Thursday 30 May 2013

የኢትዮጵያ መንግስት የኢንተርኔት ድህረ ገጾችን ለማፈን 26 ቢሊዮን ብር ክፍያ ለቻይና መንግስት ፈጸመ

ግንቦት ፳፪ (ሀያ ሁለት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ኢሳት ከአስተማማኝ የኢትዮጵያ የመረጃ መረብ የደህንነት ሰራተኛ ባገኘው መረጃ መንግስት ለስርአቱ አደጋ ይሆናሉ ብሎ የገመታቸውን የመገናኝ ብዙሀን ወደ አገር ቤት ሰርገው እንዳይገቡ ለመከላከል ከ1.2 ቢሊዮን ዶላር ወይም ወደ 26 ቢሊዮን የሚጠጋ ገንዘብ መክፈሉን ለማወቅ ተችሎአል።
በቁጥር አንድ እንዲታፈን ትእዛዝ የተላለፈበት ኢሳት ሲሆን ድህረገጹ ራዲዮው እና ቴሌቪዥኑን ሙሉ በሙሉ  እንዲታፈን ስምምነት ላይ ተደርሷል።  ፣ የአሜሪካ ድምጽ  እና የጀርመን ድምጽ የራዲዮ ጣቢያዎች ደግሞ በሚያቀርቡት ዝግጅት ይዘት አይነት አፈና እንዲካሄድባቸው ሲወሰን አሁንም ድረስ ስርአቱን የሚጻረሩ ድረጎች ሙሉ በሙሉ እንደታፈኑ ይገኛሉ።
ኢሳት ድረገጹ ቢታፈንበትም ራዲዮ እና ቴሌቪዥኑ ካለፉት 5 ወራት ጀምሮ ያለ ምንም ችግር እየተላለፈ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ህዝብ የዲሽ አቅጣቻውን በየጊዜው በመቀያየር ኢሳትን በመከታተል ላይ ይገኛል። አንድንድ ባለስልጣናትም ኢሳትን እየተከታተሉ አንዳንድ እርምጃዎችን መውሰድ መጀመራቸውን የሚደርሱን መረጃዎች ያሳያሉ።
በተመሳሳይ ዜናም መንግስት በፊስ ቡክ እየደረሰበት ያለውን ውግዘት እና የለውጥ ማእበል ለመግታት ‹‹ ሬሳው ›› ሲል ስም የሰጠውን የአፈና ቴክኖለጅ ተግባራዊ ለማድረግ እንቅስቃሴ ጀምሯል፡፡ ሙከራው ተግባራዊ ከሆነ ሙሉ ለሙሉ የፊስ ቡክ ግንኙነቶችን ለመገደብ እድል እንደሚያገኝ የደረሰን መረጃ ያሳያል። ካለፈው ወር ጀምሮ ስራውን ለማስጀመር የተደረገው ተደጋጋሚ ጥረት አለመሳካቱ ታውቋል።
በጉዳዩ ዙሪያ የመንግስት ባለስልጣናትን ለማነጋገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።

             ESAT Eneweyay on the protest rally called by Semayawi Party Amsterdam   


የግንቦት ሰባት አራተኛ ጉባኤ አቋም መግለጫ | Official Site for Ginbot 7 Movement for Justice, Freedom and Democracy

የግንቦት ሰባት አራተኛ ጉባኤ አቋም መግለጫ
የግንቦት ሰባት የፍትህ ፤ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አራተኛ ጉባኤ ቅዳሜ ግንቦት 17 ቀን 2005 ዓም ተጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት ከተካሄደ በኋላ ህዝባዊ ትግሉን ወደፊት የሚያራምዱ ዉሳኔዎችን ካሳለፈ በኋለ ባለፈዉ ሰኞ ምሽት እጅግ በጣም በደመቀ ሁኔታ ተጠናቀቀ። ይህ የንቅናቄዉ አራተኛ መደበኛ ጉባኤ ንቅናቄዉ ባለፉት ሁለት አመታት የተጓዘባቸዉን መንገዶች፤ ያቀዳቸዉን ስራዎችና የዕቅዱን አፈጻጸም በጥልቀትና በስፋት በመዳሰስ መጪዉ የትግል ወቅት የሚጠይቀዉን የመስዋዕትነት ደረጃ ከወዲሁ ተመልክቶ ዘረኛዉን የወያኔ አገዘዝ በማስወገድ የኢትዮጵያን ህዝብ የፍትህና የዲሞክራሲ ጥማት ሊያረኩ ይችላሉ ብሎ ያመነባቸዉን አበይት ዉሳኔዎች አሳልፏል።
የግንቦት ሰባት አራተኛ መደበኛ ጉባኤ የንቅናቄዉን የአለፉት አምስት አመታት ጉዞና በዚህ በአራተኛዉ ጉበኤ ላይ የስልጣን ዘመናቸዉን የጨረሱት የንቅናቄዉ ምክር ቤትና የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የስራ ዕቅድና የስራ አፈጻጸም ሪፖርት አዳምጦ ሰፊና ጥልቅ ዉይይት ካካሄደ በኋላ በጉባኤዉ ላይ አዲስ ለተመረጡ የአመራር አባላት ንቅናቄዉ የታሰበበትን ግብ እንዳይመታ አንቀዉ የያዙትን እንቅፋቶች እንዲያስወግድና እንዲሁም የንቅነቁዉ ጥንካሬ በታየባቸዉ መስኮች አቅሙን አጣናክሮ በይበልጥ በመስራት የኢትዮጵያ ህዝብ ከንቅናቄዉ የሚጠብቀዉን የታሪክ አደራ እንዲወጣ አሳስቧል። በጉባኤዉ ወቅት አባላት ያደረጉት አመራሩን የመንቀፍ፤አቅጣጫ የማሳየት፤ ሀሳብ የማመንጨትና በአጠቃላይ በእያንዳንዱ የጉባአዉ ስብሰባ ላይ ባሳዩት ንቁ ተሳትፎ ንቅናቄዉ በህዝባዊ አመጽና እምቢተኝነት ዘርፎች ብቻ ሳይሆን በዲሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍም እያደገ መምጣቱን አሳይተዋል።
የግንቦት ሰባት አራተኛ መደበኛ ጉባኤ የምክር ቤትና የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፤ ኦዲትና ቁጥጥር ኮሚቴ እንዲሁም የስነ ስርአትና የግልግል ኮሚቴ ሪፖርቶችን አዳምጦ ሰፊና ጥልቅ ዉይይት ካካሄደ በኋላ ሪፖርቶቹን አጽድቋል። ከዚህ በተጨማሪ የንቅናቄዉን እስትራቴጂና ይህንኑ እስትራቴጂ ተሸክሞ በተግባር የሚተረጉመዉን መዋቅር በአጽንኦት ከፈተሸ በኋላ በስትራቴጂዉ ላይ መጠነኛ ለዉጥ በማድረግ የእስትራቴጂዉንና የመዋቅር ለዉጡን ተቀብሎ አጽድቋል። ይህ የንቅናቁዉ አራተኛ ጉባዜ ንቅናቄዉን ላለፉት ሁለት አመታት የመሩትንና ያገለገሉትን የምክር ቤት፤ የኦዲትና ቁጥጥር፤ የስነ ስርአትና ግልግልና የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ላደረጉት አስተዋጽኦ አመስግኖ በማሰናበት በምትካቸዉ ንቅናቄዉን ለሚቀጥሉት ሁለት አመታት የሚያገለግሉ የምክር ቤት አባላት፤ የኦዲትና ቁጥጥር፤ እንዲሁም የስነ ስርአትና ግልግል ኮሚቴ አባላትን መርጧል።
አራተኛዉ የግንቦት ሰባት መደበኛ ጉባኤ ኢትዮጵያ ዛሬ የምትገኝበትን ሁኔታ በዝርዝር ከቃኘ በኋላ ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር ዉጊያ የተያያዘዉ አገር ዉስጥና በዉጭ አገሮችም ስለሆነ ወያኔን በእነዚህ ሁለት የትግል መስኮች እንደአመጣጡ ከገጠምነዉ የሚሸነፍ ድርጅት መሆኑን ሙሉ በሙሉ በመቀበል አባላቱ ባሉበት ቦታ ሁሉ የሚሰሩት ስራ ወያኔን በማስወገድ ላይ እንዲያተኩር አሳስቧል። ከአለም ዙሪያ ከተለያዩ አገሮች የመጡ የግንቦት ሰባት አባላትን ያሰባሰበዉ አራተኛዉ የግንቦት ሰባት መደበኛ ጉባኤ የትግል ቃል ኪዳን የታደሰበት፤የመስዋዕትነት ዝግጅት የታየበትና አባላት የትግልና የስራ ልምድ የተላዋወጡበት ከምን ግዜዉም ባላይ የተሳካና የተዋጣለት ጉባኤ ነበር። በመጨረሻ ጉባኤዉ የግንቦት ሰባት የፍትህ ፤ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አራተኛ ጉባኤ ለአባላቱና በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ህዝብ አዲስ የትግል ጥሪ በማስተላለፍ ደማቅ በሆነ ስነሰርአት ተፍጽሟል።
የግንቦት ሰባት የፍትህ ፤ የነጻነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ
የግንቦት ሰባት አራተኛ ጉባኤ አቋም መግለጫ | Official Site for Ginbot 7 Movement for Justice, Freedom and Democracy

                   ESAT Daily News Amsterdam May 30, 2013 Ethiopia


Wednesday 29 May 2013

በአንባገነኖች የሀሰት ውንጀላ እስር እና እንግልት አንበረከክም! (ባለራዕይ ወጣቶች ማህበር)

በአንባገነኖች የሀሰት ውንጀላ እስር እና እንግልት አንበረከክም! (ባለራዕይ ወጣቶች ማህበር)

Statement from Baleraey Wetatoch

3 Responses to በአንባገነኖች የሀሰት ውንጀላ እስር እና እንግልት አንበረከክም! (ባለራዕይ ወጣቶች ማህበር

ኢህአዴግ የሚያሸንፈው መቼ ነው?

ኢህአዴግ የሚያሸንፈው መቼ ነው?

