃይለማርያም እና ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያምም ሊጠቀሱ የሚችሉ ታማኝ ሎሌዎች ናቸው ማለት ነው፡፡ ገዥው አካል ብልህ ከሆነ ሰማያዊ ፓርቲ ስለየህግ የበላይነት እና ስለዴሞክራሲያዊ አስተዳደር ያሉትን ፕሮግራሞች በመገናኛ ብዙሀን ለማስተላለፍ እንዲችል መፍቀድ ይኖርበታል፣ ይህን ካደረገ እኔ ለዚህ ደጋፊ ነኝ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ገዥው አካል ሁሉንም የፖለቲካ እስረኞች (በሚስጥር እስር ቤቶች የሚገኙትን ጨምሮ) የሚለቅ ከሆነ፣ ጨቋኝ ህጎችን የሚሰርዝ ከሆነ፣ የሰብአዊ መብት ድፍጠጣዎችን እና ምርጫ ማጭበርበርን የሚያቋም ከሆነ ከመንገድ በመውጣት የመጀመሪያ በመሆን እነሱን በማሞገስ የምዘምር እሆናለሁ፡፡ ጉዳዩ በስልጣን ላይ ስላሉት ሰዎች አይደለም፣ ሆኖም ግን ጉዳዩ በስልጣን ላይ ስላሉት ጭራቃዊ ድርጊት ስለሚፈጽሙት ሰዎች እንጅ፡፡


ባለፉት አስርት ወይም ከዚያ በላይ ዓመታት ተመስርተው በመንቀሳቀስ ላይ የነበሩት እና በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኙት የፖለቲካ ድርጅቶች ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ስኬታማ ሳይሆኑ እንደቀሩ አንዳንድ ሰዎች ይነግሩኛል፡፡ እንዲህ በማለትም ይጠይቁኛል፣ “ሰማያዊ ፓርቲም ስኬታማ ሳይሆን የሚወድቅ ላለመሆኑ ምን ዋስትና አለህ?“ ሰማያዊ ፓርቲ ላለመውደቁ ምንም ዓይነት ዋስትናዎች የሉም፡፡ ስኬታማ ሳይሆን የሚወድቅ ከሆነ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች እና አባላት ጽናት እና እራስን ለስነስርዓት ያለማስገዛት፣ የዓላማ ጽናት እና እራስን መስዕዋት ለማድረግ ያለመቻል ጉድለት ሊሆን አይችልም፡፡ በዋናነት ለውድቀቱ ምክንያት ሊሆን የሚችለው ድጋፍ ያለማግኘት፣ ቅን መንፈስ ያለመኖር፣ በእራስ የመተማመን ጉድለት፣ የለጋሽነት እጥረት እና በአገር ውስጥ ካለው ኢትዮጵያውያን/ት ወገኖች እና ከዲያስፖራው ማህበረሰብ የማቴሪያል እና የሞራል ድጋፍ ለማግኘት ያለመቻል ነው፡፡ ፓርቲው ስኬታማ ባይሆን እና ለውድቀት ቢዳረግ በእብሪትነት ተነሳስተን፣ የሌባ ጣታችንን ወደ ፓርቲው በመቀሰር፣ “ተናግሬ አልነበረም!“ ስንል ሦስቱ ጣቶቻችን ደግሞ ቀስ ብለው ወደ እኛ እያመለከቱ መሆናቸውን መዘንጋት የለብንም፡፡ ኔልሰን ማንዴላ እንዲህ ሲሉ ተማጽነዋል፣ “እኔን በማስመዘግባቸው ስኬቶች አትገምግሙኝ፣ይልቁንም ምን ያህል ጊዜ እንደወደቅሁ እና ከውድቀቶች ተመልሸ እንደተነሳሁ እንጅ” ብለዋል፡፡ ከዚህ አንጻር ሰማያዊ ፓርቲ ወደፊት ምን ያህል ጊዜ አዳልጦት ይወድቃል ብለን ከመገምገም ይልቅ ፓርቲው በእኛ እገዛ እና ድጋፍ ከውድቀቱ እንደገና ለመነሳት ምን ያህል ጊዜ ጥረት ያደርጋል የሚለውን ነው መገምገም የሚኖርብን፡፡


ባለፉት በርካታ ጊዚያት እንደታየው የሚያዋጡት የገንዘብ ድጋፍ አላግባብ ሊባክን ይችላል የሚል ስጋታቸውን አንዳንድ ሰዎች ገልጸውልኛል፡፡ ጠንካራ የሆኑ የተጠያቂነት እና ግልጸኝነት ዋስትናዎችን ማግኘት ይፈልጋሉ፡፡ እንዲህ ብለውም ይጠይቁኛል፣ “ባለፉት ጊዚያት ሌሎች እንዳደረጉት ሁሉ ሰማያዊ ፓርቲም በእርሱ ላይ ያለንን እምነት ላለመሸርሸሩ በምን ሁኔታ ማረጋገጥ እንችላለን?”


በሰሜን አሜሪካ ያለው የሰማያዊ ፓርቲ የድጋፍ ስብስብ በጣም ጠንካራ እና በስነስርዓት የታነጸ የኢትዮጵያ ወጣት ኃይል ስለሆነ ከዚህ ስብስብ ጋር መተዋወቄ እና አብሬም መስራቴ ታላቅ ክብር እና ደስታ ይሰጠኛል፡፡ እነዚህ ወጣት ኢትዮጵያውያን/ት የኢትዮጵያን ወጣቶች ትግል ለመደገፍ ከኪሳቸው በርካታ ገንዘብ በማውጣት በስራ ላይ እንዲውል በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ የሙያ ስብጥራቸውን ስንመለከት ወጣት ፕሮፌሽናሎች፣ በንግድ የሙያ ዘርፍ የተሰማሩ ወንዶች እና ሴቶች እንዲሁም የኢትዮጵያን የጎሳ፣ የጾታ እና የባህል ህብረ ብሄር የሚወክሉ ናቸው፡፡ የተያቂነትን እና ግልጸኝነትን ዋጋ በሚገባ የተገነዘቡ ናቸው፡፡ እርስ በእርሳቸው በመተማመን እና ለእሴቶቻቸው ተገዥ በመሆን ድጋፋቸውን የሚሰጡ ናቸው፡፡ ለወጣቶቹ ዕድሎችን በመስጠት መሞከር እና ለምሰጠው የድጋፍ ገንዘብ ችግር የለብኝም፣ ምክንያቱም ወጣቶቹ የዚህ አይነት ዉርደት ላይ መውደቅ አንደማይሹ ተገንዝበአለሁ፡፡ መርህን በሚያከብሩት የኢትዮጵያ ወጣቶች እና ህዝቦች ታላቅ እምነት አለኝ፣ የኢትዮጵያ ወጣቶች ትክክለኛውን ነገር ይሰራሉ የሚል እምነት የእኔ ዋስትና ነው፡፡


እ.ኤ.አ ዴሴምበር 15/2013  በኣርሊንግቶን ከተማ አዳራሽ ለመጀመሪያ ጊዜ በተጠራው የሰማያዊ ፓርቲ ስብሰባ ላይ በመገኘት ባደረግሁት ንግግር የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ይልቃል ጌትነት እርዳታ ለመሰብሰብ እና ለኑስ አምስት ሳንቲም ልመና ወደ አሜሪካ አልመጣም በማለት ለተሰበሰበው ታዳሚ ተናግሬ ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ከእኛ በሰሜን አሜሪካ ከምንኖር ኢትዮጵያውያን/ት እርዳታ ወይም የገንዘብ ልገሳ አይፈልግም፡፡ ይልቁንም ይልቃል ወደ አሜሪካ የመጣው ገዥው አካል በሰማያዊ ፓርቲ ላይ እያደረሰ ያለውን አስቸጋሪ ሁኔታ፣ የህግ ስርዓት ሂደቱን፣ በአባላቱ ላይ የሚደርሱባቸውን ችግሮች፣ ጨካኝ አምባገነናዊ ስርዓት ባለበት ሁኔታ ፓርቲው ዓላማዎቹን ለማሳካት እንዴት እየሰራ እንዳለ እና የኢትዮጵያ ወጣቶች ነጻ እና ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ትግል ላይ ያሏቸውን ህልሞች እና ተስፋዎች ለእኛ ለወገኖቹ ለማካፈል ነው፡፡


በአሜሪካ ከተሞች ለሰማያዊ ፓርቲ ስብሰባዎች በተያዙ ፕሮግራሞች ሁሉ በመገኘት በኢትዮጵያ በሰላማዊ መንገድ ለውጥ እንዲመጣ ለሚታገሉት ባለራዕይ ወጣቶች ለይልቃል፣ ለሰማያዊ ፓርቲ አባላት እና ለንቅናቄው ድጋፍ ሰጭ ጀግኖች ወጣቶች አቀባበል ማድረግ እንዳለብን ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡ በከተማው የስብሰባ አዳራሽ የሚካሄዱትን ስብሰባዎች ወጣት መሪዎች እንደእነ ይልቃል፣ እስክንድር፣ አንዷለም፣ ርዕዮት እና ሌሎች ብዙዎቹ በግል ያደረጓቸውን የጀግንነት ስራዎች በማወደስ ብቻ የምናልፈው ሳይሆን በአዳራሹ ማክበር ያለብን ሌሎችም ወጣት ጀግኖች በአደባባይ በመንገዶች በመውጣት ተቃውሟቸውን እንዲህ እያሉ ላሰሙት ጭምር ነው፣ “አንለያይም! አንለያይም!“ (እንደተባበርን እንኖራለን!) ወይም ኢትዮጵያ፣ አገራችን! ኢትዮጵያ፣ አገራችን! (ኢትዮጵያ፣ የእኛ አገር!)፡፡ (አንለያይም! አገራችን፣ ኢትዮጵያ! በማለት ወጣቶቹ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ሲጮኹ ስሰማ ሁልጊዜ ይነሽጠኛል፡፡)


የሰማያዊ ፓርቲ መሪ ይልቃል እዚህ በመካከላችን መገኘቱ ለእኔ እ.ኤ.አ በ2005 በተደረገው ምርጫ የተጭበረበረውን ድምጽ በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ ወጥተው በአምባገነኑ መሪ ትዕዛዝ በታጣቂዎች በግፍ ያለቁት ወጣቶች እንዳልሞቱ የሚያደርግ ኩራትን በመፍጠር እለቱን እንድናስታውሰው ያደርገናል፡፡ ይህ ዕለት የህግ የበላይነት ምንም ይሁን ምን መቀጠል እንዳለበት እና ለነጻ እና ለፍትሀዊ ምርጫ ዕውን መሆን በሰላማዊ ትግል ሲፋለሙ ለነበሩት እና በግፍ ለተገደሉት ወጣቶች መታሰቢያ ይሆን ዘንድ የይልቃል በመካከላችን መገኘት ሕያው ምስክር ነው፡፡


ለሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ ምን ማድረግ እንችላለን? የተሸለ ጥያቄ ሊሆን የሚችለው ለወጣት ጀግኖቻችን፣ ሲፋለሙ ህይወታቸውን ላጡት፣ በእስር ቤት በመማቀቅ ላይ ለሚገኙት፣ የግርፋት ስቃይ እየተፈጸመባቸው ላሉት፣ በየዕለቱ ማስፈራራት ለሚፈጸምባቸው፣ ስቃይ እና ውርደት ለሚፈጸምባቸው  ምስጋናችንን፣ ክብር መስጠታችንን እና አድናቆታችንን እንዴት ነው መግለጽ የምንችለው? የሚል ይሆናል፡፡


ሰማያዊ ፓርቲ ማግኘት የሚችለውን ማንኛውንም ድጋፍ ማግኘት ይፈልጋል፡፡ የሞራል ድጋፋችንን ይፈልጋሉ፡፡ የእኛን ማበረታታት ይፈልጋሉ፣ እኛ በእነርሱ ላይ እምነት ያለን መሆኑን ማወቅ ይፈልጋሉ፡፡ ከሁሉም በላይ ወጣቶችን በሙሉ ለመድረስ እንዲችሉ፣ ለትምህርት እና ለግንዛቤ መፍጠሪያ ፕሮግራሞች ማስፈጸሚያ ሊውሉ የሚችሉ ከእኛ የማቴሪያል ድጋፍ ይፈልጋሉ፡፡ ድርጅታዊ ህልውናቸውን ለማጠናከር እና በመላ አገሪቱ ቀጣይነት ባለው መልኩ መንቀሳቀስ እንዲችሉ የእኛን የማቴሪያል ድጋፍ ይፈልጋሉ፡፡ ጠንካራ የህግ መከላከያ ገንዘብ ለማግኘት የእኛን ድጋፍ ይፈልጋሉ፡፡ በአፍሪካ አህጉር አላግባብ በበለጸጉ፣ ሙስናን በሚያራምዱ እና ምህረትየለሽ አምባገነኖች ላይ ትግል ለማድረግ የማቴሪያል ድጋፍ ይፈልጋሉ፡፡


ለሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ የምናደርገው የገንዘብ ድጋፍ በሰላማዊ ትግል ለፍትህ፣ ለእኩልነት፣ ለዴሞክራሲ እና ለሰብአዊ መብቶች መጠበቅ የሚያደርጉትን በቅርብ በመደገፍ ምስጋናቸንን በማቅረብ ከጎናቸው መሆናችንን ለመግለጽ ነው፡፡ ለሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ ያለን ስጦታ ሰላሟ በእራሷ የተጠበቀ ኢትዮጵያን ለማየት ሀብትን ማፍሰስ ነው፡፡ እንሰጣለን፣ እንለግሳለን፣ በዚህም መሰረት ቀጣዩ የኢትዮጵያ ትውልድ በእኛ ስህተት እና ድንቁርና በተፈጠረው ሁኔታ ሳይቸገር በአዲሲቱ ኢትዮጵያ በሰላም ይኖራል፡፡ የእኛን ወጣት ትውልድ መደገፍ የእያንዳንዳችን እና እንደሀገርም የማህበረሰባችን ኃላፊነት ነው፡፡ እኛ ልጆቻችንን፣ ሁሉንም በኢትዮጵያ ያሉ ወጣቶችን ካልረዳን… ማን እንዲረዳ ይፈለጋል?


