Wednesday 14 January 2015

“ሕዝብን ለማውደም ውጤታማው መንገድ ታሪካቸውን የሚረዱበትን መንገድ ማስካድና ጨርሶውኑ መደምሰስ ነው” ጣይቱ ወደመ ቀጣይ ተረኛ . . .?

“ሕዝብን ለማውደም ውጤታማው መንገድ ሰዎች ታሪካቸውን የሚረዱበትን መንገድ ማስካድና ጨርሶውኑ በመደምሰስ ነው” የሚለው የእንስሶች እርሻ ደራሲ ጆርጅ ኦርዌል ብሒል ሰሞኑን ከፍተኛ መነጋሪያ ሆኗል፡፡ ለዚሁም መነሻው በየተራ እንዲወድሙ ከተደረጉት የሕዝብ የማንነት መገለጫዎች መካከል አንደኛ ቅርስ የሆነው የጣይቱ ሆቴል መውደምን ተከትሎ ነው፡፡
የእንስሶች እርሻ መጽሐፍ ህወሃት በተሰነጠቀበት ወቅት የእነ መለስ መገለጫ ነው ተብሎ በስፋት ኢትዮጵያ ውስጥ ሲነበብ የነበረ መጽሐፍ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የውኅዳኑ ደጋፊ ሪፖርተርም በየሳምንቱ እየተረጎመ ያቀርበው እንደነበር ጋዜጣው ምስክር ነው፡፡
ጋሼ ጳውሎስ ኞኞ በጻፈው “አጤ ምኒልክ” መፅሐፍ ገጽ 328-330 የሆቴሉ ታሪክ እንዲህ ይነበባል፡፡
በአዲስ አበባ የእንጦጦ ማርያም ቤተክርስቲያን ተሠርታ በምትመረቅበት ጊዜ በመላ ኢትዮጵያ ያሉ መኳንንት ለምረቃው ተጠርተው ነበር፡፡ ለተጠራው እንግዳ ማሳረፊያ እንጦጦ አይበቃ ስለነበር እቴጌ ጣይቱ ከእንጦጦ ተራራ ሥር ያለው ሕዝብ ሁሉ ለሚጠራው እንግዳ መጠለያ ቤት እንዲሰጥ ለመኑ፡፡ እንግዳ የሚያሳድር ሁሉ ሽሮ፣ በርበሬና ቅቤ፣ ዱቄትና ሥጋ ከቤተ መንግሥቱ እየወሰደ እንግዶቹን እንዲያስተናግድ አዘዙ፡፡ በዚህ ዓይነት የእንጦጦ ቤተ ክርስቲያን ምረቃ ተፈጸመ፡፡ ከዚህም በኋላ ለሚመጣው እንግዳ ማረፊያና መመገቢያ ችግር እየሆነ መጣ፡፡
ምኒልክ “እህእ” እያሉ ወሬ ያጠያይቁ ጀመር፡፡ “በፈረንጅ አገር ሆቴል የሚባል ቤት ስላለ ማንኛውም እንግዳ ገንዘቡን እየከፈለ ያርፍበታል፤ ምግቡንም ይበላበታል” አሏቸው፡፡ በዚህ መሠረት ሥራው እንዲጀመርአዝዘው ሕንጻው ተሠርቶ ሆቴል ቤቱ በ1898 ዓም በነሐሴ ወር ሥራው ጀመረ፡፡ ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ ስለ ሆቴል ቤቱ ሲያብራሩ “ስሙም ሆቴል ተባለ” ይላሉ፡፡ ኃላፊነቱም፣ ሥራውንም እቴጌ ጣይቱ ተክበው ይመሩና ያስተዳድሩ ጀመር፡፡ በ1900 ዓም ጥቅምት 25 ቀን ምኒልክ በአዲስ አበባ ያሉ ዲፕሎማቶችንና የውጭ አገር ሰዎችን ጋብዘው ሆቴሉን አስመረቁ፡፡ የመጀመሪያው ሥራ አስኪያጅም ሙሴ ፍሬደሪክ ሐል ነበር:: በኋላ ግን አቶ ዘለቃ አጋርደው ተሾሙ፡፡