ጌታቸው ሽፈራው
መቼም ይህን ጥያቄ ስጠይቅ የግንቦት 20ን ‹‹ድል››፣ የ2002ና የባለፈውን ሚያዚያ 2005 ዓ/ም የቀበሌ፣ የወረዳ……ምርጫም ጨምሮ በመከራከሪያነት በማንሳት ምን ነካው ኢህአዴግ እኮ እያሸነፈ ነው የሚሉ አይጠፋም፡፡ ለእኔ ማሸነፍ ማለት የህዝብን ልብና አዕምሮ (hearts and minds) መያዝ ሲቻል ነው፡፡ በሀይልማ ከሆነ ጣሊያን፣ ጀርመን፣ እንግሊዝ በአጠቃላይ ቀኝ ገዥዎቹ አፍሪካውያንን በወታደራዊ ሀይልና በሌሎች አቅሞቻቸው በመብለጣቸው እስከ መቶ አመት ድረስ ገዝተዋል፡፡ በኤሲያን ደቡብ አሜሪካ ደግሞ ከ200 እስከ 800 አመትም የተገዙ ህዝቦች ነበሩ፡፡ ለጊዜው አሸናፊ የመሰሉት ቅኝ ገዥዎች የእነዚህን ህዝቦች ልብ መግዛት ባለመቻላቸው ጊዜ ጠብቀውም ቢሆን ተሸናፊዎች ሆነዋል፡፡ ኢህአዴግ አሸነፍኩት የሚለውን የመንግስቱ ሀይለማሪያም ደርግ ጨምሮ ህዝባቸውን በሀይል ጨምድደው የኖሩ ስርዓቶች የኋላ ኋላ ተሸንፈዋል፡፡ እነዚህ አካላት የተሸነፉት ህዝብን በሀይል እንጂ በሀሳብ ማሳመን ባለመቻላቸው ነው፡፡ ሰውን በሆዱ አሊያም በግድ ለዘላለም መግዛት አይቻልም፡፡ አንድም የሚፈልገው ነገር በየጊዜው ስለሚጨምር ይህን በየጊዜው የሚጨምርን ነገር ማሟላት አይቻልም፡፡ ማሟላት ቢቻል እንኳ ሰው የመጨረሻ ፍላጎቱ ነጻነት ነውና ዳቦ ጠግቦም ሆነ ሳይጠግብ ነጻነቱን መጠየቁን አያቆምም፡፡
ኢህአዴግም እስካሁን የኢትዮጵያውያንን ልብ በሀሳብ መግዛት አልተቻለውም፡፡ በብሄር፣ በስራና ጥቅማጥቅም፣ በማሳፈራራት፣ የሌሎቹ አስተሳሰብ እንዳይደርስ በማገድ ስልጣኑን ለማራዘም ቀና ደፋ እያለ ነው፡፡ ኢህአዴግ በዋነኝነት አሸንፍበታለሁ ብሎ የጀመረው የብሄርን ፖለቲካ ቢሆንም ይህ ቀመር የኢትዮጵያውያንን ልብ ሊገዛለት አልቻለም፡፡ ይህ እንደማያዋጣው ያሰበው ኢህአዴግ ኢትዮጵያውያን ሊሸነፉበት የሚችሉትን አስተሳሰቦች ለይስሙላህም ቢሆን ከጀመረ ጥቂት አመታት ተቆጥረዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል የሚሊኒየም በዓልና የሰንደቅ አላማ ቀን የመሳሰሉትን አገራዊ እሴቶች ማንሳት ጀምሯል፡፡ ይሁንና እነዚህንም ቢሆን ከልብ ሳይሆን ለመቀስቀሻነት ብቻ እየተጠቀመባቸው በመሆኑ ሊያሸንፍባቸው አልቻለም፡፡ በመሆኑም ኢህአዴግ  እስካሁን ኢትዮጵያውያንን ማሸነፍ አልቻለም፡፡
ኢትዮጵያውያን የሚሸነፉት መቼ ነው?
ኢህአዴግ ለጊዜው ኢትዮጵያውያንን በበላይነት መራ እንጂ አላሸነፋቸው እያልን ነው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በአንድ አካል በሀይል ቁጥጥር ስር የወደቀ ሰው በዚህ አካል ሀይል ቁጥጥር ስር እንዲገባ ያደረገውን እምነቱን ጣል እርግፍ አድርጎ እስካልጣለ ድረስ ተሸናፊ ሊባይ አይቻልም፡፡ በመሆኑም ለእኔ እነ እስክንድር ነጋ፣ ርዕዮት አለሙ፣ ውብሸት ታዬ፣ በቀለ ገርባ የመሳሰሉት ዜጎች በኢህአዴግ ቁጥጥር ስር ቢሆኑም ከአካላቸው ውጭ እምነታቸውን መቆጣጠር እስካልቻለ ድረስ ተሸናፊዎች አይደሉም፡፡ በተቃራኒው ትናንት  ‹‹ዜሮ ዜሮን›› ዘፍነው ዛሬ ‹‹ይቀጥል!›› ያሉት እነ ሰለሞን፤ ትንንት ለኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ድምጽ የነበሩትና አሁን በክብ ጠረጴዛ ለስርዓቱ ድምጽ የሆኑት እነ ሚሚ እንደልባቸው ቤተመንግስት መግባት ቢችሉም ኢህአዴግ ከልብና አዕምሯቸው በላይ ገዝቷቸዋል አሳዛኝ ተሸናፊዎች ናቸው፡፡ አሳዛኝ ተሸናፊ መጀመሪያ የተነሳበትን አያውቅም አሊያም ሲሸነፍም ድሮ ከነበረው አመለካከት በተቃራኒ ሁለመናውን የሚማረክ ነው፡፡ የእነዚህ ኢትዮጵያውያን ሽንፈት ጠንካራ ወታደር እያለው እራሱን ለጠላት በምርኮ እንዳቀረበ ጀኔራል እቆጥራቸዋለሁ፡፡ በተቃራኒው እነ እስክንድር ምንም ወታደር በሌለበት ብቻውን ከጠላት ጋር የሚፋለም ሲፋለም ተይዞ ስለ ክብሩ ሞትን ከሚጠባበቅ ጀግና ጀኔራል ጋር ቢመሰሉ አያንስባቸውም፡፡ ሽንፈት እንዲህ ለእየቅል ነው፡፡ ለአብዛኛዎቹ በተለይም ለታዋቂዎቹ መሸነፍ ጥቅም፣ ዝና ቀዳሚው ሲሆን በርካታዎቹ ኢትዮጵያውያን እንዳይሸነፉ ያደረጋቸው ኢትጵያውይነት ነው፡፡
አንድ ሰው በራሱ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ፣ ጉራጌ.. መሆኑን በማመኑ አሊያም ሌሎች በዚህ ምድብ ውስጥ ስላስገቡት ብቻ በብሄር ስም ሊጠራ ይችላል፡፡ አምኖም ሆነ ተወናብዶ በብሄር ማመኑ በራሱ ችግር ላይኖረውም ይችላል፡፡ ብሄር ችግር የሚያመጣው የመከፋፈያ መንገድና ለፖለቲከኞች መጠቀሚያ በሚያመች መልኩ ሲመነዘር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ብሄር ለመከፋፈያና ለፖለቲከኞች መጠቀሚያ በሚያገለግል መልኩ ቢመነዘርም አብዛኛዎቹ ኢትዮጵያውያን በዚህ ደስተኛ ባለመሆናቸው ኢህአዴግም ለማስመሰያነት  የሚጠቀምበት የአንድነት አጀንዳ ለማንሳት ፈራሁ ተባሁ እያለ ይመስላል፡፡ ኢትዮጵያውያን በዚህ በኩል ከመሸነፍ ይልቅ ማሸነፍ ወደሚችሉበት መንገድ ተቃርበዋል ማለት ይቻላል፡፡
በተቃራኒው ግን ብሄርን በዋነኛ መሳሪያነት የሚጠቀመው ኢህአዴግ ያሸነፈ የመሰላቸው ‹‹እሳትን በእሳት›› በሚል ይህን ቀመር የመረጡ አልጠፉም፡፡ ኢህአዴግ ያደርጋቸውን እያንዳንዱን እንቅስቃሴዎች ከብሄር አይን ብቻ በማየት በብሄር ቀመር ለመፍታት መጣር እስካሁንም ተቃውሞው ጎራ ውስጥ አልጠፉም፡፡ ይህ አንድ ስልት አይደለም ማለት አይቻልም፡፡ ሆኖም በተለይ በኢትዮጵያውይነት እናምናለን የሚሉትም አጀንዳ ሲያደርጉት ፖለቲካውን መርህ አልባ ያደርገዋል፡፡ ለአብነት ያህል ከየክልሉ የሚባረሩ ኢትዮጵያውያንን በኢትዮጵያውይነታቸው ሳይሆን በአማራነታቸው ብቻ መመንዘር እየተበራከ ነው፡፡ በእርግጥ ኢህአዴግ በተወሰነ ማህበረሰብ ላይ የሚያደርገው ይህ እርምጃ ተቃዋሚዎችን ወደዚህ የኢህአዴግ መስመር ሊጎትት ይችል ይሆናል፡፡ ኢህአዴግ የሚፈልገውም እያንዳንዱ ጉዳይ በአገር ማዕቀፍ ሳይሆን በብሄር አይን እንዲመነዘር ነው፡፡ ለተቃዋሚዎች ውድቀቱ የሚሆነውም ኢህአዴግም ይህን አንድ ማህበረሰብ ላይ የሚያደርገው እርምጃ የብሄር ፖለቲካውን እንዳይበርድና ኢትዮጵያውያን በአንድ ማዕቀፍ ይልቅ በቋንቋ የሚከፋፈሉበትን ‹‹የእኛ›› እና ‹‹እነርሱ›› ፖለቲካ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ለማድረግ  ስለሆነ በእሱ መስመር መግባታቸው ነው፡፡ በዚህ የኢህአዴግ ቀመር መሰረት ‹‹አማራ›› በመሆናቸው ‹‹ከቤንሻንጉል››፣ ከደቡብ ብሄራዊ ክልሎች ተባረሩ የሚል ክርክር አሸናፊ ሊሆን አይችልም፡፡ እነዚህን ህዝቦች በብሄር አምኖ የመደበ ተቃዋሚ ‹‹ውጡልን›› ያላቸው ፖለቲከኞች ወክለነዋል የሚሉትን ብሄር መብት ኢህአዴጋዊ በሆነው በዚሁ ቀመር ሊያምን ነው ማለት ነው፡፡ በመሆኑም ጉዳዩ መታየት ያለበት በኢትዮጵያዊ መዕቀፍ እንጂ በብሄር ማዕቀፍ አይደለም፡፡ ተቃውሞው በብሄር ማዕቀፍ ሳይሆን በኢትዮጵያውይነት ከዚያም አለፍ ሲል በሰብአዊነት ሲሆን የትግል አንድነቱ በመርህ ላይ የተመሰረተ ያደርገዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያውያን ተቃዋሚዎችም ወደውም ሆነ በግድ ወደ ኢህአዴግ ቀመር እየተንፏቀቁ በመሆኑ ኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ በደል ሲደርስበት ይህን ህዝብ እንወክላለን የሚሉት አካላት ብቻ በቀዳሚነት ድምጻቸውን ያሰማሉ፡፡ አማርኛ ተናጋሪው ላይ በደል ሲደርስ በብሄርና አንድነት መካከል ግራ የተጋቡት ተቃዋሚዎች ድምጽ ሲያሰሙ ‹‹ሌላውን›› ህዝብ የሚወክሉት አካላት ድምጻቸው እምብዛም አይሰማም፡፡ በትግራይ ህዝብ ላይ በደል እንደሚደርስ የሚያምኑ ኢትዮጵያውያን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሱ ነው፡፡ በዚህ በኩል ህውሃት/ኢህአዴግ ባያሸንፍም ለጊዜው የተሳካለት ይመስላል፡፡ በቅርቡ ወደ ተቃውሞ ጎራው ለመቅረብ እየሞከሩ ያሉት ትግርኛ ተናጋሪዎች የትግራይን ህዝብ በደል ብቻቸውን የሚናገሩ ሆነዋል፡፡
ኢላማውን ያልለየ ተቃውሞ
አንድ ትግል እንደ ትግል ውጤታማ ለመሆን ኢላማውን መለየት ይገባዋል፡፡ ካልሆነ ከእንሰሳ መንጋ ውስጥ ገብቶ ያየውን ሁሉ ለመያዝ የሚቋምጥና ሁሉን ሲያሯሩጥ ውሉ ደክሞ የሚመለስ አዳኝ እንሰሳ መሆን ነው፡፡ የሚይዘውን ታዳኝ ቀድሞ ያልለየ አዳኝ ትርፉ ድካምና ታዳኙ ማንቃት ብቻ ነው፡፡ በፖለቲካ ስልትም ቢሆን ተለይተው መቀመጥ ያለባቸው ኢላማዎች ይኖራሉ፡፡ ከአንድ በላይ መለየት ያለባቸው እንኳ ቢኖሩ በቅደም ተከተል መቀመጥ የግድ ይላቸዋል፡፡ ይህ ገንዘብን፣ የሰው ሀይልንና ጊዜን ለመቆጠብም ሆነ በአጭር ጊዜ ውጤት ለማምጣት አይነተኛ መንገድ ነው፡፡ ይህ ካልሆነ ግን የሚከተለው ተስፋ መቁረጥና መጀመሪያ ከተመረጠው የትግል ስልት ማፈንገጥ ሲብስም ከተቃውሞው ጎራ መውጣትና እንዋጋዋለን በሚሉት ሀይል መዋጥ ወይንም መሸነፍ ነው፡፡
ይህ ችግር በአገራችን የተቃውሞ ጎራም ተከስቷል፡፡ በተለይ ብሄር ለዚህ አላማውን ያልለየ የፖለቲካ ኪሳራ የሚዳርግ የመጀመሪያው ምክንያት ነው፡፡ ብሄር ስስ፣ የፖለቲከኞች መጠቀሚያና እንደፈለገው የሚጠመዘዝ በመሆኑ ኢላማን ለመለየት እንዳይቻል ያደርጋል፡፡ በኢትዮጵያ ብሄርን  በቀዳሚነት የጀመሩ ሀይሎች  ተሸንፈዋል፡፡ ተሸንፈዋል ስንል ሀሳባቸውም ማለታችን ነው፡፡ ለብነት ያህል ለመጀመሪያ ጊዜ ብሄርን ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ይዞ ብቅ ያለው ጀብሃ አስከፊ ሽንፈት ከገጠማቸው ፓርቲዎች መካከል ቀዳሚው ነው፡፡ ይህ ፓርቲ በኤርትራና ኢትዮጵያ ህዝቦች መካከል ብቻ ሳይሆን ትግርኛ ተናጋሪውን የኤርትራ ህዝብ ሲከፋፍል ኖሯል፡፡ ለኤርትራ ችግር የገዥዎችን ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን ህዝቦች ራሱ ባስቀመጠው የብሄር ቁና እየሰፈረ ሁሉም ላይ ለመዝመት ሞክሯል፡፡ በአሁኑ ወቅት መሳሪያና ስንቅ ሲያስታጥቀው ከነበረው ህውሃት በታች የሆነው ሻቢያም በኢትዮጵያ ገዥዎች ብቻ ሳይሆን በአማርኛ ተናጋሪው ህዝብ ላይ የመረረ ጥላቻ የነበረውና  ኢላማውን መለየት ያልቻለ ፓርቲ ነው፡፡ ምንም ያህል ስልጣን ላይ ቢወጣም ሻቢያ ያኔ ‹‹ከአማራ ነጻነት አወጣችኋለሁ›› ብሎ ያታለላቸው ህዝቦችን ልብ መግዛት ባለመቻሉ አሁን በመሸነፍ ላይ ይገኛል፡፡ ከ30 በመቶው በላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ስም የተቋቋመው ኦነግ ከነገስታቱም ይሁን በጊዜው ከነበሩት ልሂቃን ይልቅ ‹‹አማራ›› መባሉን በማያውቀው ኢትዮጵያዊ ላይ ሁሉ በመዝመት ጊዜ፣ ጉልበቱንና አቅሙን አዳክሟል፡፡ ከምንም በላይ ወክየዋለሁ ከሚለው ኦሮምኛ ህዝብ ሳይቀር ይህ ህዝብን በጅምላ የማስጠላት ፖለሲው ላይ ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡ በየትኛውም አለም ሰፊ ህዝብ እወክላለሁ የሚል ፓርቲ አንድነትን በማጠናከር እንጂ በጠባብነት ሁሉ ላይ በመዝመት አይታወቅም፡፡ በጠባብ ብሄርተኝነት ተራው ህዝብ ላይ ሲዘምት የነበረው ኦነግም ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ለመውጣት ተገዷል፡፡ በቅርቡ ይህን ስህተቱን ያመነ የሚመስለው ኦነግ ህዝብ ላይ ሳይሆን አላማውን ልሂቃን ላይ በማድረግ በኢትዮጵያውይነት ማዕቀፍ ወደፖለቲካ መድረኩ እንደገና መመለሱ እየተነገረለት ነው፡፡
በብሄር ላይ የተመሰረቱ ፓርቲዎች የጊዜ ጉዳይ እንጂ መሸነፋቸው የግድ መሆኑን  ታሪክ ያስረዳል፡፡ ሶቬት ህብረትና ዩጎዝላቪያ በአንድ ወቅት ታላቅ ቢመስሉም በዚህ ኢላማውን በማይለይ የፖለቲካ ቀመር ምክንያት ተበታትነዋል፡፡ ሶቬት ህብረት በወቅቱ  አሜሪካን የምትገዳደር አገር ለመሆን ብትበቃም የኋላ ኋላ ተፈረካክሳ ግዛቶቿ ከአሜሪካ ስር ሆነዋል፡፡ ተከፋፍላ የነበረችው ጀርመን አውሮፓን መግዛት የቻለችው አንድ በመሆኗ ነው፡፡ የፋሽስትና ናዚ ፓርቲዎች  ኢላማ ለይተው ሳይሆን  በአለማቀፋዊ ‹‹የእኛ›› እና ‹‹እነርሱ›› ዘረኝነት ፖለቲካ ህዝብን ለጥቂት ጊዜ ማንቀሳቀስ የቻሉ ቢሆንም ሲሸነፉ ይከተሉት የነበረው ስርዓት የሚወገዝ፣ የሚናቅና የሚያስቀጣ ሆኗል፡፡ ጀብሃ፣ ሻቢያ፣ ኦነግ፣ ኦብነግ በብሄር ፖለቲካቸው ምክንያት ተሸንፈዋል፡፡ ህውሃት እስካሁን በሀይል ቢገዛም የሻቢያ መስራች ጀብሃ፣ ከዚያም የህውሃት አጋዥ ሻቢያ ክስረት ሽንፈቱ ወደማን እየመጣ ለመሆኑ ጠቋሚ ነው፡፡ ምን አልባት እነሻቢያ ብቻ ሳይሆን እነኢህአፓ፣ መኢሶንና የመሳሰሉትን አልተሸነፉም? የሚል ጥያቄ ሊቀርብ ይችል ይሆናል፡፡ ለእኔ የእነዚህ ፓርቲዎች ሀሳብ ሙሉ በሙሉ ጠፍቷል ማለት አልችልም፡፡ ከአሁን በኋላ ኢትዮጵያ እንጀብሃ፣ ሻቢያ፣ ህውሃት፣ ኦነግና ኦብነግ ያሉ ተገንጣይ ፓርቲዎችን ጸረ ኢትዮጵያዊ አቋም የምታስተናግድበት ቦታ ያላት አይመስልም፡፡ ለዚህም ህውሃት ለይስሙላህም ቢሆን የጀመረው የአገራዊ አንድነት፣ የኦነግ የስልት ለውጥ እና የአብዛኛዎቹ ሽንፈት ዋነኛ ማስረጃ ነው፡፡ ምንም እንኳ እነ መኢሶንና ኢህአፓ በፓርቲነት ባይኖሩም ጀምረውት የመነረውን ኢትዮጵያን ለክፉ የማይሰጥ ‹‹የብሄር›› ፖለቲካቸውን የአሁኑ ኢህአዴግ እንኳን አውን ሊያደርገው አልቻለም፡፡ ምን አልባት ከቀደም ፓርቲዎች ስህተት መማር ከቻሉ ተቃዋሚዎች የኢህአፓንና መኢሶንን አንዳንድ መስመሮች መፍታት የሚችሉ ይመስለኛል፡፡ በተለይ እነዚህ ቀደም ፓርቲዎች ብሄርን ከጠባብ ብሄርተኝነት ይልቅ ለአገር አንድነት  በሚጠቅም መልኩ  ለማዋል ጥረት  ማድረጋቸው የሚታወቅ ነው፡፡
በአሁኑ ወቅት ባለው ፖለቲካችንም አላማን ያልለየ ፖለቲካ ይስተዋላል፡፡ በእርግጥ ለዚህ ዋነኛ ምንጩ ህውሃት/ኢህአዴግ ነው፡፡ ህውሃት ትግርኛ ተናጋሪውን ህዝብ ከቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ በመነጠል ለመያዣነት እየተጠቀመበት ይገኛል፡፡ ይህም በብሄር ስም በተወናበደው ህዝብና በአንዳንድ ተቃዋሚዎች ዘንድ ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ ተጠቃሚ እንደሆነ ተደርጎ እየቀረበ ነው፡፡ ይህን ህውሃት ይፈልገዋል፡፡ ምክንያቱም ትግርኛ ተናጋሪውን ህዝብ ልብ ለማግኘትም ሆነ ሌላውን ለማሸነፍ የሚጠቅመው ይህ ስልት በመሆኑ ነው፡፡  የሌላ ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦችም ይወክሉናል በሚሉት ስር ከመስራት ውጭ በኢትዮጵያውነት ማዕቀፍ ለመታገል አማራጭ እንደሌላቸው ያምናሉ፡፡ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ውጭ ሌሎች ተቃዋሚዎች  በአገር ማዕቀፍ የሚታገሉ በመሆኑ በብሄር ስም የሚታገሉትም በመዳከማቸው የኢትዮጵያ ህዝብ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶችም ጎን ተስልፎ የአገሪቱን ኬክ ለመካፈል፣ ራሱን ለመከላከልና ለጥቅም እንዲቋምጥ ያደርገዋል፡፡ ማህበራዊ ድህረገጾችን ጨምሮ በአገር ውስጥ በሚደረገው ተቃውሞ ጠባብ ብሄርተኝነት የወለደውን እሳት በሌላ ጠባብ ብሄርተኛ እሳት ለመዋጋት የሚደረግ ጥላቻ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በንጉሳዊያኑ ዘመን  አማርኛ ተናጋሪ ህዝብ አልተጠቀመም ብለው የሚከራከሩ ሀይሎች በኢህአዴግ ዘመን ትግርኛ ተናጋሪው ህዝብ ተጠቅሟል ወደሚል መርህ አልባ ፖለቲካ እያዘነበሉ ነው፡፡ ህወሓት ከሌሎቹ ‹‹የኢህአዴግ አባል›› ድርጅቶች በላቀ መከላከያውን፣ ደህንነት፣ የውጭ ጉዳይ፣ ፍርድ ቤት በአጠቃላይም የኢትዮጵያን ተቋማ ይዟል፡፡ በእርግጥ ቅጥር በዘመድ አዝማድ፣ በጓድነት፣ በፖለቲካዊ ቅርርብ ነውና እነዚህ ሰዎች በርካታ ሰዎችን (የህወሓት አባላትን) ስበዋል፡፡ ይህ ከህወሓት የበላይነት እንጅ ትግርኛ ተናጋሪው ኢትዮጵያዊ እንደ ህዝብ ገዥ በመሆኑ የተፈጠረ አይመለኝም፡፡ በአሁኑ ወቅት ከህውሃት ጎን ባለመሆናቸው እንደሌሎች ኢትዮጵያውያን ጥቃት እየደረሰባቸው የሚገኙ ትግርኛ ተናጋሪዎች  የብሄር ፖለቲካ ለመጠቀሚያነት ብቻ እያገለገለ የሚገኝ ቀመር መሆኑ እየተዘነጋ ይመስላል፡፡ ይህ የኢህአዴግን ቀመር መጠቀም ኢህአዴግን እቃወማለሁ የሚል አካል ሁሉ ኢትዮጵያውያንን ወደ ብሄር ፖለቲካ በመግፋት የራሱን ሽንፈትና የኢህአዴግን ድል ማፋጠኑ የግድ ነው፡፡ በአንድ ወቅት በብሄር ሳይሆን በኢትዮጰያውነት ማዕቀፍ ይህን ብልሹ ፖለቲካ ሲታገል የነበረው የአውራምባው ዳዊት  ሌሎች ባደረጉበት ግፊት (የራሱ ጽናት ማጣትም ተጨምሮበት) የብሄር ፖለቲካውን እየታከከ ነው፡፡ ይህ የኢህአዴግ ቀመር ነው፡፡ ይህ ብሄርን መሰረት ያደረገና አላማውን ያልለየው ‹‹የእኛ›› እና ‹‹እነርሱ›› ፖለቲካ በኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈጥረው ሽንፈትን ብቻ ነው፡፡ የኢህአዴግ የብሄር ፖለቲካም የሚያሸንፈው ያኔ ነው፡፡