ሰማያዊ ፓርቲ ለእኛ ምን እንደሚያደርግልን እንጠይቅ፣


እ.ኤ.አ በኦገስት 2012 በአንድ ትችቴ ላይ “የአቦሸማኔው ትውልድ፣ የጉማሬው ትውልድ” በሚል ርዕስ እንዲህ ስል ጠየቅሁ፣ “ኢትዮጵያን ሊጠብቅ ሊያድን የሚችል ማን ነው?“ በሰላማዊ መንገድ በኢትዮጵያ ለውጥ ለማምጣት መከተል ያለብን መንገድ አገራዊ ውይይት ማድረግ እንደሆነ የኢትዮጵን ወጣቶች ተማጽኛለሁ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አቤቱታዬን ለበርካታ ጊዚያት በተደጋጋሚ ሳቀርብ ቆይቻለሁ፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄን በመጀመሪያ በተጠናከረ መልኩ በእራሳቸው በፓርቲው አባላት ላይ በቀጣይም በመላው የኢትዮጵያ ወጣት ማህበረሰብ ላይ የዕርቅ ውይይት ማድረግ እንደሚያስፈልግ ጥሪ አቅርቤ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ የዕርቅ ውይይት በኢትዮጵያ የወጣቱ ህብረተሰብ ውይይት መጀመር ቀጥሎ የሚፈጸም ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡


የኢትዮጵያ የአቦሸማኔ ትውልድ እራሳቸውን ማጠናከር አለባቸው፣ የእራሳቸውን የፖለቲካ እና የማህበራዊ ቦታ መፍጠር አለባቸው፡፡ አገራቸው ከአምባገነንነት ወደ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት በሰላማዊ መንገድ ሽግግር ማድረግ እንድትችል የእራሳቸውን አጀንዳ በመቅረጽ ወጣቶቹ ዘርፈ ብዙ ውይይቶችን መጀመር አለባቸው፡፡ የቋንቋ፣ የኃይማኖት፣ የጎሳ፣ የጾታ፣ የክልል እና ወዘተ ገደብ ሳይኖር ወጣቶች የእራሳቸውን ግንዛቤ ለማሳደግ የዘመቻ እቅድ ማዘጋጀት እና በወጣቱ ማህበረሰብ ዘንድ ንግግሮችን ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ ውይይቶቻቸው ግልጽ በሆኑ መርሆዎች፣ በእውነት፣ በዴሞክራሲያዊ ተግባሮች እና በነጻነት እና በሰብአዊ መብቶች መከበር ላይ የተመሰረቱ መሆን አለባቸው፡፡ ከፍርሃት እና ከጭፍን ጥላቻ ነጻ ሆነው መወያየት አለባቸው፡፡ ሆኖም ግን በመከባበር እና በሰለጠነ መንገድ መከናወን ይኖርበታል፡፡ ከሁሉም በላይ የአቦሸማኔው ትውልድ የውይይት ሂደቱን “የእራሱ” ማድረግ አለበት፡፡ የአቦሸማኔው ትውልድ በሚሰበሰብበት ጊዜ የጉማሬው ትውልድም ይገኛል፣ ነገር ግን በዝምታ  ማዳመጥ ነው ያለባቸው:: ወጣቱን የህብረተሰብ ክፍል በቀላሉ ለማታለል የሚችሉ መሰሪ የጉማሬው ትውልድ አበጋዞች ስለሚኖሩ ምንጊዜም ቢሆን የአቦሸማኔው ትውልድ ነቅቶ ባይነ ቁራኛ ሊጠብቃቸው ይገባል፡፡ በአረብ የለውጥ አመጾች/Arab Spring እንደታየው ሁሉ ወጣቶች በወጥመድ ተይዘው የታዩባቸው ሁኔታዎች ስለነበሩ የኢትዮጵያ ወጣቶችም በወጥመዶች እንዳይጠለፉ ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው፡፡ በመጨረሻም በማታለል የተካኑት የጉማሬው ትውልድ አባላት ወጣቶችን ከጨዋታ ውጭ እንዲሆኑ፣ እንዲጭበረበሩ፣ እንዲደለሉ ያደርጓቸዋል፡፡ መጠንቀቅ ተገቢ ነው::


የዕርቅ ወይይቶች በድንገት እና ተራ በሆነ መልኩ በወጣት የመብት ተሟጋቾች መካከል መጀመር እንዳለባቸው አምናለሁ፡፡ ለምሳሌ እንደዚህ ያሉ ውይይቶች በሚግባቡ እና ተመሳሳይነት አስተሳሰብ ባላቸው የሰብአዊ መብት ተሟጋች ወጣቶች መካከል በመንደር ወይም በጎረቤት ደረጃ መካሄድ ይችላሉ፡፡ ወጣት የሰብአዊ መብት ተሟጋች ወጣቶች አቅማቸውን፣ ያላቸውን እምቅ ኃይል፣ ዕድሎችን እና ችግሮችን ለይተው በማውጣት ዕቅድ ነድፈው ትናንሽ ህብረተሰብ አቀፍ የዕርቅ ውይይቶችን ማካሄድ ይችላሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት ያሉትን ድርጅቶች፣ ተቋሞች፣ ማህበራትን እና መድረኮችን በመጠቀም ወጣት የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች የዕርቅ ውይይቶችን በማካሄድ የወጣቶችን ግንዛቤ ማሳደግ  ይችላሉ፡፡


የዕርቅ ወይይት መነጋገርን ብቻ አይደለም የሚያካትተው ነገር ግን እርስ በእርስ በንቃት መደማመጥን ጭምር እንጅ፡፡ ወጣቶች ከኢትዮጵያ ብሄረሰቦች እርስ በእርስ በመማማር የእራሳቸውን ብዙሀንነት ማጠናከር ይችላሉ፡፡ በተጨማሪም የኢትዮጵያ የአቦሸማኔ ትውልድ ከጉማሬው ትውልድ ስህተቶች እና ከሌሎች አገሮች ወጣቶች ልምዶችም ለመማር ይችላሉ፡፡ የኢትዮጵያ አቦሸመኔ ትውልድ የሚያደርጓቸው የዕርቅ ውይይቶች በመርህ ላይ የተመሰረቱ እንዲሆኑ አጥብቄ እማጸናለሁ፡፡ ወጣቶች ደስተኛ ባልሆኑባቸው ነገሮች ላይ መቃወም መቻል አለባቸው፡፡ በነገሮች ላይ አለመስማማት ማለት የዕድሜ ልክ ጠላት መሆን ማለት አይደለም፡፡ የሰለጠነ ውይይት ማድረግ ለጉማሬው ትውልድ ከባድ ቢሆንም ለአቦሸማኔው ትውልድ ግን በጣም አስፈላጊ ነገር ነው፡፡


ምነው ዝምታ?


“ዓለም አቀፍ ማጭበርበር በተንሰራፋባት ምድር ላይ“ ዝምታ ከቃላት እና ከስዕል የበለጠ ይናገራል፡፡ ማርቲን ሉተር ኪንግ እንዲህ አሉ፣ “በመጨረሻ የምናስታውሰው የጠላቶቻችንን ቃላት አይደለም፣ ነገር ግን የጓደኞቻችንን ዝምታ እንጅ“፡፡ ይህንን ትችት ካጠናቀቅሁ በኋላ “ስለጓደኞቻችን” “ዝምታ” መናገር አለብኝ፣ ምክንያቱም አንዳንድ ጊዜ ዝምታ ከመናገር የበለጠ የመግለጽ ችሎታ አለው፡፡ የኢትዮጵያ ወጣቶች ፓርቲ መሪ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ዋሽንግተን ዲሲ በመጡበት ጊዜ እና እስከ አሁን ድረስ ለበርካታ ዓመታት ታይቶ በማይታወቅ መልኩ እጅግ ብዙ ኢትዮጵያውያን ታዳሚዎች በተገኙበት ስብሰባ ላይ የወጣቶቹ መሪ ንግግር በሚያሰሙበት ጊዜ ትኩረትን በሚስብ መልኩ የአሜሪካ ድምጽ ወኪል ጋዜጠኛ ሳይገኝ ቀርቷል፡፡ የአሜሪካ ድምጽ ድርጊቱን ለመዘገብ አንድም ጋዜጠኛ ሳይልክ ቀርቷል፡፡ የአሜሪካ ድምጽ ዜናውን ለመዘገብ ለምን እንዳልተገኘ የማውቀው ነገር የለም፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ስብሰባ ግን ከተለያዩ የኢትዮጵያ ስፖርቶች፣ ባህላዊ፣ አካዳሚያዊ እና የማህበረሰብ ስብሰባዎች እንዲሁም የመጽሀፍት ርክክብ ፊርማ ስነስርዓት ሲኖር የአሜሪካ ድምጽ በሳምንቱ መጀመራያ እና በሳምንቱ ማጠቃለያ በዋሽንግተን ዙሪያ አካባቢ ሰፊ ሽፋን ሰጥቶ ከሚዘግበው የሚያንስ አለመሆኑን በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ፡፡ ምናልባትም ሰማያዊ ፓርቲ እና የኢትዮጵያ ወጣቶች ለአሜሪካ ድምጽ ምንም ያልሆኑ ቀላል ነገሮች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የአሜሪካ ድምጽ ለወጣቶቹ ግድ ላይኖረው ይችላል፣ የኢትዮጵያ ወጣቶችም ለአሜሪካ ድምጽ ጉዳያቸው አይደለም፡፡


የአሜሪካ ድምጽ እንዲገነዘበው የምፈልገው ነገር ግን በሟቹ በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዝናዊ “ኢትዮጵያ  ላይ ዘር ማጥፋት” ፕሮፓጋንዳ አካሂደዋል የሚል ክስ በይፋ ባስታወቀበት ጊዜና ሌላም ጊዜ ወንጭፋቸውን ሲያነጣጥሩባቸው እና ቀስቶቻቸውን ሲቀስሩባቸው በነበረበት ወቅት ከእነርሱ ጎን ቆሜ ነበር፡፡ በዚያ ውንጀላ ጊዜ የአሜሪካ ድምጽ በጽናት ለመርህ የቆሙ መሆናቸውን፣ ለሙያው ክብር ሰጥተው ይዘግቡ እንደነበር፣ ያለአድልኦ እንደሚሰሩ ጊዜን አክብረው ደግመው እና ደጋግመው እንደሚዘግቡ ሽንጤን ገትሬ ተከራክሪያለሁ፡፡ የአሜሪካ ድምጽ በሰማያዊ ፓርቲ ጉባኤ ላይ በመገኘት እንደ ድሮው ሁሉ በጽናት ለመርህ ቆመው፣ ለሙያው ክብር ሰጥተው እና ያለአድልኦ የጉባኤውን ሂደት እንደሚዘግቡ እጠብቅ ነበር፡፡ ምናልባትም ኢትዮጵያውያን በአሁኑ ጊዜ የአሜሪካ ድምጽ የሚለውን ስያሜ የዝምታ ድምጽ ተብሎ መጠራት ጀመረ ወይ ብለው እየጠየቁ ይሆናል፡፡ የዝምታ ድምጹን ለመስማት እንቀጥላለን፣ ሆኖም ግን በዝምታ አይደለም የምንሰማው፡፡


ከዚህ በኋላ ዝምታ መኖር የለበትም፣ ድምጻችንን ከፍ አድርገን እንጩህ እና ለሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ ድጋፋችንን እናሳይ፣ ዝምታን ከዚህ በኋላ እናቁም፡፡ ለሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ ድጋፋችንን በይፋ እናውጅ፡፡ ቀጥ ብለን እንቁም እና በእነርሱ እንኩራ፡፡ ለሚያካሂዱት ሰላማዊ እና ግጭት አልባ የስርዓት ለውጥ ትግል አድናቆታችንን በመግለጽ ድጋፋችንን እንስጥ፡፡ ወደ ነጻነት የሚወስደው መንገድ የቱንም ያህል ረዥም ጉዞ ቢፈጅ ከእነርሱ ጋር መሆናችንን እናረጋግጥላቸው፡፡ ወጣቶቹ በመጨረሻም ድልአድራጊዎች ይሆናሉ፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ንቅናቄ አባላትን እንደምንወዳቸው በተግባር እናረጋግጥላቸው!


የኢትዮጵያ ወጣቶች ተባበሩ፣ በፍጹም እጅ እንዳትሰጡ፡፡ ኃይል ለኢትዮጵያውያን/ት ወጣቶች!