እንደ አገር አባባል ጣይቱ እጅ የሚያስቆረጥም ወጥ እያሠሩ ገበያ ቢጠብቁ ጠፋ:: እንኳን ምግብ መብላት ከግሪኮች ሻይ ቤት ገብቶ ሻይ መጠጣት ነውር ነበረና ጣይቱ ጠዋት የሚያሠሩት ወጥ ለሠራተኞቹ የማታ ራት ይሆን ጀመር፡፡ የሚስታቸው ገበያ ማጣት ያሳሰባቸው አጤ ምኒልክ አንድ ቀን ከችሎት ሊነሱ ሲሉ በአካባቢያቸው ላሉ መኩዋንንቶች “ጣይቱ ምግብ የሚሸጥበት ቤት ከፍታለችና ኑ እንሂድና ልጋብዛችሁ” ብለው ወሰዱዋቸው፡፡ መኳንንት በላ ጠጣና ምኒልክ 30 ብር ከፈሉ፡፡
በማግሥቱ እንደተለመደው ገበያ ቢጠበቅ ጠፋ ቀጥሎም ጠፋ፤ ቀጥሎም ጠፋ፡፡ እንደገና ምኒልክ ሆቴል ገብቶ መብላት ነውር ያለ መሆኑን ለመኳንንቱ ገልፀው እንደገና ምሣ ጋበዙ፡፡ በሌላው ቀን አሁንም ገበያ አልተገኘም፡፡ ቢጠበቅ ቢጠበቅ ድርሽ የሚል ሰው ጠፋ፡፡ በሌላ ቀን ደግሞ አጤ ምኒልክ ከችሎት ሊነሱ ሲሉ በዙሪያቸው ላሉ መኳንንት “ሰማችሁ ወዳጆቼ” አሉ:: “በፈረንጅ አገር አንድ ቀን አንድ ሰው የጋበዘ እንደሆነ ያ የተጋበዘ ሰው በሌላ ቀን ደግሞ ብድሩን ይከፍላል ብድሩን ካልከፈለ ግን እንደ ነውር ይቆጠርበታል፡፡” ብለው ንግግራቸውን ሳይጨርሱ መኳንንቱ “እርስዎን ፈርተንና አፍረን ነው እንጂ የሚሆንልን ከሆነ የምኒልክን ብድር ለመመለስ እኔ አለሁ” እያለ ተራ በተራ ከሆቴል ቤት ምኒልክንና ጣይቱን ይጋብዝ ጀመረ፡፡ ገበያ እየደራ ሄደ፡፡ ምሳችንን እቴጌ ሆቴል ሄደን እንብላ የሚለው ስለበዛም ስሙ እቴጌ ሆቴል ተባለ፡፡
ዛሬ በታላላቅና በሌሎችም ሆቴል ቤቶች ጋሻና ጦር እየተሰቀለ እናያለን፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አደራረግ የተጀመረው በምኒልክ ነው፡፡
[እምዬ ምኒልክ መጋቢት 3፤ 1900ዓም ለደጃዝማች ሥዩም የላኩት መልዕክት እንዲህ ይነበባል]
ይድረስ ለደጃዝማች ሥዩም፤
“. . . የላክኸው የዝሆን ጥርስ አልጋና ተምቤን የተሠራ ጋሻ ደረሰልኝ፡፡ ጋሻ ግን ለግራኝ ተብሎ ተሠርቶ እንደሆነ ነው እንጂ ሌላ ሰው ይይዘዋል ተብሎ አልተሠራም፡፡ ነገር ግን ለሆቴል ቤት ለላንቲካ እንዲሆን አደረግሁት. . . ”
**********************************
?
አይመስለኝም ነበር እሳት ወኔ ኖሮት
ጣይን የሚገላት
ወልዮልሽ አራዳ … …. ወዮልሽ ሃገሬ
ማን ሊያሞቅሽ ነዉ
አድማስ ተደርምሶ ጣይሽ ጠልቃ ዛሬ?
(Binu Ye Tsehay ፌሰቡክ)