Tuesday 28 May 2013

ጋዜጠኛ ሙሉቀን ተስፋሁን ቤንሻንጉል-ጉምዝ ውስጥ ታስሯል

images (1)
“ኢትዮ-ምኅዳር” ለሚባለው ሣምንታዊ ጋዜጣ ከአማራ ክልል ሲዘግብ የቆየው ሙሉቀን ተስፋሁን በቤንሻንጉል-ጉምዝ ፖሊስ መያዙን የጋዜጣው ምንጮች አስታወቁ።ስለጋዜጠኛው እሥራት ከአካባቢው ፖሊስ መልስ ለማግኘት የተደረገው ሙከራ አልተሣካም። ሙሉቀን ከተያዘበት ዕለት ጀምሮ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ፍርድ ቤት እንዳልቀረበም የቅርብ ዘመዶቹ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገመንግሥት “የተያዙ ሰዎች በአርባ ስምንት ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት አላቸው” ሲል በአንቀፅ 19 ንዑስ አንቀፅ 3፤ “ማንኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት ሐሣቡን የመግለፅ ነፃነት አለው፤ ይህ ነፃነት በሃገር ውስጥም ሆነ ከሃገር ውጭ ወሰን ሳይደረግበት በቃልም ሆነ በፅሁፍ ወይም በሕትመት፣ በሥነጥበብ መልክ ወይም በመረጠው በማንሃውም የማሠራጫ ዘዴ ማንኛውንም ዓይነት መረጃና ሐሣብ የመሰብሰብ የመቀበልና የማሠራጨት ነፃነቶችን ያካትታል” ሲል በአንቀፅ 29 ንዑስ አንቀፅ 2 ያረጋግጣል፡፡ እንዲሁም በአንቀፅ 29 ንዑስ አንቀፅ 3 እና ንዑስ አንቀፅ 3/ለ የሚከተለው ሠፍሯል “3. … የፕሬስ ነፃነት የሚከተሉትን ሕጎች ያጠቃልላል…፤ …ለ/ የሕዝብን ጥቅም የሚመለከት መረጃ የማግኘት ዕድልን”
ጋዜጠኛ ሙሉቀን ተስፋሁን ዓርብ ግንቦት 16/2005 ዓ.ም ጀምሮ በቤንሻንጉል-ጉምዝ ክልል ዶቢ በምትባል የገጠር መንደር ፖሊስ ጣቢያ ታስሮ መቆየቱንና እስከዛሬም ማክሰኞ ግንቦት 20/2005 ዓ.ም ፍርድ ቤት አለመቅረቡን ቅርበት ያላቸውና ማንነታቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ ምንጮች ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡
በዶቢ ቀበሌ እሥር ቤት ውስጥ ሣለ ሙሉቀንን ባለቤቱና ወንድሙ ሄደው የጎበኙት ሲሆን ማክሰኞ፣ ግንቦት 20/2005 ዓ.ም ጠዋት ግልገል በለስ በተባለ ሥፍራ ወደሚገኘው የዞኑ እሥር ቤት መወሰዱን ምንጩ ጠቁመዋል፡፡
ሙሉቀን ለላከው “ኢትዮ-ምኅዳር” ጋዜጣ መረጃ በመሰብሰብ ላይ እያለ ፖሊሶቹ ጋዜጠኛ ለመሆኑ ማስረጃ እንዲያቀርብ ጠይቀውት ማሣየቱንና “በፖለቲካ ነው የምንፈልግህ” ብለው እንደወሰዱት፤ በአካባቢው የነበሩት ሰዎች “ለምን ትወስዱታላችሁ?” ብለው ሲጠይቁም “እናንተንም እናስራችኋለን” ብለው ያስፈራሯቸው መሆኑን ገልፀዋል፡፡

የአለም ባንክ እና ኢትዮጵያ ውዝግብ ውስጥ ገቡ

ላለፉት 20 አመታት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ከሞላ ጎደል ጥሩ የሚባል ግንኙነት የነበረው የአለም ባንክ በሀይል ከሚፈናቀሉ ዜጎች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ መግባቱ ታውቋል።
Image
ሂውማን ራይትስን ጨምሮ ሌሎች አለማቀፍ የሰብአዊ መብቶች ተከራካሪ ድርጅቶች የኢትዮጵያ መንግስት በጦር ሀይል በመታገዝ ከ45 ሺ በላይ የጋምቤላ ተወላጆችን በግዴታ ማስፈሩን ተቃውመው ነበር።
የአለም ባንክ አንድ ገለልተኛ ቡድን በማቋቋም ክሱን ለማጣራት ባለፈው ጥቅምት ወር እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ መንግስትም ከአጣሪ ቡድኑ ጋር እንደማይተባበር ይፋ አድርጓል።
የጠቅላይ ሚ/ር ሀይለማርያም ደሳለኝ ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ ጌታቸው አረዳ ከአጣሪ ቡድኑ ጋር እንደማይተባበሩ ዘገባውን ላወጣው ብሉምበርግ ገልጸዋል። “ከአለም ባንክ ጋር እንተባበራለን ነገር ግን አለም ባንክ ካቋቋመው አጣሪ ኮሚቴ ጋር አንተባበርም” ብለዋል ቃል አቀባዩ።
የአለም ባንክ አጣሪ ቡድን በመጀመሪያ ሪፖርቱ ባንኩ የሚሰጠው ገንዘብ ዜጎችን በሀይል ከማፈናቀል ጋር የሚያያዝ መሆኑን ማመልከቱ የኢትዮጵያን መንግስት ሳያስቆጣ አልቀረም።
የኢትዮጵያ መንግስት አጣሪ ቡድኑ በኢትዮጵያ ላይ  የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ከጀመሩት ከእነ ሂውማን ራይትስ ጋር ግንኙነት አለው ይላል።
አንድ የሰብአዊ መብት ድርጅት ተከራካሪ የአለም ባንክ አባል የሆነ አገር ባንኩ ካቋቋመው አካል ጋር አልተባበርም ማለቱ ያልተጠበ ነው በማለት ለብሉምበርግ ገልጸዋል።
የአለም ባንክ ” አትጠይቁኝ” የሚለውን የኢትዮጵያን  መንግስት ከዚህ በሁዋላ ሲረዳ አይታየኝም በማለት ባለስልጣኑ አክለዋል።
አትዮጵያ አምና ብቻ 3 ቢሊዮን 5 መቶ ሚሊዮን ዶላር ወይም ከ60 ቢሊዮን ብር  ያላነሰ ገንዘብ በእርዳታ አግኝታለች።
ትህዴን ሃይሉን ኣጠናክሮ ጠላቶቹን ሊቀጣ ተነስተዋል፣፣ የኢህኣዴግ ስርኣት የሚወድቀው በሰለማዊ ትግል ሳይሆን ራሱ በመረጠው በትጥቅ ትግል ስለሆነ፤ ኣንድነትን በመፍጠር እድሜ ጠላታችንን እናሳጥር የሚለው ትህዴን ድርጅት፤ ዛሬም በተጠናከረ ሁኔታ ጠላቶቹ ለመቅጣት ተነስተዋል፣፣ ይህ የሚታዩት ቪድዮ የምስራቅ ክ/ር ግንባር ሰራዊት ነው፣፣