ታህሳስ 15 ቀን 2006 ዓ.ም

የፌዴሬሽን ምክርቤት በአቶ መላኩ ፈንታ ጉዳይ አስቸኳይ ስብሰባ ጠራ

በአቶ ካሳ ተክለብርሃን የሚመራው የፌዴሬሽን ምክርቤት ፍ/ቤት በሰጠው ትዕዛዝ መሠረት በሙስና ወንጀል በተከሰሱት
የቀድሞ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሰልጣን ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ መላኩ ፈንታ ጉዳይ የመጨረሻ ውሳኔ
ለመስጠት የፊታችን ሰኞ አስቸኳይ ስብሰባ መጥራቱ ታወቀ፡፡

የፌዴራሉ ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሙስና ወንጀል በመጠርጠር በሶስት የተለያዩ መዝገቦች ስር
ከባለስልጣናትና ባለሀብቶች ጋር ክስ የመሰረተባቸው አቶ መላኩ ፈንታ፤ ሚኒስትር በመሆኔ ጉዳዬ መታየት ያለበት
በጠቅላይ ፍርድ ቤት ነው በማለት ባቀረቡት መከራከሪያ መሰረት ችሎቱ ጉዳዩ የሕገ መንግስት ትርጉም ያስፈልገዋል
ሲል ለፌዴሬሽን ም/ቤት የሕገመንግስት አጣሪ ጉባኤ መምራቱና ጉባዔውም በበኩሉ የውሳኔ ሃሳቡን ለፍ/ቤቱ ማሳወቁ
ይታወሳል።

የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ህዳር 11 ቀን 2006 ዓ.ም በዋለው ችሎቱ ላይ የቀድሞው
የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ መላኩ ፈንታ ያነሱትን ክርክር ተከትሎ ብይን
ለመስጠትና ጉዳያቸው መታየት ያለበት በከፍተኛው ፍርድ ቤት ነው ወይስ በጠቅላይ ፍርድ ቤት በሚለው ጉዳይ
ለመወሰን ለታህሳስ 3 ቀን 2006 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል። በዕለቱም የሕገመንግስት አጣሪ ጉባዔ
የውሳኔ ሃሳብ የደረሰው ፍ/ቤቱ የፌዴሬሽን ም/ቤት በጉዳዩ ላይ ውሳኔ ሰጥቶ እንዲያሳውቀው ትዕዛዝ በመስጠት
ለታህሳስ 22 ቀን ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ አይዘነጋም፡፡

ፍርድ ቤቱ የአቶ መላኩ ፈንታን ጉዳይ የሕገ-መንግስት ትርጓሜ ያስፈልገዋል ብሎ በዝርዝር ትንታኔ እንዲታይ
ከማድረጉ በፊት የግራ ቀኙን የተከራካሪ ወገኖች ሀሳብ አድምጦና መዝገቦችንም አገላብጦ ባገኘው መረጃ መሰረት፤
በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ እና በተሻሻለው የፀረ-ሙስና ልዩ የስነ-ሥርዓትና የማስረጃ ሕግ መሰረት፣
ሚኒስትሮችን ጨምሮ የፌዴራል መንግስቱ ባለስልጣናት በስራ ኃላፊነታቸው ምክንያት ተጠያቂ በሚሆኑባቸው ወንጀሎች
በማናቸውም የወንጀል ጉዳዮች የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የመጀመሪያ ደረጃ የስረ-ነገር ክርክር
ማስኬጃ እንዲሆን ስልጣን የተሰጠው መሆኑ በግልፅ ተደንግጓል ብሏል።
ሆኖም የነዚህ ሁለት አዋጆች ንዑሳን አንቀፆች ሕገ-መንግስታዊ ናቸው ወይም አይደሉም የሚለው የተጣራ ትርጉም ያስፈልገዋል በሚል በጉዳዩ ላይ የመጨረሻ እልባት ለመስጠት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት የሕገ-መንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ መምራቱ የሚታወስ ነው፡፡

የፌዴሬሽን ም/ቤት ታህሳስ 21 እና 22 ቀን 2006 ዓ.ም ተሰብስቦ የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ
ወንጀል ችሎት ትእዛዝ በሰጠበት በአቶ መላኩ ፈንታ ጉዳይ ላይ የሕገ-መንግስት አጣሪ ጉባዔ የውሳኔ ሃሳብ ላይ
በመወያየት የመጨረሻ ውሳኔ በማሳለፍ ለፍ/ቤቱ ያሳውቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የፌዴሬሸን ም/ቤት በሕገመንግስቱ መሰረት በፌዴራሉ መንግስት አባል ክልሎች የሚገኙ ብሔር ብሔረሰቦች፣ሕዝቦች
የሚልኩዋቸው አባላት የሚወከሉበት ምክርቤት መሆኑ ይታወቃል፡፡

ኢኮኖሚያችን ሲያድግ የህዝቡ ኑሮ ለምን አሽቆለቆለ?

ማስተዋል ደሳለው

ላለፉት 8 እና ዘጠኝ ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በሁለት አሃዝ አያደገ ነው ሲባል እንሰማለን፤  የእድገት ፍጥነቱ  ላይ የሚነሱ በርካታ ጥያቄውች  ቢኖሩም መንግስት  የመንገድ ግንባታ ፣ የኃይል ማመንጫ ግንባታወችን እና መሰል ነገሮችን  በመጥቀስ እድገት እንዳለ አስረግጦ ይከራከራል::  በሌላ በኩል የኢኮኖሚ እድገቱ ተመዘገበ በሚባልባቸው ዓመታት በዋጋ ንረት የህዝቡ ኑሮ ከጊዜ ወደጊዜ እያሽቆለቆለ  እንደሆነ በግልፅ የሚታይ ነገር ነው:: ታዲያ  የኢኮኖሚ እድገት አለ በተባለባቸው ዓመታት የህዝቡ ኑሮ ለምን አሽቆለቆለ? ይህን ጥያቄ ከ 7 ዓመት በፊት ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ  ተጠይቀው የሰጡት መልስ የዋጋ ንረቱን የኢኮኖሚ እድገቱ እራሱ የፈጠረው ጉዳይ ነው ነገር ግን ቀስ በቀስ እድገቱ ሲቀጥል ራሱ እድገቱ ችግሩን ይፈታዋል ብለው ነበር፤ ነገር ግን ከሰባት ዓመት በዃላም እንኩአን ሊሻሻል  የህዝቡ የኑሮ ሁኔታ ከቀን ወደቀን እየባሰበት ሂዷል::  ችግሩ የተለያዩ  ምንጮች ቢኖሩትም በዋናነት በ 2 ከፍሎ ማየት ይቻላል::
፩. የኢኮኖሚ እድገቱ ምንጭ
፪. የሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ መዋቅር
የኢኮኖሚ እድገት ማለት በአጭሩ ኢኮኖሚዉ ዉስጥ ተጨማሪ ሀብት መፍጠር ማለት ነው::  በመጀምሪያ ላለፉት 8  እና ዘጠኝ ዓመታት ኢትዮጵያ ዉስጥ  የተፈጠሩት ተጨማሪ ሀብቶች ምንድን ናቸው ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል ፤  በአብዛኛዉ ሀገሪቱ ዉስጥ የተፈጠሩት ሀብቶች ከመንገድ ፣ ከሕንፃ እና ከ ከኃይል ማመንጫ ከግንባታ ጋር የተያያዙ ናቸው:: በመቀጠልም የዚህ ሀብት የገንዝብ ምንጭ ምንድን ነው ብሎ ማየት ያስፈልጋል፤ የገንዘቡ ምንጭ በዋናነት ከብድር እና እርዳታ የተገኘ ሀብት ነው ፣ በተለይም በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከ 1998 ዓም ጀምሮ በሶማሊያ በመጀመሪያ የእስላማዊ ፍርድ ቤቶች ህብረት በመቀጠልም የአልሻባብ እንቅስቃሴ መጠናከር ለኢትዮጵያ ትልቅ ሲሳይ ይዞ ነው የመጣው:: በሶማሊያ ያለዉን ሁኔታ  ለመቆጣጠር ምዕራባዉያኑ የሚያደርጉትን ጥረት በመደገፍ  በዋና አጋርነት የተሰለፈችዉ ኢትዮጵያ ላለፉት ስምንት ዓመታት በየዓመቱ በቢልየን ዶላር የሚቆጠር ገንዘብ በእርዳታ መልክ ከምዕራብ ሃገራት እንድታገኝ አድርጓታል:: ይህም ማለት ሀገሪቱ ዉስጥ የጎላ  የኢኮኖሚያዊ መዋቅር ፣ የአሰራር ስርዓት  እና የቴክኖሎጅ ለውጥ ሳይኖር ከፍተኛ ገንዘብ ወደኢኮኖሚው ፈሰስ እንዲሆን አድርጓል:: በሌላ አገላለፅ  የቆየው የሀገሪቱ  ኢኮኖሚ የጎላ የምርት ጭማሪ ሳይኖረው ከዉጭ የተገኘ ብድር እና እርዳታ ኢኮኖሚዉ ዉስጥ ተጨመረ እና የኢኮኖሚዉ መጠን አደገ ማለት ነው::  ስለዚህ የህዝቡን የኑሮ ሁኔታ እና የሀገሪቱን ተወዳዳሪነት ሊያሻሽል የሚችል የግብርና እና የኢንዱስትሪ ዘርፎች ላይ የጎላ  ለዉጥ ሳይታይ ለመሠረት ልማት ኢኮኖሚዉ ዉስጥ ፈሰስ የተደረገው ገንዝብ የገንዘብ አቅርቦትን (Money Supply) በመጨመር እና  የአገልግሎት ዘርፉ ( Service sector) ከሌሎቹ የኢኮኖሚ ዘርፎች ተነጥሎ እንዲለጠጥ እንዲሁም ዋጋ እንዲንር በማድረግ አብዛኛዉን ሕዝብ ለችግር አጋለጠ ::
ከብድር እና እርዳታ የተገኘው ገንዘብ መሰረተ ልማት ላይ ሲዉል ከላይ የተገለፀው ችግር ቢኖርበትም በአንፃሩ የመሰረተ ልማት መስፋፋት የማምረቻ ወጭ ( cost of production) እንዲቀንስ በማድረግ የሚያስገኘው ጥቅም አለ ፤ በተጨማሪም ገንዘብ ገንዘብን ይፈጥራል “ money creats money” በሚለው የኢኮኖምክስ  መርህ መሰረት ኢኮኖሚዉ ዉስጥ የተረጨው ገንዘብ በአብዛኛዉ አገልግሎት ዘርፉ ላይ የፈጠረው ተጨማሪ ሀብት አለ:: ነገር ግን ይህ የተፈጠረ ተጨማሪ ሀብት በጠንካራ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ መዋቅር ስላልተመራ ወደጥቂት ሰወች እጅ እንዲገባ ሁኗል::  ሃብቱ እጃቸው የገባ ሰወችም የኢኮኖሚዉን መዋቅር ሊለዉጡ የሚችሉ እንደኢንዱስትሪ አይነት ዘርፎች ላይ ከመሰማራት ይልቅ ከሙሰኛ ባለስልጣናት ጋር በመመሳጠር ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለዉን የከተማ ቦታ በኢንቨስትመንት እና በሊዝ ስም በመዉሰድ ህንፃ በመገንባት እየተለጠጠ ላለው የአገልግሎት ዘርፍ በማከራየት በአቁአራጭ ከፍተኛ ገቢ ለመሰብሰብ ተጠቀሙበት::
በሌላ በኩል የሀገሪቱ የመሬት አስተዳደር ስርዓት በሙስና የተጨማለቀ እና ወጥ ስላሆነና አዳዲስ ብቅ ለሚሉ ባለሀብቶች መሬት ማግኘት ከባድ ስለሆነ ሀገሪቱ አሁን ባለችበት ተጨባጭ ሁኔታ ወሳኝ ሀብት (strategic resource) የሆነዉን የከተማ ቦታ ቀድመው የያዙ ባለሀብቶች የገቢያ ዉድድሩን ሚዛናዊ እንዳይሆን በማድረግ አዲስ የሚፈጠሩ ተወዳዳሪያቸውን በቀላሉ ከገቢያ ያስወጣሉ:: በተጨማሪም እንደነዚህ አይነቶቹ  ባለሀብቶች በአብዛኛው የፖለቲካዉ እና የግዥዉ ፓርቲ ጥገኛ ስለሆኑ የሚጠበቅባቸዉን ያክል  ግብር እና ታክስ አይከፍሉም:: ሥራቸዉን ስለሚያውቁም በሀገሪቱ በረጅም ጊዜ ሊከሰት ይችላል ብለው የሚፈሩትን ፖለቲካዊ አለመረጋጋት ስለሚሰጉ የሚያገኙትን ትርፍ ወደዉጭ ያሽሻሉ ፤ በጎን ሙሰኛ ባለስልጣናትም የሚዘርፉትን ገንዘብ ከሀገር ያሸሻሉ:: ከዚህ ላይ ፋይናንሽያል ትራንስፓረንሲ ኳሊሽን  ያወጣዉንና ኢትዮጵያ በህገወጥ የገንዘብ ፍሰት (illicit financial flow) በፈረንጆቹ ከ 2000 እስከ 2009 ያጣችዉን 11. 7 ቢልየን ዶላር ልብ ይሏል::
ለማጠቃለል የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ጤናማ ሁኖ እንዲያድግ ከተፈለገ ከላይ የተጠቀሱት  የሀገሪቱ የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ መዋቅር ድክመቶች መስተካከል የሚገባቸዉ ሲሆን ፤ በዉጭ ብድር እና እርዳታ ላይ መንጠልጠሉን ቀንሶ ከሀገር ቤት በፍትሃዊነት ከሚሰበሰብ ግብር ሊሆን ይገባል:: ከዉጭ የሚገኘዉን ሀብትም  በብዛት መሰረተ ልማት ላይ ብቻ ማዋሉ የሚያስከትለዉን ችግር ጥልቅ ጥናት በማካሄድ  መመርመር እና  ገንዘቡ ከመሰረተ ልማቱ ጎን ለጎን የኢንዱስትሪው እና የእርሻዉን ዘርፍ መዋቅር ወደተሻለ ደረጃ እንዲደርስ ለማስቻልም መሰራት አለበት:: ከሁሉም በላይ ግን የኢኮኖሚ ነቀርሳ የሆነዉን ሙስና ለማስወገድ ከአንድ ፓርቲ የበላይነት ወደ መድብለ ፓርቲ ስርዓት መሸጋገር እንዲሁም ተጠያቂነትን ሊያጠናክሩ የሚችሉ እንደገለልተኛ ፍርድ ቤቶች ፣ የግል መገናኛ ብዙሃን  የመሳሰሉትን ተቋማት መፍጠር ያስፈልጋል:: ይህ ካልሆነ ግን ሀገሪቱ ሽህ ጊዜ ብታድግ የኢኮኖሚውን ፍሬ ጥቂቶች እየበሉ የአብዛኛዉ ሕዝብ  ኑሮ ማሽቆልቆሉ ይቀጥላል::

የድብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በግፍ ተባረሩ

ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርስቲና የጤና ነክ ተማሪዎች ለውዝግብ የተዳረጉት በሚሰጠው ድግሪ ሲያሜ እንደሆነ ከቦታው የደረሰን ማስረጃ ያስረዳል፡፡ ከ1ኛ እስከ 4ተኛ ዓመት ያሉ ተማሪዎች ሲመደቡ ዲግሪያቸው የጤና ሳይንስ መኮንን (Public Health Officer) እንደሚባል እንደተነገራቸው ገልፀው ነገር ግን ዩኒቨርሲቲው አሁን የህብረተሰብ ጤና (Public Health) ብቻ የሚል ስያሜ እንደሰጣቸው ተናግረዋል፡፡ ተማሪዎቹ ጉዳዩን በማሳወቅ ማብራሪያ የጠየቁ ሲሆን “‹የህብረተሰብ ጤና አጠባበቅ› የሚለው እናንተን አይመጥንም” እንደተባሉ ገልጸዋል፡፡
Debre_Markos
በመልሱ ያልረኩት የዲፓርትመንቱ ተማሪዎች ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ከህዳር 28 ጀምሮ ደረጃውን ጠብቀው ለሚመለከተው የዩኒቨርስቲው ኃላፊዎችና ለፕሬዚደንቱ ጥያቄ ቢያቀርቡም “ብትማሩ ተማሩ ባትማሩ ግቢውን ለቃችሁ ትወጣላችሁ” የሚል ማስፈራሪያ እንደተሰነዘረባቸው አሳውቀዋል፡፡ ታህሣስ 05 ቀን 2006 ዓ.ም የተሰበሰበው የዩኒቨርስቲው ሴኔት 173 ተማሪዎች ከግቢ እንዲባረሩ ወስኗል፡፡
ከሰኞ ታህሣስ 7 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ መታወቂያቸውን በፖሊስ ተቀምተው ከግቢው እንዲባረሩ የተደረጉት 173 ተማሪዎች በአሁኑ ሰዓት ሜዳ ላይ ተበትነው እንደሚገኙና ለከፍተኛ ችግር እንደተጋለጡ በምሬት ተናግረዋል፡፡
ጉዳዩን ለማረጋገጥ የጤና ዲፓርትመንት ኃላፊ ወደ ሆኑት አቶ ዱቤ ጃራ ስልክ ደውለን የተባለው ነገር መከሰቱን ጠቅሰው ነገር ግን “ውሳኔው በአግባቡ ነው የተላለፈው፤ ይህ ስያሜ ከ1954 ዓ.ም ጀምሮ የነበረ ነው፤ ካሪኩለሙ ላይ ያለው የህብረተሰብ ጤና (Public Health) እንጂ የህብረተሰብ ጤና መኮንን (Public Health Officer) አይደለም” ብለዋል፡፡
አቶ ዱቤ በተደጋጋሚ የዲግሪው ስያሜ “አዲስ የተሰጠ ስያሜ አይደለም” ካሉ በኋላ በተጨማሪም “ተማሪዎቹ ያለ ትምህርት ለ11 ቀናት ግቢ ውስጥ መቀመጣቸው ተገቢ ስላልሆነ ከግቢ እንዲወጡ ተደርጓል” ብለዋል፡፡ በተያያዘ ጉዳይ ከጊቢው የተባረሩ ተማሪዎች ከፍተኛ ችግር ላይ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ስሙ እንዲገለፅ ያልፈቀደ አንድ ተማሪ “መጠለያ፣ ልብስና ምግብ” እጅግ እንደቸገራቸው ገልፆ በተለይ ሴት ተማሪዎቹ መጠለያ እንዲሰጣቸው ለምስራቅ ጎጃም ዞን የሴቶች ጉዳይ ቢያመለክቱም “ዩኒቨርሲቲው ያባረራቸውን ብንረዳ እንጠየቃለን፤ ስለዚህ ልንረዳቸው አንችልም ማለታቸው ታውቋል፡
ፍኖተ ነፃነት ጋዜጣ እንደዘገበው

Monday 23 December 2013

የኢህአዴግ አዲሱ አሰላለፍ ፪ – ከተመስገን ደሳለኝ (ጋዜጠኛ)