“ሕዝብን ለማውደም ውጤታማው መንገድ ሰዎች ታሪካቸውን የሚረዱበትን መንገድ ማስካድና ጨርሶውኑ በመደምሰስ ነው” ጆርጅ ኦርዌል፡፡

taitu hoteltayitu hotelItegue-Taitu-Hoteltaitu hTaituHotelTaitu-hotelTaitu_hTaytu-Hotel

በኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባርና የግንቦት 7፣ ለፍትህ፣ ዴሞክራሲና የነጻነት፣ ንቅናቄ መሀል የተደረገውን ውህደት በተመለከተ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ፣

በኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባርና የግንቦት 7፣ ለፍትህ፣ ዴሞክራሲና የነጻነት፣ ንቅናቄ መሀል የተደረገውን ውህደት በተመለከተ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

በዛሬው ዕለት፣ ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባርና የግንቦት 7፣ ለፍትህ ለዴሞክራሲና የነጻነት፣ ንቅናቄ፣ ድርጅቶች፣ ተዋህደን “አርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ”፣ በሚባል ሥም መጠራት መጀመራችንን ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስናበስር፣ እጅግ ከፍተኛ ደስታ ይሰማናል።
የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ባለፉት በርካታ አስርተ አመታት፣ለፍትህ፣ ለእኩልነት፣ ለነጻነት፣ መብትና አንድነት፣ ከፍተኛ ትግል ሲያካሂድ ቆይቷል። በአደረገውም ትግል እጅግ ከፍተኛ መስዕዋትነት ከፍሏል። ለከፈለው ከፍተኛ ዋጋ የሚመጥን ግን ምንም ዓይነት ውጤት አላገኘም። እንዲያውም ከጊዜ ወደ ጊዜ የመብት ረገጣው፣ አድሎው፣ ማስፈራራቱና ማዋከቡ ተጠናክረው መቀጠል ብቻ ሳይሆን፣ ሀገራችን ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ልትቀጥል የማያስችል ከፍተኛ የመበታተን አደጋ አንጃቦባት ትገኛለች ።
በሀገራችን ላይ ላንጃበበው ከፍተኛ የመበታተን አደጋ ምክንያት የሆነው በሥልጣን ላይ ያለው የወያኔ የአምባገነን ቡድን ነው። ይህ ዘረኛ አምባገነን ቡድን በሀገራችን ታሪክ በሥልጣን ላይ ከመጡ የገዥ ሃይሎች ጋር ሲወዳደር ሀገርን ለከፍተኛ አደጋ በማጋለጥ፣ ሕዝቧን በማወረድ፣ ተወዳዳሪ የማይገኝለት ዕኩይ ሃይል መሆኑን በበርካታ ተግባራቶቹ ያለ ምንም ጥርጣሬ አረጋግጧል።
በሌላ በኩል ለቀድሞቹም ሆነ ለዛሬው ዘረኛው የወያኔ አምባገነን ገዥ በሕዝብና በሀገር ላይ በደል እየፈጸመ በሥልጣን መቆየት የቻለበት ምክንያት፣ በተቃዋሚነት የሕዝቡን ትግል ለመምራት የተንቀሳቀስን ድርጅቶች፣ የተቋቋምንበት ዓላማ መለያዬት ብቻ ሳይሆን፣ አንድ ዓይነት ዓላማ ያለንም ብንሆን፣ ከድርጅቶቻችን ጠባብ ፍላጎቶችና ስሜቶች ባለፈ፣ የሀገርና የሕዝብን ጉዳይ በማስቀደም በጋራ መሰባሰብና መታገል ስላቃተን ነው። በዚህም ድርጊታችን የራሳችንን ብቻ ሳይሆን የወገናችንንም የመከራ ዘመን እያራዘምን እንገኛለን ።
ይህ ሁኔታ በተለያዩ ተቃዋሚ ድርጅቶች መሀል ከፍተኛ ጥርጣሬና ፍርሀት ከመፍጠሩ የተነሳ በምንም ዓይነት ሁኔታ፣ ተቃዋሚ ድርጅቶች በጋራ በሀገርና በሕዝብ ደረጃ ትርጉም ያለው ስራ መስራት አይችሉም፣ የሚለው አመለካከት የበላይነት እንዲያገኝ አድርጎታል።