ለብዙ ኢትዮጵያውያን ግንቦት 20 ካለፈው ይልቅ መጪውን የሚፈሩበት ጊዜ ነው

ጌታቸው, ከኦስሎ
ዛሬ ግንቦት 20 ነው።ግንቦት 20 የኢትዮጵያ የፖለቲካ መዘውር የተዘወረበት ለመሆኑ አሌ አይባልም። ዕለቱ እንደ አቶ ሃይለማርያም የመጀመርያ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ እንዳደረጉት ንግግር ” ኢትዮጵያ ልትበታተን ስትል የዳነችበት ቀን” ነው ለብዙ ኢትዮጵያውያን ግን ግንቦት 20 ካለፈው ይልቅ መጪውን የሚፈሩበት ጊዜ ነው።ይህንን ሁለተኛውን ሃሳብ እኔም እጋራዋለሁ። ካለፈው ይልቅ መጪው ይቀርበናል።ያለፈውማ አለፈ።መጪው ግን ቢዘገይም ቢፈጥንም አይቀርም።እና ግንቦት 20 ካለፈው ይልቅ ለመጪዋ ኢትዮጵያ እንዴት አስጊ ያደርገዋል። ይህንን ለማብራራት ግንቦት 20 እንደ ሀገር ለኢትዮጵያ ይዞት የመጣውን በጥቂቱም መጥቀስ ይፈልጋል።ስለተሰራው የመንገድ እርዝመት፣ህንፃ፣ወዘተ ማተት ይቻላል።እርግጥ ነው መንገድ ተስርቷል።ህንፃ ተገንብቷል።ከተሞች ሰፍተዋል።ይህ ሁሉ  ግን መጪውን አስፈሪ ጊዜ ለሀገር ከመተው አልገታውም።
መጪውን አስፈሪ የሚያደርገው የግንቦት 20 ውጤቶች ምን ምን ናቸው?
እንድሜ ለግንቦት 20 ብዬ ብጀምርስ-
  • እድሜ ለግንቦት 20 ዛሬ ኢትዮጵያ በአለም ታይቶ በማይታወቅ መልክ በቁጥር ተከልላ ክልሎች ስለ ድንበሮቻቸው ሲደራደሩ አንዳንዴም ሲጋጩ ለማየት በቅተናል። ምሳሌ የአፋር እና ትግራይ፣ የሱማሌ እና ኦሮሞ፣ የአማራ እና አፋር ወዘተ መጥቀስ ይቻላል።
  • እድሜ ለግንቦት 20 አንድሰው ከአንዱ የሃገሪቱ ክልል ተነስቶ እንበል ደቡብ ወይንም ጅጅጋ  ገብቶ መሬት ገዝቶ ልረስ ወይንም ልነግድ  ቢል እርሱ ከመምጣቱ በፊት ከ 60 እና 70 አመት በፊት የሰፈሩቱ ከጉርዳፈርዳ፣ጋምቤላ፣ጅጅጋ እና አሶሳ ካለምንም ካሳ ሲባረሩ ያያል እና መጪው እያስፈራው አይሞክረውም።
  • እድሜ ለግንቦት 20 ወላጆች ልጆቻቸውን በፈለጉት ቋንቋ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ ለማድረግ በታሪካዊ አጋጣሚ የሚኖሩበት ክልል ቋንቋ ውጭ እንዳይስተምሩ ታግደዋል።ለምሳሌ ኦሮምኛ ተናጋሪ ልጁ በአማርኛ እንዲማር ቢፈልግ ግን በኦሮምያ ክልል ቢኖር አማርኛ ወደምነገርበት ክልል መሄድ ብቸኛ አማራጩ ነው።በምዕራቡ አለም የሚኖር አንድ ኢትዮጵያዊ ግን ልጁን በሀገሩ ቋንቋ እንዲያስተምር ባህሉን እንዲጠብቅ ድጋፍ ይደረግለታል።
  • እድሜ ለግንቦት 20 ኢትዮጵያ ወደብ አልባ ሆና የባህር ኃይሏን በትና  30 እና 40 ኪሎሜትር እርቀት የባህሩ ማዕበል ሲማታ እየተሰማ ከ85ሚልዮን በላይ ሕዝብ ወደብ አጥቶ የጅቡቲን እና የሱዳንን ወደቦች በከፍተኛ ገንዘብ እንዲከፍል ተወስኖበታል፣
  • እድሜ ለግንቦት 20  ጦርነት ቆመ በተባለበት ጊዜ በአዲስ አበባ ብቻ ከ 100ሺህ በላይ ”ጎዳና ቤቴ” ያሉ ሕፃናት መንገድ ላይ ፈሰው ኃላፊነት የሚወስድ መንግስት አጥተው ለማየት የበቃነው በግንቦት 20 ፍሬ ነው። (በቀድሞው መንግስት የተመሰረተው የሕፃናት አንባ እንዴት በአሁኑ መንግስት እንደፈረሰ ይህንን ሊንክ ከፍተው ቪድዮውን ይመልከቱ (http://gudayachn.blogspot.no/2013/05/main-play-list-on-home-page-playlist.html)፣
  • እድሜ ለግንቦት 20 ከሃያ ሁለት አመት በፊት ”የጫት ቤት” ብሎ በር ላይ መለጠፍ የምያሳፍርባት አዲስ አበባ ዛሬ ጫት በየዘርፉ ”የበለጩ ፣የባህርዳር፣ የወልሶ ጫት ቤት” ብቻ ተብሎ ሳይሆን የሚለጠፈው ”ጫት እናስቅማለን፣ እንፈርሻለን” ተብሎ የተፃፈባቸው ባብዛኛው ትምህርት ቤቶች የሚገኙበትን ቦታ ፈልገው የሚከፈቱ የጫት ቤቶች በዝተው ለመታየት በቅተዋል። ምን ይህ ብቻ ዩንቨርስቲዎቻችን በየዶርሙ ጫት ሸጉጠው ሲገቡ- ሲ ቃምባቸው ደጉ መንግስታችን በዝምታ አልፎ ትውልዱን ጫት ቃሚ አድርጎታል።
  • አድሜ ለ ግንቦት 20 ምሳ ሰዓት ላይ ከቢሮ ወጥተው ጫት ቅመው የሚመለሱ የባንክ ሰራተኞች፣መሀንዲሶች ወዘተ አፍርቷል ግንቦት 20።ከደንበል ህንፃ ጀርባ የሚገኙ የመቃምያ ቦታዎችን ብንመለከት በምሳ ሰዓት ደንበል ህንፃ የሚሰሩ ምሁራን ዩንቨርስቲ ሳሉ በተፈቀደላቸው የመቃም መሰረት ሥራ ከያዙ በኃላም ለመላቀቅ ትቸግረው ይታያል።እረ  እንዲያውም በሥራ ሰዓት ሾለክ ብለው የሚቅሙ ሰራተኞች መኖራቸውን የእዚህ ፅሁፍ ፀሐፊ እማኝ ነው። እድሜ ለግንቦት 20።
  • እድሜ ለግንቦት 20 ወላጅ አልባ ሕፃናት ጎዳና እንዳይወጡ በሕዝቡ የሚደገፍ እንደ ሕፃናት አምባ መስርቶ ከማሳደግ ይልቅ ለአንድ ሕፃን እስከ 25000 ዶላር መንግስት እየተቀበለ በጉዲፈቻ ስም ለአሜሪካ እና አውሮፓ የተቸበቸቡት እና ብዙዎች በህሊና ስቃይ እና የማንንነት ጥያቄ እንዲሰቃዩ የተደረጉት በግንቦት 20 ፍሬ ነው (ሰኔ 25/2012 እአአቆጣጠር  በቢቢሲ ድህረ ገፅ ላይ በወጣ አንድ ዘገባ መሰረት ኢትዮጵያ በአመት 5ሺህ በላይ ሕፃናት በማደጎነት ወደ አሜሪካ  ብቻ እንደሚሄዱ  እና አሜሪካ ከዓለም ላይ በማደጎነት ከምትወስደው ሕፃናት ኢትዮጵያውያን ሕፃናት ከ አምስቱ አንዱ እንደሆኑይገልፃል።(http://www.bbc.co.uk/news/world-africa-18506474)
  • እድሜ ለግንቦት 20 ሴት እህቶቻችን ተስፋ ቆርጠው ለአረብ ሀገር ባርነት  በአስርሺዎች የተጋዙት በሄዱበት ሀገርም ስበልደሉ የሚሰማቸው አጥተው አሳር ፍዳቸውን የሚያዩት ከግንቦት 20 ፍሬ ወዲህ ነው።
  • እድሜ ለግንቦት 20 ”የኤርትራ ጥያቄን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መፍታት የሚቻለው የ ሻብያን ሃሳብ በመቀበል ነው” ብለው ስያግባቡን የነበሩት  አቶ መለስ- ጦርነቱ አበቃ ከተባለ ከ ሰባት አመታት በኋላ ለዳግም እልቂት ”ድንበር” በሚል ሰበብ ዳግም የኢኮኖሚ ፀባቸውን ወደ ወታደራዊ ግጭት ቀይረው በአስር ሺዎች የረገፉት በ ግንቦት ሃያ ውጤት ነው፣
  • እድሜ ለግንቦት 20 ስደት ቀድሞ የነበረ ቢሆንም በከፍተኛ ተስፋ መቁረጥ በባህር፣በእግር ወዘተ ወጣቱ ከሀገር የሚወጣው ከግንቦት 20 ፍሬ ወዲህ ነው (ወደየመን በጀልባ ተሳፍረው ከገቡት ስደተኞች ከ 70%በላይ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ኮሚሽን በዘንድሮው ዘገባው መጥቀሱን ልብ በሉ) ፣
  • እድሜ ለግንቦት 20 ወጣቶች ተምረው በእውቀታቸው ሀገርንም መጥቀም ሲገባቸው፣የስራ ዕድል የሚያገኙበት ወይንም  ስነልቦናቸውን የሚጠብቅ ግን ለፈጠራ የሚያዘጋጅ የስራ መስክ ከመፍጠር ይልቅ በምረቃቸው ጊዜ (የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ  2004ዓም ምረቃ ላይ አቶ ጁነዲን ለተማሪዎቹ እንደተናገሩት)ከዩንቨርስቲ ሲወጡ  የኮብል ስቶን ሥራን መስራት እንደሚገባ የተነገራቸው በግንቦት 20 ውጤት ነው።
  • እድሜ ለግንቦት 20 በሚድያውስ ቢሆን (ጎረቤት ኬንያን ለማነፃፀርያ እንጠቀም) ኬንያ የህዝብ ብዛቷ 30 ሚልዮን ሲሆን እኛ 85 ሚልዮን መሆኑን እናስታውስ እና ኬንያ በይዘታቸውም ሆነ በአቀራረባቸው የመንግስት እጅ ያልተጫናቸው 8 የቴሌቭዥን ጣቢያ፣ 38 ራድዮ ጣብያዎች፣ ከእሩብ ሚልዮን በላይ አንባቢ ያላቸው በየቀኑ የሚታተሙ 4 ጋዜጦች (http://www.pressreference.com/Gu-Ku/Kenya.html#b) ሲኖሩ ሃሳብን የመግለፅ መብት እና በሀገሪቱ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ የመወያየት ነፃነት ከእኛ ጋር ሊወዳደር የማይችል መሆኑን ስናስብ እና ጋዜጠኞች መንግስትን ወቀሱ ተብለው በአሸባሪነት ዘብጥያ መውረዳቸውን ስናስብ እድሜ ለግንቦት 20 እንላለን።
  • እድሜ ለ ግንቦት 20 ጋና ነፃነቷን ስታገኝ የገነባነው ስታድዮም ዛሬ ጋና ከነፃነት አልፋ እስከ መቶ ሺሕዝብ የሚይዝ ስታድዮም ስትገነባ እኛ አሁንም አንድ ለእናቱ በሆነ ስታድዮም መገኘታችን የግንቦት 20 ውጤት ነው።እርግጥ ነው በዛሬው የግንቦት 20 በዓል የስፖርት አካዳሚ ምረቃ በአል እየተከበረ ነው። ስታድዮምስ ?
  • እድሜ ለግንቦት 20 ቀድሞ ጉቦ የሚለው ቃል ሲነሳ ስለ 20 እና 30 ብር ጉቦ እናስብ ነበር። ዛሬ ጉቦ፣ሙስና እና ዝርፍያ ማለት አድገው ተመንድገው  ዝርፍያ ማለት የብሔራዊ ባንክን የወርቅ ክምችት በወርቅ መሰል ነገር መቀየር ሲሆን ጉቦ ማለት ደግሞ የሀገር መሬት እና ውሃን  ለሕንድ እና ለአረብ በርካሽ መቸብቸብ ፣ በባለስልጣናት ቤት እንደባንክ ቤት በኢይሮ ብሉ በዶላር ቢሉ በፈለጉት የገንዘብ አይነት ከቤት ማስቀመጥ ማለት ነው (በቅርቡ የግምሩክ ባለስልጣናት ቤት  ተገኘ የተባለውን ብር ያስታውሱ)።
ይህንን ሁሉ ስናስብ ነው እንግዲህ ግንቦት 20 ካለፈው ይልቅ መጪውን የሚያስፈራ የሚያደርግብኝ።ከሁሉ የከፋው ግን መንግስት ስለሰራሁት መንገድ እና ድልድይ ስታመሰግኑኝ መስማት ብቻ ነው የምፈልገው ከማለቱም በላይ መሰረታዊ ስህተቶችን ”የጨለምተኞች አመለካከት’፣ የአመለካከት ችግር” እያለ ማጣጣሉን መቀጠሉ ነው አሳዛኙ።