በድህረ-መለስ ኢትዮጵያ የፖለቲካው ሥልጣን በስርዓቱ ልሂቃን መካከል ከሚደረገው የኃይል መተናነቅ አንጻር፣ ዛሬም ከመፈራረቅ ጣጣው የተላቀቀ የማይመስልባቸው ምልክቶች መታየታቸው እንደቀጠለ ነው፡፡ ከአራት ወር በፊት በዚህ መፅሄት ላይ ‹‹አዲሱ የኢህአዴግ አሰላለፍ›› በሚል ባቀረብኩት ፅሁፍ በገዥው ፓርቲ ውስጥ ተፈጥሮ ከነበረው ክፍፍል የትኛው ቡድን የበለጠ ጉልበት አግኝቶ በአሸናፊነት መውጣት እንደቻለ ከገለፅኩ በኋላ ፅሁፉን የቋጨሁት እንዲህ በማለት ነበር፡- ‹‹የፓርቲው የታሪክ ድርሳን እንደሚነግረን ‹ይሆናሉ› የተባሉት ተቀልብሰው፣ ባልተጠበቁ ሁነቶች (የኃይል መገለባበጥ ተከስቶ) ፖለቲካው የሚመራበት አጋጣሚ ሊፈጠር የሚችልበት ዕድል ሊኖር እንደሚችልም መዘንጋት አያስፈልግም፡፡››
እነሆ በዚህ ፅሁፍ ደግሞ በቅርቡ በተጨባጭ የታዩትን አዳዲስ ኩነቶች እና ይህንኑ ተከትለው ሊመጡ ይችላሉ ብዬ የምገምታቸውን ‹የቢሆን ዕድሎች› (Scenarios) ለማየት እሞክራለሁ፡፡ 
ሰላም የራቀው-ኢህአዴግ 
በግንባሩ አባል ድርጅቶች መካከል ዛሬም ድረስ ሙሉ በሙሉ የተረጋጋ ፖለቲካ አልሰፈነም፤ የዚህ ዋነኛ ምክንያቱ ደግሞ፣ ቁልፍ የሥልጣን ቦታዎችን ጠቅልሎ ይዞ በነበረው በቀድሞ ሊቀ-መንበሩ ህልፈት ሳቢያ የተፈጠረው የአመራር ክፍተት እና እርሱን ሊተካ የሚችል መሪ ማግኘት ባለመቻሉ ይመስለኛል፡፡ እንዲህ አይነት አጋጣሚዎችም በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ባለ ከሕግ ይልቅ የጠመንጃ ኃይልና የግለሰብ አምባገነናዊነት በገነነበት ሀገር ‹የማይገመቱ ክስተቶች› (Unpredictable Event) ማምጣታቸው የሚጠበቅ ነው፡፡
የሆነው ሆኖ በዚህ አጀንዳ ለመመልከት የምሞክረው ጉዳይ፣ በአሁኑ ጊዜ ሀገር እየመራ ያለው ኃይል ለሁለት የተከፈለ ቢሆንም፣ በአንፃራዊነት በጥምር የሚሰራ መሆኑን በማስረገጥ ነው፡፡ የእነዚህ ሁለት ቡድኖች የጉልበት ምንጭም የታጠቀውን ኃይል በመቆጣጠር እና የፖለቲካውን ሥልጣን በመያዝ ላይ የተመሰረተ ነው፤ ይኸውም ሠራዊቱ እና የደህንነት መስሪያ ቤቱ ሙሉ በሙሉ በህወሓት ሰዎች ሲንቀሳቀሱ፣ ፖለቲካውን ደግሞ የብአዴን መሪዎች፣ ከተወሰኑ የኦህዴድና ደህአዴን የአመራር አባላት ጋር ተባብረው መያዛቸውን የሚያሳዩ ምልክቶች መኖራቸው ነው፡፡
የህወሓት ኃይል
ህወሓት የቀድሞው ፍፁማዊ የበላይነቱን ለመመለስ ዋና ችግር የሆነበት በውስጡ ለተፈጠረው መከፋፈል እስካሁን መፍትሄው ተለይቶ አለመታወቁ ነው፤ ከዚህ ቀደም በዚሁ መፅሄት፣ አንዱ ኃይል የተሻለ ጉልበት በማግኘቱ ሌላኛውን (እነአዜብ መስፍንን ጨምሮ አባይ ወልዱና ቴዎድሮስ ሀጎስን የመሳሰሉ ከፍተኛ ካድሬዎች የተሰባሰቡበትን) በመብለጥ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን እንቅስቃሴያቸውን መገደቡ ተሳክቶለት እንደነበረ ማስነበቤ ይታወሳል፡፡ ይህ ክፍፍል ምንም እንኳ እንደ 1993ቱ ከፓርቲ እስከ ማስወጣት የሚደርስ አለመሆኑ ቢታወቅም፣ ዶ/ር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል እና ጌታቸው አሰፋ የተሰለፉበት ቡድን ተፅእኖ ፈጣሪ ሆኖ መውጣት ችሏል፤ ይህም ሆኖ ውስጥ ውስጡን የሚገመደው ተንኮልም ሆነ ሽኩቻ ገና መቋጫ አለማግኘቱ ግልፅ ነው፡፡
በዚህ ፅሁፍ ጠመንጃ የታጠቀውን ክፍል ‹የህወሓት ኃይል› እያልኩ የምገልፀበት ዓብይ ምክንያት፣ በጄነራል ሳሞራ የኑስ ኤታ ማዦር ሹምነት የሚመራው የመከላከያ ሠራዊት እና በማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ጌታቸው አሰፋ ስር ያለው የደህንነት ኃይል ለሚደግፉት ቡድን መጠናከር እያበረከቱት ያለውን አስተዋፅኦ ከግምት በመክተት ነው፡፡ ሁለቱም ሰዎች ለመለስ ፍፁም ታማኝ የነበሩ ቢሆንም፣ ከህልፈቱ በኋላ እንደእርሱ ተጭኖ ሊቆጣጠራቸው የሚችል ጉልበታም ህወሓትን ጨምሮ በሁሉም የግንባሩ አባል ፓርቲ ውስጥ አለመኖሩ፣ በፖለቲካው ‹ቼዝ› የ‹ዘመነ መሳፍንቱ›ን ሚካኤል ስሁል አይነት ሚና እንዲጫወቱ አስችሏቸዋል፤ ሁለቱም ከስራቸው የነበሩትንና ‹ስልጣን ሊጋፉ ይችላሉ› ብለው የጠረጠሯቸውን ባልደረቦቻቸውን አስቀድሞ ገለል ማድረጉ ከሞላ ጎደል የተሳካላቸው ይመስለኛል፡፡
በተለይም ጌታቸው አሰፋ ከራሱ ወንበር አልፎ ከእነአዜብ መስፍንና አባይ ወልዱ ጋር በመተባበር አንድ ቀን በጠቅላላው የመንግስት የሥልጣን እርከን ላይ ‹ናቡቴ ሊሆን ይችላል› የሚል ስጋት ያሳደረበትን እና ‹መለስ ዜናዊ ሞት ባይቀድመው በእርሱ ቦታ ሊተካው ነበር› እየተባለ የሚነገርለትን የመረጃ ኃላፊ ወልደስላሴ ወልደሚካኤል በሙስና የሚወነጀልበትን መንገድ አመቻችቶ ለእስር ባይዳርገው ኖሮ ‹‹ለቁርስ ያሰቡንን…›› አይነት ታሪክ ራሱን መድገሙ አይቀሬ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡
ጄነራል ሳሞራ የኑስ በበኩሉ ተቀናቃኙ አድርጎ ይመለከታቸው የነበረው ሶስቱ ከፍተኛ መኮንኖች እንደ ወልደስላሴ ‹ፍንቀላ መሳይ ነገር ሊሞክሩ ይችላሉ› ተብለው አይደለም፡፡ የእነርሱ የመጀመሪያው ችግር ከወታደራዊ ዲሲፕሊን በማፈንገጥ አለቃቸውን አለማክበራቸው ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ሳሞራ ‹በየትኛውም ምክንያት ከኃላፊነቴ ብነሳ የቆየ ፋይል አገላብጠው አደጋ ላይ ሊጥሉኝ ይችላሉ› በሚል ስለሚጠረጥራቸው ነው፡፡ እነዚህ መኮንኖች የሰሜን ዕዝ አዛዥ ሌፍተናንት ጄነራል ሰዓረ መኮንን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ መልካም ግንኙነታቸው እንደቀድሞው እንዳልሆነ የሚነገረው የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌፍተናንት ጄነራል አበባው ታደሰ እና የአየር ኃይሉ አዛዥ ሜጀር ጄነራል ሞላ ኃይለማርያም ናቸው፡፡ እናም ሰዓረ እና አበባው በቀጥታ ሠራዊት ከሚያዙበት ቦታ ተነስተው በመከላከያ ሚኒስትር ውስጥ በቢሮ ስራ ላይ ሲመደቡ፣ ሞላም ከነበረበት ኃላፊነት አኳያ ብዙም ይመጥነዋል የማይባል የቢሮ ስራ ተሰጥቶታል፤ በእርሱም ቦታ ሜጀር ጄነራል አደም መሀመድ ተተክቷል፡፡ የሳሞራ እና የሞላ ልዩነት በመለስ ዘመንም በአደባባይ የሚታወቅ እንደነበረ ሰምቻለሁ፡፡
ለጉዳዩ ቅርብ ከሆነ የመረጃ ምንጬ እንዳረጋገጥኩት የአስተዳደር ዘይቤውን በማኪያቬሊያዊ አስተሳሰብ (ከፋፍለህ ግዛ) የሚያሳልጠው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፣ ለሞላ ትዕዛዝ የሚሰጠውም ሆነ ማንኛውንም ጉዳይ በተመለከተ የሚያነጋግረው የዕዝ ተዋረዱን ጠብቆ በኤታ ማዦሩ በኩል ሳይሆን፣ በቀጥታ በመገናኘት መሆኑ፣ አየር ኃይሉን ከመከላከያ ሚኒስቴር የተገነጠለ አስመስሎት ነበር፤ ይህ ሁኔታም በሁለቱ መኮንኖች መካከል ያለው ግንኙነት የሥልጣን ተዋረድን የጠበቀ እንዳይሆን በማሰናከሉ በጄነራሉ ላይ ደፍሮ የማይናገረው ቅሬታ ሊያሳድርበት ችሏል፤ ከመለስ ህልፈት በኋላም ሳሞራ ሂደቱን ለማስተካከል መሞከሩ፣ በየግምገማው ላይ እስከ መዘላለፍ አድርሷቸው ነበር (በነገራችን ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ እንደ ጦር ኃይሎች አዛዥነቱ፣ ከጄነራሎቹ ጋር መደበኛ /Official/ በሆነ መንገድ ትውውቅ አላደረገም፤ እነዚህ ሶስት ጄነራሎችም ለዚህ አይነቱ የአሰራር መፋለስ ጥፋተኛ የሚያደርጉት አለቃቸውን ሳሞራ የኑስን ነው፤ ከምንጮቼ እንደሰማሁት ከሆነም ከወራት በፊት ኃይለማርያም ደሳለኝ በተገኘበት ‹ጎልፍ ክለብ› በሚባለው የጄነራሎቹ መዝናኛ በተዘጋጀ ፕሮግራም ማጠናቀቂያ ላይ ሳሞራ አንድ ጠረጴዛ ከበው ወደ
ተቀመጡት እነዚህ ጄነራሎች ጋ ሄዶ ‹ኑ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ላስተዋውቃችሁ› ማለቱን እና እነርሱም በጥያቄው ተበሳጭተው ቢሮ ያላቸው መሆኑን እና ክብራቸውን በሚመጥን መልኩ መተዋወቅ እንደነበረባቸው በኃይለ ቃል መመለሳቸውን ነው)
የሳሞራ የኑስ እና ሰዓረ መኮንን መነቋቆር ከትግሉ ዘመን ጀምሮ የመጣ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ሆኖም ሳሞራ ከማንም በላይ የሚፎካከረውም ሆነ መበለጥ የማይፈልገው በሟቹ ጄነራል ኃየሎም አርአያ እንደ ነበር የቀድሞ ጓዶቻቸው ያስታውሳሉ፤ ይህ ሁኔታ ዛሬም ድረስ በስራ ላይ ያሉ መኮንኖችን ‹የሳሞራ› ወይም ‹የኃየሎም ተከታይ› በማለት መከፋፈሉ በጓዶቻቸው እና በፓርቲው መሪዎች አካባቢ የሚታወቅ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ለማዕረግ እድገት የተለየ የድጋፍ አስተያየት የሚያገኙት በዛን ዘመን ‹የሳሞራ ተከታይ› የሚባሉት እየተመረጡ እንደነበረ በወሬ ደረጃ ይናፈሳል (በነገራችን ላይ ጄነራል ሳሞራ ከጤንነት ጋር በተያያዘ በአጭር ጊዜ ውስጥ በጡረታ ይሰናበታል በተባለበት ጉዳይ ላይ እያንገራገረ እንደሆነ ከመከላከያ አካባቢ የሚወጡ መረጃዎች ያመላክታሉ፤ እንደ ምክንያት የሚጠቀሰው ደግሞ ‹ለእኔ በጎ አመለካከት የላቸውም› በሚል የሚጠራጠራቸው ጄነራሎች በሥራ ላይ እያሉ የእሱ ጡረታ መውጣት ከመስሪያ ቤቱ ጋር ተያይዘው የሚነሱ ያደሩ የሙስና ካርዶች የሚመዘዙበትን ዕድል ያሰፋዋል የሚል ነው፤ በተለይም በግዙፍ የቢዝነስ ሥራዎች ላይ በታላቅ ተፎካካሪነት እየተሳተፈ የሚገኘው ‹መቴክ› ምንም እንኳ ማረጋገጫዎች ባይቀርቡበትም በመከላከያ ሥር ከነበረበት ዘመን እስከ 2002 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ ከግዥዎች ጋር ተያይዘው የሚነሱ በርካታ የሙስና ሁኔታዎች በመኖራቸው ነው፡፡
መቴክ ካለፉት አራት ዓመታት ጀምሮ በአዋጅ የልማት ድርጅት እንዲሆን ቢደረግም፣ ዛሬም ዳይሬክተሩ የሠራዊቱ አባል ብርጋዴር ጄነራል ክንፈ ሲሆን፣ መከላከያ ደሞዝ የሚከፍላቸው ጥቂት የማይባሉ ሠራተኞችንም እንዳቀፈ ይታወቃል፡፡ እናም ሳሞራ ሃሳቡ ከተሳካለት ለጥቂት ተጨማሪ ዓመታት በሥልጣኑ ላይ ሲቀጥል፣ አሊያም ‹የወንድ በር› ለማግኘት በትግሉ ዘመን የእርሱ ሰልጣኝ እንደነበረ የሚነገርለትን እና በቅርቡ ብቸኛው ከሜጀር ወደ ሌፍተናት ጄነራል ማዕረግ ያደገው ዮሀንስ ገ/መስቀል እንዲተካው መንገድ ጠረጋውን ማመቻቸቱ ትኩረት ሰጥቶ የሚሰራበት ጉዳይ ይመስለኛል)
ይህም ሆኖ የተኮረኮርን ያህል የምንስቀው ጄነራል ሳሞራ የኑስ በቅርቡ ለታተመው ‹‹ህብረ ብሔር›› መፅሄት ሙስና ለሠራዊቱ አደገኛ መሆኑን እንዲህ በማለት መግለፁን ስናነብ ነው፡-
‹‹ሙስና ሠራዊቱን ሊያበላሸው ይችላል፡፡ ሙስና ፀረ-ልማት ነው፤ ሠራዊቱን ሊበትነው እና ሕዝባዊ ባህሪውን እንዲያጠፋ ሊያደርገው ይችላል፤ አንድ ሠራዊት ሠራዊት ነው የሚባለው እንደ ወታደር እንደ አንድ አካል ሲያስብ እንጂ ለግሉ ሲያስብ አይደለም፡፡ …በአጠቃላይ (ሠራዊቱ) በዚህ ነው የሚፈርሰው፡፡›› 
መቼም ጄነራሉ ይህንን የተናገረው እራሱን ጨምሮ በርካታ ከፍተኛ መኮንኖች እንደ እንግሊዝ ንጉሳውያን ቤተሰቦች በተንጣለለ ቪላ ቤት ውስጥ፣ የተቀማጠለ ኑሮ መኖራቸውን ረስቶት አይመስለኝም፤ ‹ይህ የተንዛዛ ወጪያቸውም የሚሸፈነው ከደሞዛቸው በሚያገኙት ገቢ ነው› ብሎ ቧልት መሳይ ክርክር ሊያመጣ አይችልም፡፡ ይሁንና እታች ያለው ጭቁን የኢትዮጵያ ሠራዊት ምንም እንኳ በአለቆቹ ‹ቴክሳስ›ነት ላይ ለመቆጣት ባይደፍርም፣ እንደማንኛውም ዜጋ ለኑሮ ውድነትና አስከፊ ድህነት የተጋለጠ መሆኑን መካድ አይቻልም፡፡
የሆነው ሆኖ ተሰሚነታቸው እየተቀዛቀዘ የመጣው አቦይ ስብሃት ነጋ ከወራት በፊት ለ‹‹ውራይና›› መፅሔት ‹‹ህወሓት ትንሳኤ ያስፈልገዋል›› በማለት የሰጡትን ምክር ተከትሎ፣ ጄነራል ሳሞራ እና አቶ ጌታቸው አሰፋ፣ ከድርጅቱ ምክትል ሊቀ-መንበር ዶ/ር ደብረፅዮን ጋር በመተባበር ህወሓትን ለማጠናከር እና በፖለቲካ ውስጥ የነበረውን የአንበሳውን ድርሻ ለማስከበር (ጉዳዩን ከለጠጥነው ደግሞ ‹ለማስመለስ›) እየሰሩ እንደሆነ ይነገራል (በነገራችን ላይ የሳሞራና ጌታቸው ተፅእኖ መጨመሩን ለመረዳት፣ መከላከያ ‹አገራዊ ጥቅምንና ደህንነትን ለመከላከል› በሚል ‹እጅግ ጥብቅ ሚስጢር ብሎ የሰየማቸውን የሰው ኃይል ፕሮፋይል፣ የሒሳብ መዝገቦችና ሰነዶች እና የክፍያ ማስረጃዎች ለማንም አካል እንዳይገለፅ› የሚያስችለውን ስልጣን፣ ደህንነቱ ደግሞ በስራ ላይ የሚፈፅማቸው ማንኛውም ጉዳዮች ወደፊት በህግ እንዳይጠይቅ እስከ መከላከል የሚደርሰውን አዲስ የተዘጋጁትን አዋጆች ማንበቡ በቂ ነው፡፡ በርግጥ እነዚህ ባለሥልጣናት እንዲህ ባለ ተመሳሳይ መንገድ እንዲጓዙ ያስተሳሰራቸው አንዱ ጉዳይ ‹ህወሓት ተዳከመ፣ ተሸነፈ፣ አበቃለት…› የሚለው የካድሬውና ደጋፊው ቁጭት እንጂ ወትሮም መልካም ግንኙነት ኖሯቸው አይመስለኝም)