በዛሬው ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም ወደ ውህደት የመጣነው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባርና የግንቦት 7፣ ለፍትህ፣፡ ለነጻነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ መዋሃድ መወሰናችንን ፣ ስንገልጽ በተናጠል ከሚደረጉ በጋራ የሚደረጉ የትግል ጥረቶች ውጤታማ ይሆናሉ በሚል ብቻ ሳይሆን፣ የተቃዋሚ ድርጅቶች፣ በምንም ዓይነት ሁኔታ በሀገርና በሕዝብ ደረጃ ትርጉም ያለው ሥራ በጋራ መስራት አይቻሉም የሚለውን፣ አስከፊ ተመክሮና አመለካካት ለመስበርም ነው።
በእኛ እምነት ከትናናሽ ድርጅቶች ዙሪያ ከሚሽከረከሩ ሀሳቦችና ስሜቶች ለመውጣትና ሀገራዊና ሕዝባዊ የሆነው ጉዳይ ለማስቀደም የወሰነ ማንኛውም ድርጅት፣ አርበኞችና ግንቦት7፣ የደረሱበት የውህደት ውሳኔ ወይም በሌሎች በጋራ ሊያሰሩ በሚችሉ ስምምነቶች አብሮ ለመስራት መወሰን የማይችልበት ምንም ምክንያት አይታየንም። በወያኔ አድሎ ስርዓት የተንገፈገፈና ትግሉን ለመቀላቀል የቆረጠ ማንኛውም ዜጋ፣ የተገኘውን አጋጣሚ በመጠቀም ትግሉን መቀላቀል ይችላል፣ የኢትዮያ ሕዝብ በአንድነት የተነሳ ቀን ደግሞ፣ የወያኔ ግብዓተ መሬት ይፈጸማል፣ ብለን ከልብ እናምናለን።
ይህም በመሆኑ፣
ለተቃዋሚ ድርጅቶች፣
ዛሬ በአርበኞችና በግንቦት 7፣ የተጀመረው ጉዞ ውጤታማ በመሆን ሀገራዊና ታሪካዊ ትርጉም እንዲኖረው፣ ሌሎችም በተግባር የምትንቀሳቀሱ ተቃዋሚ ድርጅቶች፣ ወያኔን የማስወገድንና ብሎም ሀገር የማረጋጋቱን ሀላፊነት በጋራ እንድንወጣ የሚያስችል መቀራረብ እንድናደርግ ፣ በውህደት በመሰረትነው፣ በአርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ፣ ሥም፣ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
ለወታደራዊና የፖሊስ ሠራዊት አባላት፣
የወያኔ ዘረኛና አምባገነን ቡድን ዕድሜን ለማሳጠርና ሁላችንንም በእኩልነት የምታስተናግድ ሀገር እንድትኖር ፣ በየቦታው የሚደረገውን ትግል፣ የሰሞኑን ቆራጥ የዓየር ሃይል መኮንንኖች ያሳዩትን ዓርያነት በመከተልና በተገኘው አጋጣሚና ሁኔታ በመጠቀም፣ እንድትቀላቀሉ በውህደቱ ድርጅት፣ በአርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ፣ ሥም፣ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
የተከበርከው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሆይ፣
በረጅም ታሪክህ አይተሄው ለማታውቀው፣ ውርደት፣ ክፋት፣ የመከፋፈልና የመጋጨት አደጋ፣ የመብት እረገጣና አፈና፣ ሀገርና ሕዝብን የማራከስና የመሸጥ፣ ዕኩይ ተግባር፣ የተጠናወተው ወያኔ እና የግብር አበሮቹን፣ ጠራርጎ ለማስወገድ በተጀመረው የጋራ ትግል ውስጥ በቀጥታ እንድትሳተፍም ሆነ በምትችለው ሁሉ እርዳታ እንድታደርግ፣ በዛሬው ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም የአርበኞችና የግንቦት 7 ውህደት በወለደው፣ በአርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ ሥም፣ ጥሪያችንን እናቀርባለን።
ድል ለኢዮጵያ ሕዝብ!!!
አርበኞች ግንቦት 7፣ ለአንድነትና ዴሞክራሲ፣ ንቅናቄ፣
ጥር 2 ቀን 2007 ዓ.ም