የትም የተፈጨ ዱቄት አንበላም – ታሪካዊ ደብዳቤ – በፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም

…..“የትም ፍጭው፣ ዱቄቱን አምጭው” የሚሉ አይጠፉም፡፡ ግን ዱቄቱ የሚፈጭበት መጅና ወፍጮ ንፅህና፣ የሚፈጭበት ቤት ነዋሪዎች ጤንነት፣ ….. የእንጀራውን ጣእምና ተበይነት ይወስነዋል፡፡ ህይወት የትም የተፈጨ ዱቄት የሚበላበት ዘመን አይደለም፡፡ ያልፈጩትን እህል ከውርደት ጋር በልቶ ከመኖር በረሃብ መሞት ይሻላል፡፡ በኩራት ኖሮ፣ በኩራት ካልተሞተ ህይወት ሌላ ምን ትርጉም አለው?
በ1995 አእ የስዊስ መንግስት 10ሺ ዶላር ለኢሰመጉ ከሰጠ በኋላ፣ በገንዘቡ ዋጋ ኢሰመጉን መግዛት የሚችል መስሎት፣ “ኢሰመጉ ባወጣው ዘገባ መንግስትን ያለአግባቡ ነቅፏል” በማለት ኢሰመጉን አወገዘ፡፡ በጊዜው የኢሰመጉ ሊቀመንበር የነበሩት ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም የሚከተለውን ደብዳቤ ለስዊሱ አምባሳደር ጻፉለት፡፡ ደብዳቤው የተጻፈው በእንግሊዘኛ ነበር፡፡ ግን የተጠቀሰውን የሼሊን ውብ ግጥም በአማርኛ ማንበብ ስለፈለግሁ ደብዳቤውን በሙሉ ወደ አማርኛ ተርጉሜዋለሁ፣ ለሚገኘው የትርጉም ስህተት አስቀድሜ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡
ይህ ታሪካዊ ደብዳቤ፣ ኢትዮጵያውያን የትም የተፈጨ ዱቄት እንደማንበላ በግልፅ የሚያሳይ ነውና ህፃናትም በቃላቸው ሊያጠኑት ይገባል፡፡
ኦክቶበር 9. 1995
ለክቡር ዶክተር ፒተር አ.ሽዋይዘር
የስዊዘርላንድ አምባሳደር
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
ክቡር ሆይ
ምናልባት፣ (ደብዳቤዬን) በሼሊ “የፍቅር ሽሽት” መጀመሩ ተገቢ ሳይሆን አይቀርም፡፡
ፋኖሱ ሲተረከክ
          የአቧራ ላይ ብርሃን ያከትማል
ደመናው ሲበተን
          የቀስተ ደመናው ግርማ ይነጥፋል
ዋሽንቱ ሲሰበር
          ጣፋጭ ድምፆች ይተናሉ
ከንፈሮች ተናግረው ሲያበቁም
          የፍቅር ቃናዎች ይረሳሉ፡፡
ከአምባሰደሮች ሁሉ የላቁ የኢሰመጉ ወዳጅ እንደነበሩ አለመርሳታችንን (በቅድሚያ) ላረጋግጥልዎ እወዳለሁ፡፡ ቀደም ሲል የሞራል ድጋፍ እንዳደረጉልንም አልረሳንም፡፡ ለዚያም ውለታው አለብን፡፡
ከኢሰመጉ ጋር ያለዎት የቅርብ ግንኙነት ሳይሆን አይቀርም የትስስሩ ጥንካሬ በዚህ አጋጣሚ ለፈተና የተጋለጠው፡፡ ትስስሩም ደካማ መሆኑ በግልጽ ታወቀ፤ እንዲያም ሆኖ የመታውን ማእበል መቋቋም ተሳነው፡፡ ለመርህ የነበረንን አክብሮት ትተን በነበረን የጋራ ስሜት ምን ያህል መልካም እንደሠራን መገንዘቡ ከኛ ይልቅ ለክቡርነትዎ ግልፅ ነው፡፡ ክቡርነትዎ 10000 ዶላር የሚገመት ሃብት የማባከን ስሜት እንደተጫጫነዎ ያስታውቃል፡፡ ለዚህም የብክነት ስሜትዎ ማካካሻ ብሄራዊ ራታችንን፣ ሰብአዊ ክብራችንን እና ለመርህ ያለንን ተገዥነት እንድንሸጥልዎ ያደረጉት ሙከራ ምን ያህል እንዳስቆጣን ክቡርነትዎ ሊገነዘበው ይገባል፡፡ እንደ ሸክስፒር አባባል፣ ጣፋጭ ነገሮች በምግባራቸው ወደ ኮምጣጣነት ይቀየራሉ፡፡
በመንፈስ ደሃ እንዳልሆንን ክቡርነትዎ አይጠራጠሩም፡፡ ገንዘብዎን ለመመለስ ረዥም ጊዜ ስለወሰደብንም ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡ውግዘት ከኢሰመጉ የባንክ መዝገብ ህገወጥ እገዳ ጋር ተጣምሮ መምጣቱን ክቡርነትዎ ያውቀዋልና፡፡ ሆኖም፣ የኢትዮጵያ ህዝብ ከኢሰመጉ ጎን በመሰለፍ ገንዘቡን በሙሉ እንድከፍል ስላስቻለን ደስ ብሎናል፡፡ ቼኩን ከዚህ ደብዳቤ ጋር አያይዘን ልከናል፡፡
ከመልካም ምኞት ጋር
አክባሪዎ
መስፍን ወልደ ማርያም
የኢሰመጉ ሊቀመንበር
——–

አምሃ አስፋው በገብረክርስቶስ ደስታ ግጥሞች (መንገድ ስጡኝ ሰፊ) ላይ ካቀረቡት ዳሰሳ ላይ ከ”አንድምታ መጽሔት”  የተቀነጨበ /1999ዓ.ም/
source:/henoksitotaw.blogspot

አቶ ስብሐትና የተንኮል ፖሊቲካ በፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም (መነበብ ያለበት)

ጥቅምት 2005
አቶ ስብሐት ነጋ ሙሉ ነጻነቱን የሚወድ ሰው መሆኑን አደንቅለታለሁ፤ አስቦም ይሁን ሳያስብ አንደልቡ የመናገር ባሕርይ አለው፤ በበኩሌ ይህንን ባሕርዩንና በመብቱ መጠቀሙን አከብርለታለሁ፤ ሀሳቡ የተሳሳተ ይሁንም አይሁንም፣ እኔ የምስማማበት ሆነ አልሆነም፣ እኔ ልቀበለውም አልቀበለው ስብሐት ነጋ በሙሉ ነጻነቱ ተጠቅሞ ሀሳቡን ሁሉ መግለጹን አከብርለታለሁ፤ እሱም የእኔን ሀሳብ የመግለጽ ነጻነት አንደሚያከብርልኝና እንደሚያስከብርልኝ ተስፋ አለኝ፤ ከዚያም በላይ ነጻነት ሁልጊዜም፣ የትም ቦታ ከኃላፊነት ጋር የተቆራኘ መሆኑን እንድንገነዘብ ያሻል፤ ኃላፊነት የሌለበት ነጻነት የለም፣ ኃላፊነት የሌለበት ነጻነት ስሙ ሌላ ነው፡፡
በቅርቡ አቶ ስብሐት በአደረገው ቃለ መጠይቅ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር የተሾመው ወያኔ ዱሮም አስቦበት ወንበሩን ከአማርኛ ተናጋሪዎችና ከኦርቶዶክስ አማኞች ለማጽዳት በተዘጋጀበት እቅድ ነበር ብሎአል፤ ልብ ላለው አነጋገሩ በሁለት በኩል ስለት ያለው ቂል የያዘው ሰይፍ ነው፤ ከፊት ለፊት የተሰነዘረው አማርኛ ተናጋሪውንና የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አማኙን ለመምተር ነው፤ ቂል የሚያደርገው አማራ የሚባል ጎሣ ቢኖርም የኦርቶዶክስ ሃይማኖት በአማርኛ ተናጋሪዎች ታጥሮ ትግሬንና ኦሮሞን፣ ወላይታንና ጉራጌን፣ ሌሎችንም የማይነካ መስሎት ከባድ ስሕትት ላይ መውደቁ ነው፤ ከሁሉም በላይ እሱን የሚያህል ሰው የተክለ ሃይማኖትን ታሪክ አለማወቁ ያሳዝናል፡፡
አማራንና የኦርቶዶክስ ተከታዮችን መትሮ ሲመለስ ደግሞ ሰይፉ የሚቀላው ወላይታንና ጴንጤነትን፣ ምናልባትም እስልምናን ይሆናል፤ አማራን ለመምተር ተነሥቶ ሌላውን ስንቱን ቀላው! እስልምናን በጥርጣሬ ያስገባሁት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እስላም ነው የሚባል ያልተጣራ ወሬ በመስማቴ ነው፡፡
አቶ ስብሐት በፊት ለፊት የተናገረው ገና የዛሬ ሀያ አንድ ዓመት ‹‹እንዳያንሰራራ አድርገን አከርካሪቱን እንሰብረዋለን›› ተብሎ ያለቀለትን አማራ ዛሬ ወንበር ማጣቱን ለማብሰር አልነበረም፤ ይህ በጣም ግልጽና ከማንም ያልተሰወረው እውነት ነበር፤ ስውር ዓላማም አለው፤ ያንን ብዙ ሰው አይገነዘበውም ይሆናል፤ በአቶ ስብሐት አነጋገር ውስጥ ዋናውና ተንኮልን ያዘለው ዓላማ ወንበሩን የያዘው ዋናው የወላይታ ጴንጤ ሲሆን ምክትሉ ደግሞ እስላም መሆናቸውን ለመናገር ያለው ፍላጎት ላይ ነው፤ ከአቶ ስብሐት ነጋ በቀር የአዲሶቹን ሹሞች ዘርና ሃይማኖት ከጉዳይ ያስገባ ያለ አይመስለኝም፤ አቶ ስብሐት በፊት-ለፊት ዓላማው ተስፈንጣሪ ተራማጅ ሲመስል በስውሩ የተንኮል ዓላማው ግን ኋላ-ቀር ወግ-አጥባቂ ይሆናል፤ በዘርና በሃይማኖት ላይ ሲያተኩር ዋናውን ቁም-ነገር ጠቅላይ ሚኒስትሩና ምክትሉ ሰዎች፣ ከዚያም ቀጥሎ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን ፈጽሞ ዘንግቶታል፤ ለእኛ ትልቁ ነገር ይህ ነው፤ በሁለታችን መሀከል ያለው ልዩነት ስብሐት ኢትዮጵያውያንን የሚያዛምዳቸውን ሁሉ አያይም፤ እኔ ደግሞ ኢትዮጵያውያንን የሚለያያቸውን ሁሉ አላይም፡፡

Wednesday 22 May 2013

ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት የ ‹‹ሰማያዊ›› ፓርቲ ሊቀመንበር ከላይፍ መጽሄት ጋር ያደረጉት ቃለ መጠይቅ



ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት የ ‹‹ሰማያዊ›› ፓርቲ ሊቀመንበር ናቸው፡፡ ፓርቲው ከተመሰረተ ጥቂት እድሜ ያስቆጠረ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች የሚነሳ ለመሆን በቅቷል፡፡ የላይፍ መጽሄት አዘጋጅ የሆነው ዳዊት ሰለሞን ግንፍሌ አካባቢ በሚገኘው የፓርቲው ጽ/ ቤት በመገኘት ኢንጅነሩን በዋናነት ስለ አማሮች መፈናቀል አነጋግሯቸዋል፡፡