ለማንኛውም በጥቅሉ ሲታይ የህወሓት ትልቁ ችግር ተብሎ በአመራር አባላቱ የሚጠቀሰው ‹በዚህ ወቅት ወደፊት መምጣት የሚችሉ ጠንካራ ቴክኖክራቶችን አለማፍራቱ፣ ሁለንተናዊ ድጋፍ የሚያደርግለትን የታጠቀውን ኃይል ተጠቅሞ የፖለቲካ ልዩነቱን ጨፍልቆ በአሸናፊነት ይዞት መውጣት የሚችል መሪ እንዳይኖረው አደረገ› የሚል ነው፡፡ በርካታ የላይኛ እና የታችኛው ካድሬዎችም ‹ለእንዲህ አይነቱ ክፉ ጊዜ ድርጅቱ የሚያስፈልገው፣ በትግሉ ዘመን ልምድ ያካበተ ታጋይ ብቻ ነው› የሚል አቋም እንዳላቸው ይነገራል፡፡ ስርዓቱ ከሚያራምደው ርዕዮተ-ዓለም ጋር ጠንካራ ትውውቅ ያሌለውን እና የትግሉን ዘመን በአሜሪካን ሀገር በማሳለፉ ‹የምዕራባውያን ድጋፍ አለው› ለሚባለው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የሚሰጡት ዝቅተኛ አመለካከት መግፍኤም ይኸው ይመስለኛል፡፡
ለነገሩ እርሱም ቢሆን በጠንካራ ድርጅታዊ ዲሲፕሊን ካለመታነፁ እና መሰል ጉዳዮች ጋር በሚያያዙ ምክንያቶች ለትንፋሽ ጊዜ የማይሰጠውን የድርጅት ሊቀ-መንበርነትንም ሆነ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ የሚወራውን ያህል ይፈልገዋል ብሎ መደምደሙ አስቸጋሪ ነው ብዬ አስባለሁ፤ ከዚህ ይልቅ በተፈጥሮ ከታደለው የተግባቢነት ባህሪው አኳያ እንደ ሕዝብ ግንኙነት የመሳሰለ ብዙም የማያጨናንቅ ሥራን ይመርጣል፡፡ ለዚህም ይመስለኛል ከሰለጠነበት ሙያ ጋር የቀጥታ ተያያዥነት ያለውን የጤና ጥበቃ ሚኒስትር በሚመራበት ዘመን፣ ከውጭ ሀገር በርካታ የተቋረጡ ፈንዶችን እንደገና ለማስለቀቅ መቻሉ እንደ ታላቅ ስኬት የሚወራለት፤ አልፎ ተርፎም ‹ወባን ከኢትዮጵያ ምድር ለማጥፋት ብርቱ ትግል አደረገ› ተብሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሳይቀር እስከ መሸለም የደረሰው እዚህ መስሪያ ቤት እያለ እንደሆነም ይታወቃል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ በፓርቲውም ሆነ በመንግስት አስተዳደር ከህወሓት ሰዎች ትልቁን ስልጣን የያዘው ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል ከምዕራባውያን ጋር የቆየ ቀረቤታ እንዳለው ሰምቻለሁ፤ እንደሚታወሰው ደብረፅዮን ከክፍፍሉ በፊት (የደህንነት መስሪያ ቤቱ እንዲህ እንደ ዛሬው እጅግ ዘመናዊ በሆነው የቻይና ቴክኖሎጂ ሳይጥለቀለቅ) ከነበረው ከፍተኛ የሥልጣን ቦታ ላይ ተነስቶ፣ ቁልቁል ወርዶ በሁመራ በአንድ ዞን እንዲሰራ የተመደበው (ሁላችንም ስንገምት እንደነበረው) የአንጃው አባል ወይም ደጋፊ ሆኖ አይደለም፤ ይልቁንም የእነስዬ-ተወልደ ቡድን በመባል የሚታወቀው (‹አፈንጋጩ› ኃይል) ደብረፅዮንን በሲ.አይ.ኤ እና ሞሳድ ወኪልነት የመክሰሱ ጉዳይ የድርጅቱን በርካታ አባላት ቀልብ በመሳቡ፣ መለስ ይህንን ተከትሎ ከሚመጣበት አደጋ ራሱን ለመከላከል የወሰደው እርምጃ በመሆኑ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት እስከ 1998 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በሁመራና ራያ አካባቢዎች በዞን ደረጃ ለማገልገል ተገዷል፡፡ እናም እርሱን የምዕራቡ ዓለም ፊት-አውራሪ አሜሪካና ሸሪኮቿ ወዳጅ ነው የሚያስብለው በቀድሞ መስሪያ ቤቱ በኩል በነበረው ግንኙነት ይመስለኛል።
የፖለቲካውን መዘውር የጨበጠው ኃይል
የዚህ ቡድን አምበል እንደ ድርጅት ብአዴን ቢሆንም፣ በቋሚ ተሰላፊነት ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ አባዱላ ገመዳ፣ ሙክታር ከድር እና ሬድዋን ሁሴን እንደሚገኙበት ይነገራል፤ ለብአዴን ‹በተሻለ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ ለመገኘቱ መደላድል ፈጥሮለታል› የሚለውን ሙግት ምክንያታዊ የሚያደርገው ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፖሊሲና ጥናት ምርምር አማካሪ በረከት ስምዖን፣ የኢህአዴግን የካድሬ ማሰልጠኛ ማዕከል በዳይሬክተርነት የሚመራው አዲሱ ለገሰ፣ ደርቦ ይዞት የነበረውን የትምህርት ሚኒስትርነት ለሽፈራው ደሳለኝ በመልቀቅ፣ በአሁኑ ወቅት ሙሉ የስራ ጊዜውን በግንባሩ ፅ/ቤት የሚያውለው ም/ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን እና የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈ-ጉባኤው ካሳ ተክለብርሃን የያዙት ሥልጣን ያለውን የፖለቲካ አቅም መመዘኑ ይመስለኛል፡፡ በመከላከያ ሠራዊቱ ውስጥም ከሳሞራ አንድ እርከን ዝቅ ባለ ሥልጣን ከሌሎች ሁለት ጄነራሎች ጋር የሚገኘው አበባው ታደሰ እንደ ቀድሞው በዕዝ አዛዥነቱ (በቀጥታ በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ወታደሮችን ማንቀሳቀስ የሚችልበት) ላይ ቢሆን ኖሮ ጥንካሬውን የተሟላ ማድረጉ አይቀሬ እንደነበረ መገመት ይቻላል፡፡
ከዚህ ሌላ ለእነበረከት ቡድን ተጨማሪ የፖለቲካ ጉልበት እየሆናቸው ያለው የኃይለማርያም ደሳለኝ ቢሮ እና በአባዱላ ገመዳ አፈ-ጉባኤነት የሚመራው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት ነው፡፡ አባዱላ፣ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ሪፖርት ለማቅረብም ሆነ ለመታዘዝ ፍቃደኛ ያልሆኑ አንዳንድ ባለስልጣናት፣ በውስጥ መስመር በሚተላለፍለት ‹ጥቅሻ› በምክር ቤቱ በኩል የሚመለከተው የቋሚ ኮሚቴ አባላት አስጠርቶ የተሰጠውን ኃላፊነት የሚገመግምበት ስልት እየተገበረ ነው፡፡ በአናቱም ምን ጊዜም የሳምንቱን የሥራ መጨረሻ ቀን አርብን ጠብቆ የሚሰበሰበው የሚኒስትሮች ም/ቤትን ከሞላ ጎደል ይህ ቡድን እየጠቀመበት ይመስለኛል፡፡ በርግጥ ሚኒስትሮቹ በሚገናኙበት አብዛኛውን ሰዓት ሳይግባቡ (በጭቅጭቅ) ማሳለፋቸው ይነገራል፤ የዚህ ምክንያቱ ደግሞ በአቶ መለስ ዘመን ም/ቤቱ የሚሰበሰበው የተለያዩ አጀንዳዎችን ለማቅረብ እና በቀረበው አጀንዳ ላይ ለመከራከር (ለመመካከር) ሳይሆን፣ መለስ ወስኖ የመጣበትን የሥራ ድርሻ ተቀብሎ ለመበተንና ሪፖርት ለመስማት የነበረው አሰራር፣ ዛሬ ተቀይሮ በርካታ የተነቃቁ ሚኒስትሮች የየራሳቸው ሃሳብ ተቀባይነት እንዲያገኝ (ለማንፀባረቅ) የሚታገሉበት መድረክ ወደ መሆን በመሸጋገሩ ነው፡፡ ይህም ሁናቴ ዋናውን የመንግስት ሥራ የመገምገም እና የማስፈፀም አቅምን ሳይቀር ከሚኒስትሮች ም/ቤት ወደ ኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ አሻግሮታል የሚያስብሉ ማሳያዎች አሉ፡፡ ይሁንና በዚህስብሰባ ላይም ቢሆን ደፈር ብሎ ከበረከት ስምዖን እና አባይ ፀሀዬ የተሻለ አዳዲስ ሃሳብ የሚያቀርብ ባለሥልጣን እንደሌለ ሰምቻለሁ (በነገራችን ላይ ምክንያቱን ባላውቅም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹የፖሊሲና ጥናት ምርምር አማካሪ› ተደርገው የተሾሙት በረከት ስምዖን፣ አባይ ፀሀዬ፣ ኩማ ደመቅሳ እና ዶ/ር ካሱ ኢላላ የሥራ ቦታቸው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ፅ/ቤት ሳይሆን መገናኛ አካባቢ በሚገኝ አንድ ህንፃ ላይ ነው፡፡ የተሰጣቸው ኃላፊነት ኃይለማርያምን በቅርብ እንዲያገኙ ከማስገደዱ እና በግልፅ ከሚታወቀው የአማካሪ አስፈላጊነት አኳያ ካየነው ግን ግራ የሚያጋባ ይመስለኛል)
ጠቅላይ ሚኒስትሩ…
ኃይለማርያም ደሳለኝ ይህንን ቦታ ከያዘ በኋላ፣ ብዙዎች በስልጣኑ የማዘዝ አቅሙ ላይ አመኔታ እንደሌላቸው (አንጋፋ ታጋዮች እንደ ‹አሻንጉሊት› ሊጠቀሙበት እንደሚችሉ) ደጋግመው መግለፃቸው ይታወሳል፡፡ በግልባጩ ‹አፈንግጦ ለመውጣት መሞከሩ አይቀሬ ነው› የሚሉ ግምቶች ነበሩ፡፡ በርግጥ እነዚህ መላ-ምቶች ዛሬም ድረስ እልባት ባያገኙም፣ እዚህ ጋ ያልጠቀስኳቸው አንዳንድ ጉዳዮች ላይ ያሳያቸው ወጣ ያሉ አቋሞቹን ሳስተውል ግን፣ አሁን ያለው አሰላለፍ (የአነበረከት እና አባዱላ ፖለቲካዊ መጠናከር) ለእርሱም የተረፈው ይመስለኛል፡፡ እንዲሁም ከቤንች ማጂ የተባረሩ አማርኛ ተናጋሪዎችን አስመልክቶ በድርጅቱ ውስጥ ባልተለመደ መልኩ ‹አጥፊዎቹ ላይ እርምጃ እወስዳለሁ› ከማለት አንስቶ (በነገራችን ላይ በአማካሪ ብዛት እንዲከበብ ካደረገው ምክንያት አንዱ ጓዶቹ በዚህ ንግግሩ መበሳጨታቸው ነው) በቅርቡ ህወሓትን ለመሸምገል በተዘጋጀ መድረክ ላይ ‹ሁኔታዎች እንዲህ እየተካረሩ ከሄዱ ወደ ማሰሩ መግባታችን አይቀርም› በማለት ማስፈራራቱ እና በቴዎድሮስ አድህኖም የሶሻል ሚዲያ አጠቃቀም ላይ የመቆጣቱ ጉዳይ ድረስ የሚካተቱ እውነታዎች ሰውየው የራሱን መንገድ ለመከተል እየሞከረ መሆኑን ያሳያሉ ብዬ አስባለሁ፡፡
የሆነው ሆኖ እነዚህ ሁናቴዎች የፖለቲካውን ጉልበት ሙሉ በሙሉ በብአዴንና በተባባሪነት በጠቀስኳቸው የኦህዴድና ደህአዴን የአመራር አባላት አካባቢ ቢያከማቻቸውም፣ በማንኛውም ሰዓት ያሻውን ማድረግ የሚችለው የታጠቀው ኃይል ደግሞ ከህወሓት ጎን እንደተሰለፈ ይገኛል፡፡ መጪውን ጊዜም አዲስ ክስተት እንድንጠብቅ ገፊ ምክንያት ይህ አይነቱ የኃይል አሰላለፍ ይመስለኛል፡፡
ምን እንጠብቅ?
ከረጅሙ የፓርቲ ፖለቲካና መንግስታዊ መንገራገጮች በኋላ፣ የሁለቱንም የኃይል መሰረቶች ጠቅልሎ በመዳፉ ሥር የከተተው መለስ ዜናዊ በሞተ ማግስት ‹የኃይል መገዳደሮች ሊከሰቱ ይችላሉ› የሚለው የብዙዎቹ ግምት ነበር፤ ከወራት በፊት አስነብቤ በነበረው ከላይ በተጠቀሰው ፅሁፍም ግምቶቹ እውን መሆን እንደ ጀመሩ ማሳያዎች ማቅረቤ ይታወሳል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ ራሳቸውን ያቧደኑት ኃይሎች ዋነኛ ግብ ከሥልጣን የሚነሱ ጥቅሞችና አነስተኛ የየራሳቸው ፓርቲ ፍላጎቶች የፈጠሩት በመሆኑ፣ እንደ ሟቹ ደመ-ቀዝቃዛ አምባገነን አይነት በጠንካራ መዳፍ ሥር የሚያሰባስባቸው ባለመገኘቱ በየጊዜው የኃይል መሸጋሸጎች ሊከሰቱ እንዲችሉ አድርጓቸዋል፤ አሁንም እየተስተዋለ ያለው ይኸው እውነታ ነው፡፡ በዚህ አውድ ላይ ቆመን ሊፈጠሩ የሚችሉ የቢሆን ሃሳቦችን ስናስቀምጥም በጠረጴዛው ላይ የምናገኘው ሁለት ዕድሎችን ይመስለኛል፡፡
የመጀመሪያ ሲናሪዮ የሚሆነው ከላይ የጠቀስኩት ቡድንተኝነት እንዳለ ሊቀጥል ይችላል የሚል ነው፤ ይህም የሚሆንበት ምክንያት ባለኝ መረጃዎች መሰረት የፖለቲካውን መስመር የያዘው ቡድን መሪ አባላት፣ አሁን ያላቸውን መንግስታዊ ሥልጣን ጠብቀው መቆየትን መሰረታዊ መሰባሰቢያ አጀንዳ ማድረጋቸው ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የሳሞራና ጌታቸው ጥምረት ህወሓትን ወደ ቀደመው ዘመኑ ለመመለስ ቢሻም፣ ሊሄድበት የሚችልበት መንገድ አደገኛ መሆኑ (ወታደራዊ ላዕላይ መዋቅሩንና የደህንነት ኃይሉን ከመያዙ አኳያ) ሁኔታዎችን ባሉበት ይዞ መቀጠልን በትርፍ-ኪሳራ ስሌት የተሻለ አማራጭ አድርጎ ይወስደዋል ብዬ አስባለሁ፡፡
ሁለተኛው የቢሆን ዕድል፣ ዳግመኛ የኃይል መሸጋሸግ ሊፈጠር መቻሉ ነው፤ ሰዎቹ ጥቅመኛ በመሆናቸው የቋንቋ ተናጋሪነት ልዩነቶቻቸውንና የኋላ የመቆራቆስ ታሪኮቻቸውን ተሻግረው፣ አንዳቸው ከአንዳቸው ጋር ሌላ መልክ ያለው ስብስብ ሊፈጥሩ ይችሉ ይሆናል፤ ይህ አይነቱ አዲስ የኃይል አሰላለፍም፣ ከቀጣዩ ሀገራዊ ምርጫ በፊት በማይታወቀው ተሰዊና ሰዊ ሊጠናቀቅም ይችላል፡፡
በመጨረሻም ምንም ይፈጠር ምን፤ እኛን ሊያግባባን የሚገባው ጭብጥ፣ የትኛውም ቡድን በግንባሩ ውስጥ ቢነሳ፣ የማዕከላዊ መንግስቱን ህልውና ወደሚበታትን ሂደት መግባቱ ሊሰካለት አለመቻሉ ነው፤ ምክንያቱም በዚህ መልኩ ሄዶ የሚጣሉበትን ጠረጴዛ መስበሩ ምን እንደሚያስከትል ያውቁታልና ወደዚህ ምዕራፍ እንደማይሻገሩ አምናለሁ፡፡ ይሁንና ከፓርቲው ዝግነት እና ከፖለቲከኞቹ አቋም የለሽነት አንፃር አሁንም ሆነ በቀጣይ ጊዜያት ከማንም ግምት ውጪ ያሉ ክስተቶች እንደ ደራሽ ውሃ ድንገት ሳይታሰብ ግንባሩን ሊያተራምሱት ይችላሉ ብሎ መገመቱ አግባብ ይመስለኛል፡ ,,,,,,       / ዘሀበሻ/