Interview Eng. Yilkal Getnet
ላይፍ ፡- ለፖለቲካ ስራ ሙሉ ጊዜን መስጠት በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ አስቸጋሪ አይሆንም?
ኢንጅነር ይልቃል ፡- መኖር ስላለብኝ ጥቂት ስራ እሰራለሁ፣ የሚበዛውን ጊዜዬን ግን የማሳልፈው ለፓርቲው ስራ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ነገሮች ለምርጫ አስቸጋሪ ሲሆኑ የምትወስደው ውሳኔ አንዱን በማጠፍ ለአንደኛው ብቻ ራስህን መስጠት ይሆናል፡፡
ላይፍ ፡- የሚመሩት ፓርቲ ሰማያዊ የፖለቲካ ፍልስፍናው በምን ላይ የተመሰረተ ነው?
ኢንጅነር ፡- ጥያቄው ሰፋ ያለ ነው፡፡ በዋናነት ግን የፖለቲካ ፍልስፍናችን በግለሰብ መብት ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ሴንተር ራይት ሞደሬት ሊበራሊዝምን የፖለቲካ አመለካከት እናራምዳን ብለን ነው የምናምነው፣ የግለሰብ መብት ከተከበረ የሁሉም መብት ይከበራል እንላለን፣ መብት ከግለሰብ ይጀምራል፡፡ ለምሳሌ ይልቃል ወንድ ነው ስለዚህ ጾታ አለው፣ ይልቃል ቋንቋ፣ ትምህርትና ሞያ ያሉት በመሆኑ ሌላ የተለየ ነገር አያስፈልግም፡፡ የእኔ መብት ከተከበረ የምናገረውም ቋንቋ ይከበራል ማለት ነው፡፡ ቡድንና ግለሰብ እኩል ይታያሉ የሚለው አመለካከት ምክንያታዊ አይደለም፡፡ ከቡድን በፊት ግለሰብ ይቀድማል፡፡ እናም የግለሰቡ መብት ሲከበር የቡድኑ ይከበራል ብለን እናምናለን፡፡ የፖለቲካ ድርጅት በየጊዜው ራሱን እያረመ የሚሄድ እንጂ በቅድመ ድንጋጌ ላይ ተመስርቶ ፖለቲካ ሊሰራ አይችልም፡፡ ለምሳሌ የጎሳ ድርጅት እንጂ የጎሳ ፓርቲ መሆን አይቻልም፡፡ እዚህ አገር ጉዳዩ በጣም ስስ በመሆኑ አንነካውም እንጂ አንድ ሰው የኦሮሞ ድርጅት ነኝ ብሎ ከተነሳ ከኦሮሞ ወዴት መሄድ ይችላል? ምክንያቱም ከመነሻው የተወሰነ ነው፡፡ በጎሳ መደራጀት አሁን እየተፈጠሩ ያሉ ነገሮች መነሻ ነው ብለን እናምናለን፡፡ በቡድን መብቶች መከበር እናምናለን፡፡ ነገር ግን የሁሉ ነገር ማጠንጠኛ በኢትዮጵያችን ውስጥ ጎሳ መሆን ይገባዋል የሚል አመለካከት የለንም፡፡
ላይፍ ፡ ገዢው ፓርቲ ዜጎችን ከመደራጀት ውጪ የማያውቅ የማይመስልበት ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ነው፡፡ የፌደራል ስርዓቱም ክልላዊነት፣ ቡድናዊነትና መንደርተኝነት እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል በማለት የፖቲካ ምሁራን ይተቻሉ፡፡ እናንተ ደግሞ የሁሉ ነገር መነሻ ግለሰብ ነው እያላችሁ ነው፡፡ እነዚህ ጫፎች እንዴት ይታረቃሉ?
ኢንጅነር ፡- ፖለቲካ ለጊዜው በሚፈጠር ንፋስ የሚነሳ መሆን የለበትም፡፡ ሩቅ አሻግረህ በማየትም አሰላለፍህን መቅረጽ ይኖርብሃል፡፡ ጎሰኝነት እዚህ አገር ውስጥ ከሰፋ አንተ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብለህ ብትሄድ ተቃውሞ ሊያጋጥምህ ይችላል፡፡ ይህ በመሆኑ ግን በቃ በማለት ነገሩን ተቀብለህ እንድትሄድ ሊያደርግህ አይገባም፡፡ የጎሰኝነት አመለካከት የመጣው ከቅኝ ገዢዎች ጋር ተያይዞ ነው፡፡ ቅኝ ገዢዎች ተገዢዎቹን ከፋፍለው ለመግዛት ያመቻቸው ዘንድ ተጠቅመውበታል፡፡ እንግሊዞች በዚህ መንገድ ብዙ ርቀት መጓዝ ችለዋል፡፡ ነገር ግን አሁን ይህ አመለካከት ስልጣንና አቅም ያገኘ በመሆኑ አገር እያተራመሰ ይገኛል፡፡ ምንም እንኳን የእኔ እበልጥ የእኔ እበልጥ ፉክክር ነግሶ አገራችንን ሊያጠፋብን የተቃረበ ቢሆንም የግለሰብ መብት መከበር ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል በማለት እየታገልን እንገኛለን፡፡ ኢትዮጵያዊያን ታላቅ ነበርን፣ ኢንተርኔት ውስጥ ገብተህ ስለ ኢትዮጵያ ለማወቅ ብትፈልግ ከአለማችን ጥንታዊ ህዝብ አንዷ ስለመሆኗ ትገነዘባለህ፡፡ ይህ የጎሳ አመለካከት ግን አሁን የተፈጠረና የቅርብ ጊዜ ታሪክ ነው፡፡ህዝቡ ወደቀደመው ታላቅነቱ መመለስ ይኖርበታል፡፡
ላይፍ ፡ – የነበረንን ብሔራዊና የአንድነት መንፈስ ያላላና ወደ ቡድናዊነት እንድናዘነብል ያደረገን ነገር በአንተ ዕይታ ምንድን ነው?
ኢንጅነር ፡- አንዳንድ ሰው ደርግን ብሔራዊ ስሜት የነበረው በማለት ሲያቀርበው እገረማለሁ፡፡ ደርግ አለም የወዛድሮች ትሆናለች የሚል አመለካከት ነበረው፡፡ ኢትዮጵያዊነት በአለም አቀፋዊ ወዛደራዊነት ጥላ ስር ገብቶ ነበር፡፡ ኢህአዴግ የደርግን አለም አቀፋዊ ወዛደራዊነት በብሔር ብሔረሰቦች ለወጠው፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ ይህንን አመለካከቱን ለማስረጽ በብዙ ነገሮች ላይ ዘምቷል፡፡ እኔ ዩኒቨርስቲ የገባሁት ኢህአዴግ ስልጣን በያዘበት ወቅት ነበር፡፡ በትምህርት ቤት ይሰጥ የነበረን የታሪክ ትምህርት አፋለሰ፣ ትልቅ ክብር ይሰጣቸው የነበሩ መመህራንን ከዩኒቨርስቲዎች እንዲባረሩ አደረገ፣ ከዚያ በመቀጠልም በኢትዮጵያ ውስጥ ትልቅ ትርጉም የነበረውን ሽምግልና አጠፋ፡፡ ሕዝቡ ሃይማኖተኛ በመሆኑ ለሃይማኖቱ ላቅ ያለ ግምት ይሰጣል፣ ኢህአዴግ በዚህ ዙሪያ ያሉ ሰዎችን በመያዝ የሃይማኖት ቤቶችን በካድሬዎች እንዲሞሉ አደረገ፡፡ የአገሪቱ አንኳር ነገሮችን በመያዝ ሚዲያውን በመቆጣጠር ለህዝቡ ውሸት መመገብ ጀመረ፡፡ እንግዲህ በዚህ ውስጥ ያለፈ አንድ የ20 አመት ወጣት ታሪክ፣ ሃይማኖት፣ ሽምግልና እና ትምህርት ከሌለው እንዴት ማንነቱን ማግኘት ይችላል? በእነዚህ ነገሮች ላይ በአቋም ደረጃ ተዘምቷል፡፡ የአገሪቱ ምሰሶ የነበሩ ነገሮች አሁን በቦታቸው አይገኙም፡፡ በአንድነት ውስጥ የነበረን ህዝብ በጎሳው እንዲሰባሰብ በማድረግ በህዝቡ መካከል አለመተማመን እንዲሰፍን ተደርጓል፡፡ የፖለቲካው ዋነኛ ኃይል ደግሞ ከጥቅም ጋር እንዲተሳሰር በመደረጉ አንድ ሰው ለምን ኢህአዴግ እንደሆነ ብትጠይቀው ምላሽ አይሰጥህም፡፡ ምክንያቱም ወደዚያ የሚሄደው የስራ ዕድል፣ የትምህርትና ሌሎች ጥቅሞችን እንደሚያገኝ የሚሰበክ በመሆኑ ነው፡፡ ብሔራዊ ስሜት የምንለውን ነገር ይህ መንግስት ያሳሳው በአጋጣሚ ሳይሆን ሆን ብሎ አስልቶ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡
ላይፍ ፡- ነገር ግን ኢህአዴግ የመንግስትነቱን ሚና መጫወት ከጀመረ ወዲህ ማንነታችን ተከበረ፣ በራሳችን ቋንቋ መናገር ጀመርን የሚሉ ቡድኖች ተፈጥረዋል፡፡ ኢህአዴግም የደርግን የአንድነት ፍልስፍና በመተቸት በልዩነታችን ውስጥ አንድነታችን እንዲወጣ አድርጊያለሁ ይላል፡፡
ኢንጅነር ፡- እኔ ምን እንደተገኘ አይገባኝም፡፡ በቋንቋ መናገር የሚባለውም ነገር አዲስ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ደቡብ ኢትዮጵያ ብትሄድ ህዝቡ በአማርኛ ሲናገር ታገኘዋለህ፡፡ አማርኛን ድሮ ይናገር ከነበረው ህዝብ አሁን የሚበልጠው ይናገረው እንዲሆን እንጂ አያንስም፡፡ መጻህፍት ከድሮ ይልቅ አሁን በአማርኛ በብዛት ይጻፋሉ፡፡ ድሮ ብዙ መጽሔት አልነበረም፡፡ አሁን ግን በዛ ያሉ መጽሄቶችን በአማርኛ ማግኘት ይቻላል፡፡ የተወሰኑ የየጎሳዎቹ ልሂቃን የራሳቸውን ጥቅም በማግኘታቸው ብቻ ካልሆነ በስተቀር አዲስ ነገር ተፈጥሯል የሚል ግምት የለኝም፡፡ ኦሮምኛ እኮ በኢህአዴግ ዘመን አልተፈጠረም፡፡ ድሮም ይነገር ነበር፡፡ ነገር ግን ቋንቋውን ለማስፋፋት የላቲን ፊደል ከመጠቀም የግእዝ ፊደልን ብንጠቀም ይሻል ነበር፡፡ ኢህአዴግ ሆን ብሎ ቅኝ ገዢዎች እንዳደረጉት ህዝቡን ለመግዛት እነዚህን ነገሮች ተጠቅሞባቸዋል፡፡ ኢህአዴግን በመጠጋት በአንድ ሌሊት ሚልየነር የሆኑ ሰዎች አሉ፡፡ ግን ደሀው ኢትዮጵያዊ ኦሮምኛ፣ አማርኛ ወይም ሲዳምኛ ይናገር የእርሱ ችግር አይደለም፡፡ ከስንዝር መሬቱ ጋር ተጣብቆ ከመኖር ውጪ ጠብ ያለለት ነገር የለም፡፡ ድሮም ገጠር ውስጥ ኦሮምኛ ይናገር ነበር አሁንም ይናገራል፡፡ ድሮም የከለከለው የለም፣ አሁንም ምንም አላገኘም፡፡ ተራ ፕሮፓጋንዳ እንጂ መሬት የያዘ ምንም ነገር የለም፡፡
ላይፍ ፡- ክልሎች የራሳቸውን አስተዳደር መርጠው ህግ በማውጣት እንዲተዳደሩ ስለመደረጋቸው ይነገራል፡፡ ማዕከላዊ የነበረው የመንግስት አወቃቀር ፌደራላዊ በመሆን ስልጣኑን ለክልሎች መስጠቱን ሰማያዊ ፓርቲ የሚመለከተው እንዴት ነው?
ኢንጅነር ፡- የፌደራል ስርዓት በራሱ መጥፎ አይደለም፡፡ እኛ ኢትዮጵያዊያን ለፌደራል አስተዳደር አዲስ አይደለንም፡፡ በየክልሉ ከድሮ ጀምሮ አስተዳዳሪዎች ነበሩ፡፡ ከ90 ሚልዮን ህዝብ በላይ የሚገኝባትን አገር በአሀዳዊ አስተዳደር ለመምራት መሞከር ትልቅ ችግር ነው፡፡ ክልሎች የራሳቸውን አስተዳደር በመመስረት ስልጣን ከማዕከላዊው መንግስት መጋራታቸው ጥሩ ነገር ነው፡፡ ችግሩ ግን ህዝቡን በጎሳ ከረጢት ውስጥ በመክተት በመከራውና በደስታው ወቅት አንድ የነበረውን ህዝብ ማለያየት ነው፡፡ ዘውዴ ነሲቡ የሚባሉ ሸዋ ውስጥ 130 አመት ኖረው ያረፉ ሰው ሲናገሩ ‹‹እርሱ የሲዳማ፣ የጎጃምና የወለጋ ሰው ነው›› ይሉ ነበር፡፡ ያኔ ሰውን በጎሳው ሳይሆን በሚኖርበት አካባቢ ባለው ተቀባይነት በመነሳት ይጠራ እንደነበር መረዳት እንችላለን፡፡ እኛም ብንሆን የፌደራል ስርአቱን በመቀበል የየክልሉ ሰዎች ክልላቸውን ያስተዳድሩ መባሉን እንደግፋለን፡፡ ድሮም እኮ የሸዋ፣ የትግሬ፣ የኦሮሞ ንጉስ የሚባሉ ነበሩ፡፡ እነዚህ የየክልሉ ንጉሶች የነበሩ ቢሆንም ለንጉሰ ነገስቱ ይገብሩ ነበር እንጂ እንገነጠላለን አይሉም፡፡ ቴክኖሎጂው ባልነበረበት ዘመን የነበሩ ነገስታት ከምንም በላይ ለአገራዊ አንድነት ቅድሚያ ሲሰጡ አሁን ላይ የሚገኙ የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሰር ነን የሚሉ ግን ኦሮሞን እንገነጥላለን ይላሉ፡፡ የኢህአዴግ ፌደራሊዝም የይስሙላ ነው፡፡ ፓርቲው ሶሻሊስት በመሆኑ መሰረቱ ማዕከላዊነት ነው፡፡ ጥቂት የበላይ አመራሮች ሁሉን ነገር የሚወስኑበት ፓርቲ ነው፡፡ ለክልሎች ሰጠሁ ያለውን ስልጣን ጣልቃ በመግባት ብዙ ጊዜ ሲያፍን ተመልክተነዋል፡፡ እንደውም ከኢህአዴግ ዘመን ይልቅ በድሮ ጊዜ የየክልሉ ገዢዎች የተሻለ ስልጣን ነበራቸው፡፡ የራሳቸውን ጦር በማደራጀት ያስተዳድሩ ነበር፡፡ አገራዊ በሆነ አጀንዳ ላይ ግን በህብረት ከሌሎች ጋር ይሰሩ ነበር፡፡ የኢህአዴግ የድርጅት ባህሪና ፌደራሊዝም አብረው መሄድ የሚችሉ ነገሮች አይደሉም፡፡ ይህ የአስመሳይነትና የአታላይነት የፖለቲካ ባህል ነው፡፡ በአጭሩ በእኛ አመለካከት የፌደራል ስርአት ጂኦግራፊውን፣ በውስጡ የሚኖሩ ህዝቦች በስነ ልቦና የተገናኙ መሆናቸውን፣ ቋንቋቸውን፣ ለአስተዳደር ምቹ መሆኑን የመዘነ መሆን ይገባዋል፡፡ በአንድ አገር ውስጥ ክፍላተ ሀገራት እንዲኖሩ በማድረግ ስልጣኑ የክፍላተ ሀገራቱ እንዲሆን እንታገላለን፡፡
ላይፍ ፡- ኢህአዴግ እኔ ባልኖር አገሪቱ ትበታተናለች በማለት ሁልጊዜም ሲናገር ይደመጣል፡፡ የመበታተን ስጋት ተጋርጦባት ለነበረች አገር የመሰረትነው የፌደራል አወቃቀር ፍቱን መድሀኒት ሆኗል ማለቱን እንዴት ይመለከቱታል?
ኢንጅነር ፡- እኛ የምንከተለው የአስተሳሰብ መስመር ከኢህአዴግ የተለየ ነው፡፡ ከጋራ ጉዳይ ይልቅ ልዩነትን በማጉላት አገርን እጠብቃለሁ ማለት አታላይነት ብቻ ነው፡፡ አሁን ባለው እውነታ የብሔረሰብ አስተዳደር አለን በማለት ብትጠይቀኝ ምላሼ የለም ነው፡፡ አገሪቱን እየመሩ የሚገኙት ጥቂት ቡድኖች ናቸው፡፡ ባንኩን፣ መከላከያውንና ሌሎቹን ቁልፍ ቦታዎች እየመሩ የሚገኙት ከአንድ አካባቢ የመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ የብሄር ጭቆና ከየትኛውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ ውስጥ ያለው በዚህ አገዛዝ ነው፡፡ ብዛት ያላቸው ነጻ አውጪ ድርጅቶች የተፈጠሩት እኮ በዚህ ወቅት ነው፡፡ የብሄር ጥያቄ ከተመለሰ እነ ኦብነግን የመሳሰሉ ድርጅቶች እንዴት ሊፈጠሩ ቻሉ፡፡ መከላከያው ውስጥ ምን ያህል የብሄር ብሔረሰብ ተወካዮች በአመራር ቦታው ላይ ይገኛሉ? ፖለቲካን ትንተና ብቻ ማድረግ የለብንም፡፡ መሬት ላይ ያለውን እውነታም ልንመለከትበት ይገባል፡፡
ላይፍ ፡- የአንድ ቡድን የበላይነት ወይም ከአንድ ክልል የወጡ ሰዎች የስልጣን መደላደሉን በመያዝ የወጡበት ክልል ወይም ብሄር ስልጣን መያዝ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል?
ኢንጅነር ፡- የቡድኑን ተጠያቂነት ያሳያል፡፡ ከዚህ በላይም ለማደናገሪያነት ይውላል፡፡ ለምሳሌ ህወሃት ይህን ነገር ተጠቅሞበታል፡፡ አንደኛ ስልጣን የያዙት የእኛ ልጆች ናቸው፡፡ ተዋግተዋል፣ ደምተዋል መስዋዕትነት በመክፈላቸው ስልጣኑን መያዝ አለባቸው የሚል ስነ ልቦና እንዲፈጠር ሆኗል፡፡ የትግራይ ሰዎች ከዚህ በመነሳት ነገሮችን በዝምታ ማየቱ በስሙ እንዲነገድበት ሆኗል፡፡ ነገር ግን ጥቂቶች ይህንን ተገን በማድረግ እየተጠቀሙ ነው፡፡ ህወሃቶች ለትግራይ ህዝብ እኛ ከሌለን ሌላው ያጠፋሃል በማለት ከቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር እንዲቃረን እያደረጉት ነው፡፡ የትግራይ ህዝብ ተጠቅሟል ለማለትም አመራር ላይ ያለው ቡድን በተወሰነ ደረጃ የሚያደርገው ነገር አለ፡፡ ማደናገሪያ ቢኖረውም በዚያ አካባቢ ያለው ሰው ፊት ለፊት ወጥቶ መናገር አለበት፡፡ ሌላው ሰው በእነርሱ ቅር እንዲሰኝ እያደረገ የሚገኘው ነገርም ለዘብተኝነታቸው ይመስለኛል፡፡ አሁን አሁን ግን ይህ ነገር እየተቀረፈ ነው፡፡ በመቀሌ ዩኒቨርሲቲና በአረና ፓርቲ ውስጥ ያሉ አንዳንድ ወጣቶች ብቅ እያሉ ነው፡፡
ላይፍ ፡- በቅርቡ በጉራፈርዳና ቤኒሻንጉል አካባቢ ወደተከሰቱ መፈናቀሎች እንምጣ፡፡ ዜጎች የአንድ ክልል ተወላጆች በመሆናቸው ብቻ እንዲፈናቀሉ ተደርገዋል፡፡ ይህ ነገር በእርስዎ እይታ በምን መንስኤነት የተፈጠረ ነው?
ኢንጅነር ፡- ከጥቂት ቀናት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ለፓርላማው ቀርበው ሲናገሩ እንደሰማሁት ችግሩ የተፈጠረው በአቅም ማነስና በብቃት ችግር አይደለም፡፡ ወይም እዚያ አካባቢ ያሉ ኃላፊዎች በሙስና ከመጨማለቃቸው የተነሳ የተፈጠረ ነው ማለታቸውንም አልቀበልም፡፡ ነገሩ የተፈጠረው በፖሊሲ ደረጃ በደንብ ተጠንቶ ነው፡፡ አንደኛ ይህ ነገር አሁን የተፈጠረ አይደለም፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት ፓርላማ ቀርበው ‹‹ ደቡብ ውስጥ ለመኖር በመጀመሪያ የደቡብን አስተዳደር መጠየቅ ይገባል›› ብለው ነበር፡፡ ስለዚህ ከክልላችን ውጡ የሚለው ነገር ፖሊሲው ከተቀረጸበት እውነታ በመነሳት የተፈጠረ ነው፡፡
ላይፍ ፡- ፖሊሲውን ወይም ንድፉን ያወጣው ማን ነው ?
ኢንጅነር ፡- ህወሃት ነዋ፡፡ አንተ ለመጽሔትህ በደንብ እንድናገርልህ ፈልገህ ካልሆነ በስተቀር ይህ የሚታወቅ ነው፡፡ የተጨቆነ ብሄረሰብ እንዳለ ካመንክ እኮ ጨቋኝ የምትለው አካል የግዴታ ይኖራል፡፡ ከዚህ አንጻር ድርጅቱ አማራን በጨቋኝነት በመፈረጅ የአማራን አከርካሪ እሰብራለሁ በማለት ተነስቷል፡፡ በ1997 ምርጫ ወቅት ኢህአዴግ በዋናነት በከተሞች አካባባቢ ከፍተኛ ሽንፈት ሲያስተናግድ መለስ አሁንም የአማራና የቀድሞ መንግስት ናፋቂዎች እንዳልጠፉ ተረድቻለሁ በማለት መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ እነዚህ ንግግሮች እየዋሉ እያደሩ እንዲህ አይነት ችግሮች እንዲፈጠሩ ምክንያት ሆነዋል፡፡ በአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ላይ ያነጣጠረ ማፈናቀል መከሰቱ ትልቅ ትኩረት ማግኘት ይኖርበታል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዘር ማጥፋት ወንጀል እየተፈፀመ ነው የሚለውን ክስ ለማስቀረት ሲሉ ችግሩ የተፈጠረው በጥቂት ሃላፊነት በማይሰማቸው ሰዎች ነው በማለት ነገሩን ለማድበስበስ ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን ኢህአዴግን ጠንቅቆ የሚያውቅ ሰው አንድ ተራ ባለ ስልጣን ከመሬት ተነስቶ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን እንዲፈናቀሉ ያደርጋል በማለት ለመናገር ይቸገራል፡፡ ሌላው አስገራሚ ነገር በአሁኑ ሰአት አማራ ብቻ ሳይሆን ኦሮሞም ተፈናቅሏል ለማለት ኦሮሞ ነን የሚሉ ሰዎች ከቤኒሻንጉል እንደተፈናቀሉ ሲናገሩ እያደመጥን ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች እስካሁን ድረስ የት ነበሩ ? ኢህአዴግ የመሬት ባለቤቶች ብሄር ብሄረሰቦችና ብሄሮች ናቸው ብሏል፡፡ በኢህአዴግ አመለካከት መሰረት እኔ የመሬት ባለቤት መሆን አልችልም፡፡በኢህአዴግ አስተሳሰብ ሁላችንም በህግ እኩል አይደለንም፡፡ ያለ ብሄርህ በመሄድ መሬት የምትዘው አንተ ማን ነህ? የሚለው አስተሳሰብ የመነጨው ስርኣቱ ከሚከተለው ፖሊሲ ነው፡፡
ላይፍ ፡- አንዳንዶች አቶ ኃይለማርያም በፓርላማው በመቅረብ ችግሩን በማመን በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ኃላፊነቱን የሚወስድ አካል እንደሚኖር መጠቆማቸውን እንደ በጎ ጅምር በመውሰድ መለስ ቢሆኑ ኖሮ ተፈናቃዮቹን መሬት ወራሪዎችና ተስፋፊዎች በማለት ይነቅፏቸው ነበር ይላሉ፡፡ በዚህ አስተያየት ይስማማሉ፡፡
ኢንጅነር ፡- አንዳንድ ሰው እንግዲህ ያለበትን ሁኔታ መቀየር ያስፈልገው ይሆናል፡፡ መለስም እኮ በተወሰነ ደረጃ አቋማቸውን እንደቀያየሩ የመጡበት መንገድ ማሳያ ሆኖ መቅረብ ይችላል፡፡ እንደውም እንደ መለስ ተገለባባጭ አይነት ሰው ተመልክቼ አላውቅም፡፡ ሲመጡ ሊበራል ዴሞክራሲ፣ ነጭ ካፒታሊዝም ነው የምናራምደው አሉ፡፡ መጀመሪያ ማሌለት ነበሩ፡፡ ከዛ 1997 ላይ ታማኝ ጠንካራ ተቃዋሚ ብናገኝ ግማሽ መንገድ ድረስ ተጉዝን እንቀበላለን አሉ፡፡ ነገር ግን የሆነው ከሆነ በኋላ ልማታዊ መንግስት ነን፣ መስመሩም ዴሞክራሲ ነው አሉን፡፡ አሁንም ቢሆን በህይወት ቢኖሩ ኖሮ የማይጠበቅ ነገር ሊናገሩ ይችላሉ፡፡ አውቃለሁ መለስ መሸነፍ የማይፈልጉ እልኸኛ ሰው ናቸው፡፡ ቢሆንም ግን አለም አቀፍ ጫናው የማያምኑበትን እንኳን እንዲናገሩ ሊያደርጋቸው እንደሚችል አምናለሁ፡፡ መለስ ወጥ አቋም የነበራቸው የመርህ ሰው አይደሉም፡፡ ዛሬ ያነበቡትን መጽሀፍ በመያዝ የሚከራከሩ ነገ ደግሞ የትናንቱን በመተው የሚቀየሩ በጓደኞቻቸው ዘንድም ተለዋዋጭ ተደርገው የሚወሰዱ ነበሩ፡፡ በእርግጥ የአቶ መለስ አይነት የትግል መሰረትና መነሳሳት አቶ ኃይለማርያም ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ምክንያቱም የመጡት ከትምህርት አካባቢ ነው ፡፡ ስለዚህ አማራውን ጨቋኝ በማድረግ በመሳል የመከትከት አላማ ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ከዚህ በመነሳት ነባራዊውን ሁኔታ ከግምት በማስገባት የተወለጠ ነገር ተናግረዋል፡፡ መለስም አቅም ሲያጡና የሚገቡበት ሲጠፋቸው እንዲህ ሊናገሩ ይችሉ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን ግን ከንግግር ያለፈ ነገር አለመደረጉ መሰመር ይገባዋል፡፡ ተፈናቅለው ለነበሩ ሰዎች ምን ተደረገ ? ንብረታቸውን በትነውና የልጆቻቸውን ትምህርት አቋርጠው ለሶስት ወራት ያህል ሲንከራተቱ መንግስት ምን ይሰራ ነበር ? የአሁኑ ንግግር ከጫና የመጣ እንጂ አምነውበት የተናገሩት አይደለም፡፡ ኃይለማርያም ምናልባት የአፈጻጸም ችግር በማለት በግልጽ ተናግረው ይሆናል፡፡ መለስ በዚህ ቦታ ቢሆኑ ኖሮ ነገሩን በብልጣብልጥነት ለማለፍ ይሞክሩት እንደነበር ይሰማኛል፡፡
ላይፍ ፡- ሁኔታውን ለማጣራት ወደ ቤንሻንጉል ክልል የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ማምራታችሁንና ለተወሰኑ ሰዓታትም መታሰራችሁን ሰምተናል፡፡ እስኪ በአጠቃላይ ስለተፈጠረው ነገር ይንገሩን?
ኢንጅነር ፡- እውነት ለመናገር ስራ ስትሰራና ስትንቀሳቀስ ለአምስት ሰዓታት ያህል ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ እንድትቆይ መደረግህ ያን ያህል የሚወራለት አይሆንም፡፡ ይህ ግን የሚያሳየው ዜጎች በነጻነት ከቦታ ቦታ ተዘዋውረው መረጃ ማግኘት እንደማይችሉ ነው፡፡ በተጨማሪ ደግሞ በእኛ ላይ እንዲህ አይነት ነገር ያደረጉ ሰዎች እዛ በሚኖሩ ሰዎች ላይ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ እንድናስብ ያደርገናል፡፡ ከዜጎች ጋር በመገናኘታችን ብቻ ይህንን እርምጃ ከወሰዱ መሬታችንን ወስዳችኋል በሚሏቸው ሰዎች ላይማ ምን ሊያደርጉ እንደሚችሉ ማሰብ በራሱ ይከብዳል፡፡ ተፈናቃዮቹ በአፋጣኝ ይዞታቸውን እንዲለቁ በመደረጋቸው ዘጠኝ ሺ ብር የምትሸጥ ላም በአንድ ሺህ አምስት መቶ ሸጠዋል፡፡ ተንቀሳቅሰን የተመለከትነው ሶስት ቀበሌዎችን ነው፡፡በአንድ ቀበሌ 58 ሰው በህገ ወጥ መንገድ ስለገባችሁ እንድትለቁ የሚል ወረቀት በይፋ ነው የተለጠፈባቸው፡፡
ላይፍ ፡- የትና ማን ነው የለጠፈው ? ወረቀቱስ ማህተም ነበረው ?
ኢንጅነር ፡- ማህተሙ የቀበሌ ገበሬ ማህበር ነው፡፡ ወረቀቱ ሌላው ቀርቶ ያላችሁን ንብረት ሸጣችሁ እንድትለቁ በማለት ያዛል፡፡ እቃቸውን እንኳን ይዘው የመውጣት መብት አልነበራቸውም፡፡
ላይፍ ፡- ንብረታቸውን እንዲህ በወረደ ዋጋ የገዛው የአካባቢው ማህበረሰብ ነው ?
ኢንጅነር ፡- የሚገዛ በማጣታቸው እኮ ነው ከመጣል ብለው የሸጡት፡፡ ዘጠኝ ሺህ ብር የሚያወጣ ላም በአንድ ሺህ ብር ስለተሸጠ ሸጠው ወጡ በማለት መናገር አይቻልም፡፡ እኔ ጥለው በትነው ወጡ ነው የምለው፡፡ እንዲመለሱ ከተደረገ በኋላ የአማራ ክልል ኃላፊዎች መጡ ተባለ፡፡ ነገር ግን ምንም ያደረጉላቸው ነገር የለም፡፡ ሰዎቹ እኮ ዝርፊያና ድብደባ ጭምር ተፈጽሞባቸዋል፡፡
ላይፍ ፡- ድብደባውን የፈፀሙት ይታወቃሉ ?
ኢንጅነር ፡- ፖሊሶችና የአካባቢው ታጣቂዎች ናቸው፡፡ እኔ ካናገርኳቸው ተፈናቃዮች መካከል 60 ሺህ ብር የተወሰደበትና 60 መሃለቅ የአንገት ወርቅ የተነጠቀች እናት ይገኙበታል፡፡ በሰደፍ የተደበደቡ ሰዎች ቁስላቸው ገና ባለመድረቁ ድብደባው ያደረሰባቸውን ጉዳት መመልከት ይቻላል፡፡
ላይፍ ፡- ያለ ፍላጎታቸው እንዲፈናቀሉ የተደረጉት የአማራ ብሄር ተወላጆች በድጋሚ ያለ ፍላጎታቸው ተገድደው ወደ ቤንሻንጉል እንዲመለሱ ስለመደረጋቸው አንዳንድ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እርስዎ በዚህ ዙሪያ የተመለከቱት ምንድን ነው ?
ኢንጅነር ፡ እነርሱ ምንም አይነት ስልጣን እዚህ ውስጥ የላቸውም፡፡ በኃይል እንዲወጡ እንደተደረጉ ሁሉ በኃይል እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ሲሄዱም ሆነ ሲወጡ የእነርሱ ፈቃድ አልተጠየቀም፡፡
ላይፍ ፡- ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደተናገሩት ይህንን ድርጊት የፈፀሙ ኃላፊዎችን በማንሳት ብቻ መፈናቀሉ እንዲቆም ማድረግ ይቻላል ብለው ያምናሉ ?
ኢንጅነር ፡- አይቆምም፡፡ አንድ ሰው በኢሳት ተጠይቆ እኮ ‹‹ ምንግዜም ችግር ሲመጣባቸው በእኛ ላይ መለጠፋቸው የተለመደ ካልሆነ በስተቀር ክልሉ ሳያውቀው የተሰራ ምንም ነገር የለም›› ብሏል፡፡ ነገሩ በፖሊሲ ደረጃ ተይዞበት የተሰራ ስለመሆኑ ምንም መከራከርያ አያስፈልግም፡፡
ላይፍ ፡- የአማራው ውክልና አለኝ የሚለው ብአዴን በጉዳዩ ዙሪያ ዝምታን መምረጡን እንዴት ተመለከቱት ?
ኢንጅነር ፡- ቅድም እኮ ብዬሃለሁ፡፡ እዚህ አገር የፌደራል አስተዳደርም ሆነ ስልጣን ያላቸው ፓርቲዎች የሉም፡፡ አገሩን የሚመራው የተወሰነ የፖለቲካ ቡድን ነው፡፡ ጣልያን በወረራው ወቅት የተወሰኑ የጎሳ መሪዎችን በመሾም ቅኝ ግዛቱ ሊያደርግን ሞክሮ ነበር፡፡ ሌላው አማራ የሚባል ጎሳ(ብሄር) መኖሩን አማሮች የምትላቸው ሳይቀሩ አያምኑም፡፡ ለምሳሌ እኔ ጎጃም ነው የተወለድኩት፣ ከጓደኞቼ ጋር ስንጨዋወት እስላም አማራ እንላለን እንጂ አማራ ጎሳ ስለመሆኑ አናውቅም፡፡ እኔ አማራ የሚባል ጎሳ ስለመኖሩ የሰማሁት ዩኒቨርስቲ ከገባሁ በኋላ ነው፡፡ አማርኛ ተናጋሪው በብሔረሰብ የሚያምን አይደለም፡፡ እንደው ከአንዳንድ አክራሪዎች ጋር እንዳታጣለኝ እንጂ አማራ የሚባል ጎሳ(ብሄር) ስለመኖሩ የሚያሳይ ማስረጃ የለም፡፡ ልክ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ ጉራጌ ከዚህ ወጣ እዚህ ገባ እንደሚባለው አይነት ማስረጃ የለም፡፡ አማራ የሚለውን ቃል የሚጠቀሙበት እስላም ክርስቲያን ለማለት ነው፡፡ ይህ የህብረተሰብ ክፍል ከበሮ ተመትቶ አገር ተወረረች ሲባል ሆ ብሎ ተነስቶ ጦርነት ይገጥማል፡፡ባህሉ፣ ሃይማኖቱና አመለካከቱ ሁሉ በኢትዮጵያዊነት የታጠረ ነው፡፡ ይህንን የሚያደርገው የተለየ ጥቅም በማግኘቱ አይደለም፡፡ ከኩርማ መሬት ውጪ በየትኛውም ስርዓት ተጠቃሚ አልሆነም፡፡
ላይፍ ፡- ምናልባት ግን መፈናቀሉ በዋናነት አማራው ላይ ያነጣጠረው አማራውን የሚወክል ድርጅት ባለመኖሩ ይሆን ?
ኢንጅነር ፡- እኔ እንዲህ አይነት ድርጅት መኖር አለበት ብዬ አላምንም፡፡ የእነዚህ ሰዎች አስተሳሰብ ኢትዮጵያዊነት ነው፡፡ በጎሳው ለማያምን ሰው የሆነ የጎሳ ድርጅት ማቋቋም ተገቢ ነው ብዬ አላስብም፡፡ አማራው በጎሳ እንዲታጠር ከተደረገም ኢትዮጵያ አለቀላት ብዬ ነው የማምነው፡፡
ላይፍ ፡- በቅርቡ የቀድሞው የህወሃት አንጋፋ ታጋይ አቶ ስብሃት ነጋ ኢህአዴግ የአፍሪካ ምርጡ ፓርቲ ነው በማለት መናገራቸው ተሰምቷል፡፡ በእርስዎ ደረጃ ኢህአዴግ ግን የት ያስቀምጡታል ?
ኢንጅነር ፡- በመጀመሪያ ደረጃ ኢህአዴግ የሆነ የፖለቲካ መስመር የሚከተል ድርጀት አይደለም፡፡ ከህወሃት አንስቶ ዝብርቅርቅ ያለ መስመር የሚከተል አንድ አይድኦሎጂ የሌለው ነው፡፡ ቀደም ብዬ ለመጠቆም እንደሞከርኩት ብሄራዊ ስሜት፣ ታሪክን፣ ባህልንና ማንነትን ያዋረደ ነው፡፡ ጉልበት በእጁ በማስገባቱም ሁሉንም አዳክሞ እየገዛ ነው፡፡ አዎን ከዚህ አንጻር ከሆነ ስብሃት እንዳሉት የአፍሪካ ምርጡ ፓርቲ ነው፡፡