‹‹እስከ አፍንጫችን ታጥቀናል›› ያሉ የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጡ ተቃዋሚዎች ከ‹‹ዶ/ር ሺፈራው ተክለ ማርያም ጋራ በየዕለቱ እየተገናኘን ነው፤ ማኅበረ ቅዱሳንን አፍርሰን ሕንፃውን እንረከበዋለን›› እያሉ ነው – ‹‹ከእናንተ ጋራ መሣርያችኹ ቢኖርና በመሣርያችኹ ብትመኩም ከእኛ ጋራ ደግሞ እግዚአብሔር አለ፤ አንፈራም፤ ከዚህ በኋላ ለውጡ ወደኋላ አይመለስም፡፡›› /ብፁዕ አቡነ ሉቃስ/

bb
የቤተ ክርስቲያንን ንብረት በመሸጥ የሚታወቁት የ‹ቅሬታ› አቅራቢ ነን ባዮቹ ዋነኛ አስተባባሪ መልአከ ገነት ኃይሌ ኣብርሃ፣ በቅርቡ በ1.3 ሚልዮን ብር በገዙትና ለቻይና ተቋራጭ ባከራዩት ሲኖ ትራክ መኪና ብቻ በወር ብር 70,000 ገቢ ያገኛሉ፤ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አስተዳደራዊ ለውጥ ለማምጣት የተነሡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተንገላቱበት የግንቦት ፳፻፩ ዓ.ም. ጥቃት የተሳተፉትና ሞዴል ፴ በማቃጠል የሚታወሱት ሊቀ ትጉሃን ዘካርያስ ሐዲስ፣ ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ አቀንቃኝ ብሎጎች ጋራ ስልታዊ ግንኙነት መጀመራቸው የሚነገርላቸውና ለአፃዌ ኆኅትነት እንኳ ሳይበቁ በደ/ምሕረት ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እልቅና ለመሾም ‹‹መቶ ሺሕ ብር እከፍላለኹ›› በሚል ልጆቻቸውን ለረኀብ የዳረጉት መልአከ ብሥራት መልአከ አበባው (ብይዱ ይመር)ስ እነማን ናቸው?
* * *
የካህናቱን፣ የሊቃውንቱን፣ የሰንበት ት/ቤቶችንና የምእመናን ተወካዮችን ከ92 – 97 በመቶ ድጋፍ ያረጋገጠው የአ/አ ሀ/ስብከት የአደረጃጀትና አሠራር ለውጥ ጥናታዊ ውይይት ዛሬ ይጠናቀቃል፤ የጥናቱን ትግበራ የሚቆጣጠር በአፈጻጸምም እየተከታተለ የሚያርምና የሚያስተካክል ራሱን የቻለ አካል እንዲቋቋም ተሳታፊዎቹ በአጽንዖት ጠይቀዋል፡፡
‹‹ይህ መዋቅርና አደረጃጀት ስለ መታሰቡ፣ ቅንብር ስለ መደረጉ በቤቱ ስም አመሰግናለሁ፡፡ አባታችን የልማት አርበኛ ናቸው፡፡ በየመንደሩ ያለው አሉባልታ ይህ ነው አይባልም፤ እዚህ ስናየው ግን የተለየ ነው፡፡ የጥናት ዘገባው ቀጥሎ እንድናየው እንጂ ሁከት አያስፈልግም፡፡ ጀርባዬም ፊቴም አንድ ከኾነ በሕግ ለመተዳደር ምን ያስፈራኛል? አስቀድሞ ይህ እንዲህ ይኾናል እያሉ መደንበርስ ምን ያስመለክታል? ወጡም ሊጡም እያሉ ያሉት ጉዳቸው እንዳይጋለጥ ነው ይህ ኹሉ ጭፋሮ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ዶግማና ቀኖና ለመጠበቅ ከፍተኛ ሓላፊነት ያለበት ቅ/ሲኖዶስ ይውጣ ያለውን ሕግ መደገፍ ተገቢ ነው!!›› /የደብር አስተዳዳሪ/
‹‹አንድ ድጓ ከዲግሪ ጋራ ይወዳደራል ካላችኹ መቼ ነው እውን ኾኖ የምናየው? እውን ይኾናል ወይ? አምስት እንትን የምንላቸው ካልኾኑ በቀር ይህን የሚቃወም አይኖርምና ቶሎ ይተግበር፡፡ ብፁዕ አባታችን ከዚህ የበለጠ ምን ይጠበቃል? ይሄ ነገር ቶሎ የማይተገበር ከኾነና ወደ ኋላ የምታዘገዩት ከኾነ የልብ ልብ እንዲያገኙ ታደርጓቸዋላችኹ፤ እናንተም ተጠያቂዎች ትኾናላችኹ፡፡›› /የመምህራን ተወካይ/
‹‹የማይነካው ተነካ፤ የዘመናት ጸሎቴ ነበር፤ ፍጻሜውም ዛሬ ዛሬ. . .ይለኛል፤ እንግዲህ ጸሎተ ስምዖንን ነው የምጸልየው፤ ጌታዬ የቤተ ክርስቲያንን መዳን አሳይተኸኛልና ባሪያኽን አሰናብተኝ እለዋለኹ፡፡›› /የምእመናን ተወካይ/
ተጨማሪ መረጃውን ይከታተሉ

የደቡብ ሱዳን ሁኔታ ዓለምአቀፉን ማኅበረሰብ እያሳሰበ ነው

የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት የፖለቲካ ተቃዋሚያቸው ደጋፊዎች መፈንቅለ-መንግሥት ሞከሩብኝ ባሉ ማግሥትም ዛሬ በዋና ከተማይቱ ጁባ የተኩስ ልውውጡ ቀጥሎ ውሏል፡፡
sudan
የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት የፖለቲካ ተቃዋሚያቸው ደጋፊዎች መፈንቅለ-መንግሥት ሞከሩብኝ ባሉ ማግሥትም ዛሬ በዋና ከተማይቱ ጁባ የተኩስ ልውውጡ ቀጥሎ ውሏል፡፡
በሁከቱ ቢያንስ ሃያ ስድስት ሰው መገደሉንና በሺኾች የሚቆጠሩ ሲቪሎች መፈናቀላቸውን የመንግሥቱ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል፡፡
የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር የሰዓት ዕላፊ ገደብ መደንገጋቸውን ከቢሯቸው በገለፁበት ወቅት፤ ሰኞ፣ ታኅሣስ 7/2006 ዓ.ም
የደቡብ ሱዳን ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር የሰዓት ዕላፊ ገደብ መደንገጋቸውን ከቢሯቸው በገለፁበት ወቅት፤ ሰኞ፣ ታኅሣስ 7/2006 ዓ.ም
የጎረቤቶቿ የሱዳንና የኬንያ መሪዎችም ለሳልቫ ኪር ስልክ እየደወሉ አለኝታነታቸውን ገልፀውላቸዋል፡፡
የሱዳን መንግሥት “ሁኔታውን በቁጥጥር ሥር አውያለሁ” ካለ በኋላ ውጊያው መቀጠሉ ያሳሰባቸው መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ባን ኪ ሙንና የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣናትም ገልፀዋል፡፡
ጎረቤቶቿ ሱዳንና ኬንያም እንዲሁ ሥጋታቸውን እየገለፁ ነው፡፡
ለዝርዝሩ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡

Sunday 22 December 2013

ሻምበል ፍቅረሥላሴ ወግደረስ ጻፉ

ክንፉ አሰፋ
ፀሃይ አሳታሚ ድርጅት በታኅሣሥ 16, 2006 ዓ/ም (Dec. 25, 2013)  የቀድሞ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩትን የሻምበል ፍቅረሥላሴ ወግደረስን ‘እኛና አብዮቱ’ የሚል መጽሃፍ  ለገበያ እንደሚያበቃ አስታወቀ። ሻምበል ፍቅረሥላሴ እንደ ደርግ አባልነታቸው በጋራ ያመኑበትን፣ የተማከሩትን፣ የወሰኑትን፣ የሰሩትን፣ የገጠማቸውንና በቅርብ በዓይን ምስክርነት ያዩትን ተንትነው በ‘እኛና አብዮቱ’ ያስነብቡናል። የራሳቸውን ዕይታ ያካፍሉናል።
New book by Fkreselase Wegderes
ልጅ ሆነን አንድ አባባል እሰማ ነበር።”አበላል እንደ ደርግ አባል። አለባበስ እንደ ፍቅረሥላሴ ወግደረስ!” – የሚል። በተለይ በኔ ትውልድ ያለን ሰዎች፣ ከዚህ ውጭ ስለኝህ ሰው የምናውቀው ብዙም ነገር አልነበረም። ግና እኝህ ሰው በልባቸው መክሊት ለአመታት የቋጠሩትን መረጃ ጀባ ሲሉን፤”… አጻጻፍም እንደ ፍቅረሥላሴ ወግደረስ” የሚያሰኝ ሆኖ አገኘሁት።
ሻምበል ፍቅረሥላሴ ወግደረስ ለአስራ አምስት ዓመታት አብዮቱን ሲመሩ ቆይተው ወደ መጨረሻው ከሥልጣን በጡረታ ስም እንዲሰናበቱ ተደርገዋል። ደርግን በጣለው በወያኔ መንግሥትም ለ፳ ዓመታት ታስረው፣ የሞት ፍርድ የተበየነባቸውና በመጨረሻ ፍርዱ ወደ ዕድሜ ልክ ተዛውሮላቸው ከእሥር ቤት በአመክሮ የወጡ ግለሰብ ናቸው።
ጸሃፊው በድራማ መልክ በመጽሃፋቸው ካሰፈሩዋቸው እውነታዎችና ግለ-ሂሶች ውስጥ አንዳንዶቹን ለአንባቢያን ማካፈሉ አይከፋም።  ደርጎች መፈንቅለ መንግስት አድርገው ሲያበቁ ቀዳማዊ ሃይለስላሴ ዘንድ ቀርበው ከንጉሱ የገጠማቸውን አስገራሚ ምላሽ ሻምበል ፍቅረሥላሴ ወግደረስ  በመጽሃፋቸው እንዲህ ሲሉ አስፍረዋል።
የፖለቲካ እሥረኞች በሙሉ እንዲፊቱ የሚለው ጥያቄ እንደተነበበ ንጉሡ ጣልቃ ገብተው “ለመሆኑየፖለቲካ እሥረኞቹ እነማን ናቸው?” የሚል ጥያቄ አቀረቡ። “በእርግጥ የምናውቃቸው የፖለቲካእሥረኞች ባይኖሩም ማንኛውም የፖለቲካ እሥረኛ እንዲፈታ ነው የምንጠይቀው” አሉ ሻለቃ ተስፋዬገብረኪዳን። ንጉሡ ራሳቸውን ነቅነቅ አድርገው ጽሑፉን የሚያነበውን የደርግ አባል እየተመለከቱአልገባችሁም!” ብለው ዝም አሉ። በእርግጥም አልገባንም። ተማሪዎችና የተለየ ዓላማ የነበራቸውየተማሩ ሰዎች የሰነዘሩትን መፈክር ብቻ ነበር ይዘን ንጉሡ ፊት የቀረብነው። በፖለቲካ እሥረኝነትስም በከፍተኛ ደረጃ ለጣሊያን ወራሪ መንግሥት በባንዳነት አድረው አገራችንን የወጉ፣ ለቅኝተገዥነትም የዳረጉትን እንደ ኃይለሥላሴ ጉግሳ ያሉ ወንጀለኞች የፖለቲካ እሥረኞች ተብለው ከግዞትናከእሥር ቤት አስወጥተን እንደ ጀግና ራሳቸውን እንዲቆጥሩ አደረግናቸው።
የነ ጄነራል ተፈሪ በንቲ ጉዳይን አስመልክቶ የሰፈረው ታሪክ ደግሞ እንዲህ ይነበባል።
“በሊቀመንበርነት ስብሰባውን የሚመሩት ጄነራል ተፈሪ ‘የቋሚ ኮሚቴው’በዛሬው ቀን የሚወያይበትንጉዳይ አስመልክቶ የመቶ አለቃ ዓለማየሁ የደርጉ ዋና ፀሐፊ ይገልጽልናል’ ብለው ስብሰባውመጀመሩን ካበሰሩ በኋላ ዓለማየሁ በአጀንዳው ላይ አጭር ገለጣ ማድረግ ሲጀምር ስልክ ተደወለ።ስልኩ /ኮሎኔል መንግሥቱ አጠገብ ስለነበር ወዲያው ቅጭል እንዳለ መነጋገሪያውን በማንሳት ሃሎአሉ። ከሌላው ጫፍ ማን እንደደወለ አላወቀንም። በኋላ እንደታወቀው /ኮሎኔል ዳንኤል ነበርየደወለው። ምን እንደተነጋገሩ አልተሰማም። /ኮሎኔል መንግሥቱ ብቻ “እሺ እሺ” ብለው ስልኩንዘጉት። ስልኩን እንደዘጉ “ይቅርታ ስልኩ የተደወለው ከጎንደር ነው። ጎንደር ውስጥ ችግር አለ።እናንተ ቀጥሉ” ብለው ከጀርባቸው ባለው በር በኩል ውልቅ አሉ። በዚህን ጊዜ ዓለማየሁና ሞገስጥርጣሬ የገባቸው መሰለ።  ዓለማየሁ ንግግሩን አቋርጦ በመስኮት በኩል ውጭ ውጭዉን መመልከትጀመረ። ዓይኖቹ አላርፍ አሉ። ግራና ቀኝ ይመለከታል። አጠገቡ ያሉትን ሰዎች ሁሉ በጥርጣሬተመለከተ። ሻምበል ሞገስም በር በሩን ይመለከታል። ከአሁን አሁን አንድ ችግር ይከሰታል የሚልፍርሃት ያደረበት ይመስላል። ሁሉም የኢሕአፓ አባላትና ደጋፊዎች ፈርተዋል። እንደፈሩት አልቀረም/ኮሎኔል መንግሥቱ ከወጡ ሁለት ደቂቃ እንኳን አልሞላም ከበስተጀርባ ባለው ኮሪደር የወታደሮችንእርምጃ ሰማን። ወታደሮች ሲንቀሳቀሱ በፊት ለፊታችን ባሉት መስኮቶች በኩል ተመለከትን። በዚህንጊዜ ፍስሐ ደስታ “ተከብበናል” አለ። ወዲያው ሁለቱም በሮች በኃይል ተበረገዱ። ሁላችንም ደነገጥን፣ቀልባችን ተገፈፈ፣ እጢአችንም የወደቀ መሰለን። ድርቅ ብለን በተቀመጥንበት ቀረን።…
ሻምበል ፍቅረሥላሴ ወግደረስ ሰለ ልጅ ሚካኤልን አስተዋይነት ሲያስታውሱ እንዲህ የሚል ግለሂስም ያስነብቡናል።
እኛ በችኮላ ውሳኔ መስጠታችን፣ ሕዝቡን በደንብ አለማወቃችን፣ ሰፊ የሕዝብ አመራር ልምድማጣታችን፣ የአገርና የውጭውን ፖለቲካ ውስብሰባዊ ግንኙነት አለመገንዘባችን፣ የመንግሥትን አሠራርደንብና ሥርዓት አለመረዳታችን፣ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ጥመርታዊ ግንኙነትን መመልከት አለመቻላችን፣የተለያየ ገንቢም ሆነ አፍራሽ ተልዕኮ ያላቸው ኃይሎች ተጽዕኖ እንደሚያሳድሩብ ያለማጤናችን፣በየዋህነትና በቅንነት ብቻ እንደምንሠራ በመገንዘባቸው ሊሆን ይችላል ልጅ ሚካኤል ከእኛ ጋር መቆየትየሚችሉት ለአጭር ጊዜ ብቻ እንደሚሆን የጠቆሙት…
በወቅቱ ስለ ህዝቡ የእርስ በርስ መጨካከንና መወነጃጀል ባሰፈሩት ክፍል ውስጥ እንዲህ የሚል ታሪክ እናገኛለን።
Former Ethiopian Official Fkreselasie Wegderes..የሥራ ዕድገት የተከለከለ፣ በሌብነትም ሆነ በስካር ወይምበሌላ ጥፋት የተቀጣ፣ በግል ጉዳይም ሆነ በመንግሥት ሥራከአለቃው ጋር የተጣላ፣ በአጋጣሚው ተጠቅሞ አዲስ ሹመትወይንም ዕድገት ለማግኘት የሚፈልግ ሁሉ ጠቋሚ፣ ወንጃይ፣ከሳሽ፣ ተበዳይ ነው።
የተወሰነ ጥቅም ለማግኘት ወይም ሌላውን ለመጉዳት ብለውኢትዮጵያ ትቅደምን ይቃወማል፣ ከታሠሩት ባለሥልጣናትወይም ሚኒስትሮች የቅርብ ዝምድና አለው። ስለሆነም ሥራይበድላል፣ ሠራተኛውን ያጉላላል፣ ውሳኔ አይሰጥም” በማለትአለቆቻቸውን የሚከሱ፣ የሚወነጅሉ በርካታ ናቸው። ለደርግአባላት ቤታቸው ድረስ በመሄድ በማስረጃ የተደገፈ ቢሆንምባይሆንም ተቆርቋሪ በመምሰል የክስ ማመልከቻ የሚያቀርቡምነበሩ። እንታሠራለን ብለው በፍርሃት የተደበቁ ባለሥልጣናትንየቅርብ ዘመዶቻቸው ወይም አሽከሮቻቸው ወይምጎረቤቶቻቸው ደርግ ጽሕፈት ቤት ድረስ በመምጣትያጋልጧቸው ነበር። የመሥሪያ ቤቶችን ሰነዶች ፎቶ ኮፒ በማድረግ ወይም ሰነዱን እንዳለ ከፋይሉአውጥተው በማቅረብ “በመንግሥት ንብረት፣ ሀብት ወይንም ገንዘብ ላይ አላግባብ ተወስኗል” ብለውጥቆማና መረጃ የሚያቀርቡም ነበሩ። ሠራተኞች አሠሪዎቻቸውን ይከሳሉ፣ ይወነጅላሉ። ገበሬዎችለዘመናት በደል አደረሱብን የሚሏቸውን የአካባቢ ባለሥልጣናት ይወነጅላሉ። ውንጀላው በርካታነው።
አሽከሮች፣ ዘበኞች፣ ገረዶች… መረጃ ይሰጣሉ፣ ይጠቁማሉ። የተደበቀ የጦር መሣሪያ፣ የተደበቀ ገንዘብ፣ወደሌላ ቦታ የተወሰደ ወይም የሸሸ ሀብት እንዳለም የሚጠቁሙን እነሱ ናቸው። በአንድ ቦታ በርከትያሉ ሰዎች ተሰብስበው ምሽት ከአሳላፉ “ሲያድሙ ነበር” ብለው ከነስም ዝርዝራቸው መረጃውን ደርግጽሕፈት ቤት ድረስ ያመጣሉ። “እኛ እስከዛሬ የበይ ተመልካች ነበርን ዛሬ ዕድሜ ለእናንተ እንጀራሊወጣልን ነውከእናንተ ጎን ተሰልፈን አቆርቋዦቹን እንታገላለንበማንኛውም ጊዜ ትዕዛዝ ብትሰጡንለመፈጸም ዝግጁ ነን!” እያሉ ታማኝነታቸውንና ተባባሪነታቸውን የሚገልጡም ብዙዎች ነበሩ። በጣምየሚያስደንቀው አባቶቻቸውን፣ ልጆቻቸውን፣ ወንድሞቻቸውን፣ እህቶቻቸውን፣ ባሎቻቸውን፣ሚስቶቻቸውን በመክሰስ፣ በመወንጀል፣ በማጋለጥ፣ በመጠቆም ብሎም በማሳሰር ጉዳት ያደረሱበርካቶች መሆናቸው ነው።
እንግዲህ ስለ አዲሱ ‘እኛና አብዮቱ’ መጽሃፍ ይህንን ካልኩ ቀሪውን ለአንባቢ መተው ይበጃል። ሁሉም ሰው መጽሃፉን አንብቦ የራሱን ፍርድ ይስጥ።
ህይወት በሩጫ ትመሰላለች። የተፈጥሮ ህግጋት ነውና የሰው ልጅ እስትንፋሱ እስኪቋረጥ ይሮጣል።  ከዚያም ሩጫውን ይጨርሳል። ሩጫውን ሳይጨርስ በልቡ ቋጥኝ የያዘውን እምቅ ቋጠሮ የሚተነፍስ ደግሞ እድለኛ ነው።  በአንጻሩ ደግሞ በአእምሮውየቋጠረውን የእውቀት ምስጢር ሳያካፍል የሚያልፍ ሁሉ ያሳዝናል። ያለውን የወረወረ ንፉግ አይደለምና መንቀፍም ካለብን የሚወረውረውን ሳይሆን የማይወረውረውን ነው። መተቸት ካለብነም ሃሳቡን እንጂ ግለሰቡን ባይሆን ይመረጣል። በሃሳብ ላይ መወያየትና መተሻሸት ደግሞ አዋቂነት ነው።
በመጨረሻም የመጽሃፉ አርታኢ ኤልያስ ወንድሙ በመግቢያው ላይ ባሰፈረው መልእክት ጽሁፌን ልቋጭ።
የተማረ፣ ያወቀና ያደገ ትውልድና ዜጋ ምልክቱ የተጻፈን ማንበቡ፣ ያነበበውን ማብላላቱና ካነበበው ውስጥ ስንዴውን ከእንክርዳዱ መለየቱ ሲሆን፤ እራሱም አስተውሎና አገናዝቦ መጻፉ ደግሞ መማሩን ብቻ ሳይሆን መመራመሩንና ማወቁን የሚያሳይ ታላቅ ተግባር ነው። ለዚህም ደግሞ ግላዊ ነጻነት ያስፈልገዋልና ጫንቃው ላይ ያሉትን ግላዊና ታሪካዊ ቀንበሮች የሰበረ ነጻ ሰው መሆን ይጠበቅበታል። ትምህርትና ዕውቀት አስተዋይነትንና ጥልቀትን ከራስ በላይ ለትውልድ አሳቢነትን የሚያመለክት ታላቅ ኃላፊነት ነው። ለዚህም እንደ ትናንቱ ‘የተማረ ይግደለን’ ሳይሆን፤ የተማረ ያስተምረን፣ ያስተዳድረን ብሎም ይምራን በምንልበት ዘመን ከምናነብበው ውስጥ ያልተስማማንበትን በጨዋነት የመቃወም፣ የፈቀድነውን እንደ ስሜታችን የመደገፍና ተሳሳተ የምንለውን ለእርማት መጠቆም ግላዊ መብታችን ነው።…
* ፀሃይ አሳታሚ ድርጅት ከዚህ በፊት የቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያምን፣ የቀድሞውን የህወሃት መሪ ዶ/ር አረጋዊ በርሄን፣ የቀድሞውን የኢህአፓን አመራር አባል የዶ/ር መላኩ ገኝን፣ የቀድሞው ሚንስትር  የአቶ ተካልኝ ገዳሙን መጽሃፍትና  ከስልሳ በላይ የሆኑ በኢትዮጵያ ታሪክና ጥናት ላይ ያተኮሩ መጽሃፍትን ማሳታሙ ይታወሳል። ‘እኛና አብዮቱ’ የሚለው ይህ አዲስ መጽሃፍ በwww.tsehaipublishers.com ድረገጽና በቀርቡ በየሱቁ አንደሚገኝ ከሎስ አንጀነሰ የደረሰን ዘገባ  አስታውቋል። ሁላችንም ገዘተን እናንብብ።
መጽሃፉን አንብቤ እንደጨረስኩ በሂሳዊ ግምገማ እመለስበታለሁ።

Saturday 21 December 2013

የክፉ ቀን አለኝታዋ ትዝታ (በአበራ ለማ)

በአበራ ለማ

አበራ የማነአብ እና ገነት ግርማ

Ethiopian politicians Genet Girma and Abera Yemaneab

ከግራ ወደ ቀኝ ወ/ሮ ገነት ዘውዴ እና አቶ አበራ የማነአብ
አንጋፋው የዲሞክራሲና የለውጥ አርበኛ፥ አበራ የማነአብ፥ የሰባ ሁለት ዓመት አዛውንት ናቸው። ከዚህ እድሜያቸው ውስጥ የወያኔ/ኢሕአዴግ መንግሥት ባፈላማ ይዟቸው፤ ሃያ አምስቱን ዓመታት ባለም በቃኝና በቃሊቲ ወህኒ ቤቶች ቀርጧቸዋል። ከዚህ ውስጥ ባመክሮ ጥቂት ዓመታት አራግፈው፤ አሥራ ስድስት ዓመት ከስምንት ወራት በሕሊና እስረኝነት አሳልፈዋል። ደሞም ድፍን ሁለት ዓመታትን በጨለማ ቤት በመታገት፤ መራር ግፍና መከራን በመቋቋም፤ ከሞቱት በላይና ከቆሙት በታች በመሆን አቻ እንዳልተገኘላቸው ጉምዙ ትዝታቸው ያረዳናል፡፡
ይህም አልበቃ ያለው አጋች ክፍል አንዲት ጠባብ ክፍል ከሳምባ በሽተኞች ጋር የግድ እንዲጋሩ አድርጎ፤ ለሳምባ በሽተኝነት ዳርጓቸው ኖረዋል። ከዚህ ደዌ ለመፈወስ (ባገር ቤትም ሆነ በቅርቡ እዚህ አውሮፓ ከመጡ በኋላ) አጥብቀው ሕክምናቸውን በመከታተላቸው፤ ዛሬ በሙሉ ጤንነት ላይ ሊገኙ ችለዋል። ለሁለት ዓመታት በካቴና ታስረው እጨለማው ክፍል ውስጥ በሚማቅቁበት ወቅት የጃቸው ቆዳና ሥጋ ተበልቶ አልቆ፤ አጥንታቸው ገጦ ይታይ የነበረበትን የሰቆቃ ዓመታት ሲያስታውሱት እምባቸው ባይኖቻቸው ሙሉ ይሾማል። የኔ ብጤው ሆደባሻ አወያይ ደሞ፤ ሰቆቃቸውን ባይነ ሕሊናው ጭምር እየቃኘ፤ መግቢያ መውጪያው እንደጠፋበት የተከበበ አውሬ ጭንቅ ይለዋል።
“ለመሆኑ እኒህን በምድረ አሜሪካን ከተከበረ ቤተሰባቸው ጋር በሰላምና በተድላ ይኖሩ የነበሩን ትሁት ሰው ምን ተከርቸሌና ተቃሊቲ ወስዶ ዶላቸው?” የሚል መሪ ጥያቄ ያዘለ ሰው ብቅ ቢል አይፈረድበትም። የዚህ መጣጥፍ አቅራቢም ለሥራ ጉዳይ ወደ ቤልጅግ ብቅ ብሎ በነበረበት ወቅት፤ ይህን ጥያቄ ለሞክሼው ለአቶ አበራ ማስቀደሙ አልቀረም ነበር። አካሄዱ እሳቸውንና እሳቸውን የመሳሰሉ ጎምቱ የፖለቲካው ዓለም ምህዋር አርበኞችን የሕይወት ታሪክ ውርስ ለተሰኘ የዘጋቢ ፊልም ግብዓት ለመቃረም ነበር። (ይህ ለመጪው ትውልድ ቅርስነት የሚቀመጥ የተንቀሳቃሽ ፊልም ዘገባ አገር ቤትና እውጭ የሚኖሩትን ተጠቃሽ ያገር ልጆችን አውደ ሰብእና የሚያካትት ነው።) እናም የዚህ መጣጥፍ አቢይ ጭብጥ የሆነው ጉዳይም የተጨለፈው ከዚያው ከታሪካዊው ጭውውትና ቃለ መጠይቅ ላይ እንደሁ ምስጢር ብጤ ላውጣ። የዚህ ሠናይ ሥራ ዋልታና ማገር የሆኑት ባልደረቦቼ ጋዜጠኛና የፊልም ባለሙያው ክብረት መኮንን፥ ረዳቱ ጋዜጠኛ ሥዩም ደገፋ ይሁንታቸውን አይነፍጉኝም በሚል ተስፋም ምስጢሩን ለተደራስያን ሳካፍል ለይቅርታ እጅ እየነሳሁ ነው።
አዎን… ወደ ተነሳው መሪ ጥያቄ ልመለስና “…ሞክሼ እንዲያው ምን እግር ጥሎዎት ለዚህ ዓይነት ዳፋ ተዳረጉ?…” ለሚለው ጥያቄዬ አቶ አበራ የማነአብ የክፉ ቀን ትዝታን ጀልባ እየቀዘፉ፤  ከአሥራ ሰባት ዓመታት በፊት የሆነውን ሁሉ አጫውተውኛል፡፡ በተፈጥሯቸው እርጋታንና ጸጥታን የተላበሰው ገጽታቸው፤ የዘመኑን አንዳንድ ቀዥቃዣ መነኮሳትና ጳጳሳት ያስንቃል። ታንደበታቸው የሚወጣው እጅግ ቁጥብ አስተያየትና ረጋ ያለው ትረካቸው፤ ሲጠጡት ተዋንጫው እንዳያልቅ የሚጨነቁለትንና የሚሳሱለትን የወይን ጠጅ ያህል ያስጎመጃል። ያውም ከጠይም የመልካቸው ቀለም ጋር እየተናበበ… እየተጨዋወተ… እየተሟዘቀ… [ሙሉውን ለማንበብ እዚህ ይጫኑ]