“ከሁሉም በላይ የሚያስቆጨኝ ልጁን አቅፎ በአባትነት ፍቅር እንዳይደባብሰው እንኳ አለመፍቀዱ ነው” (የውብሸት ባለቤት ወይዘሮ ብርሃኔ ተስፋዬ)



ጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ በቅርቡ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ወደ ዝዋይ እንዲዘዋወር ተደርጓል፡፡ የቤቱ ምሰሶ የነበረው ጋዜጠኛው ማረሚያ ቤት በመወርወሩ ምክንያት ቤተሰቡ ችግር ላይ ይገኛል፡፡ ወደ ዝዋይ እንዲዘዋወር መደረጉ በራሱ ደግሞ የቤተሰቡን ችግር የበለጠ ያከፋዋል፡፡ ዳዊት ሰለሞን የውብሸትን ባለቤት ወይዘሮ ብርሃኔ ተስፋዬን በማግኘት በጉዳዩ ዙሪያ አነጋግሯል፡፡  
ላይፍ ፡- እስኪ ቃለ ምልልሳችንን ራስሽን በማስተዋወቅ ጀምሪ
ላይፍ ፡- ስሜ ብርሃኔ ተስፋዬ ይባላል፡፡ የጋዜጠኛ ውብሸት ታዬ ባለቤት ነኝ፡፡
ላይፍ ፡- ከውብሸት ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ ስተገናኘችሁበት አጋጣሚ እናውራ፡፡ እንዴት ነበር የተገናኛችሁት ?
ብርሃኔ ፡- መገናኘት ( ትንሽ ዝምታ) የጀመርነው ከረዥም አመታት በፊት ነው፡፡ በአጭሩ አብረን ነው ያደግነው ማለት እችላለሁ፡፡ ከተጋባን ግን አምስት አመት ሆኖናል፡፡
ላይፍ ፡- ጋዜጠኛውን  ውብሸትን ይጽፋቸው በነበሩ ጽሁፎች እናውቀዋለን፡፡ ነገር ግን እንደ አባወራ ለቤቱና ለትዳሩ ምን አይነት ሰው ነበር ? 
ብርሃኔ ፡- ባል የሚለው ነገር ለእኔ ብዙም ግልጽ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ቃሉ ይገልፀዋል ብዬ አላምንም፡፡ ለእኔ ውብሸት ባሌ ብቻ ሳይሆን ሁሉም ነገሬ ነው ማለት እችላለሁ፡፡በዛ ላይ ደግሞ የልጄ ሁሉም ነገሩ ነው፡፡ እንደ እናትና አባት በመሆን ያሳድገው ነበር፡፡ ከአባት በላይ ነው፡፡ እኔ ለልጁ እናት ብሆንም እንደ ውብሸት ግን እሆንለታለሁ ብዬ አላምንም፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት ከታሰረ በኋላ ቤቱን የማስተዳደር ኃላፊነት ሙሉ ለሙሉ በአንቺ ላይ ወድቋል፡፡ እንዴት ነው ህጻን ልጅ ይዘሽ ህይወትን የተጋፈጥሽው ?
ብርሃኔ ፡- ውብሸት ከመታሰሩ በፊት ፍትህ ( የልጁ ስም ነው ) ትምህርት ቤት አልገባም ነበር፡፡ ትምህርት ቤት የገባው ከአባቱ መታሰር በኋላ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ የሶስተኛ አመት የኮሌጅ ተማሪ ነኝ፡፡ ትምህርቱን የጀመርኩት ውብሸት እያለ ነው፡፡ ፍትህ ትምህርት የጀመረው አምና ነው፡፡ ዘንድሮ መደበኛ ትምህርት ጀምሯል፡፡ የአባቱ አለመኖር ከፍተኛ ተጽእኖ በእኔ ላይ ፈጥሯል፡፡ የምንኖረው ቤት ተከራይተን ነው፡፡ በቀን ፕሮግራም የምማር በመሆኑ ስራ ወይም ሌላ ገቢ የለኝም፡፡ ሙሉ ለሙሉ ቤቱን ያስተዳድር የነበረው ውብሸት ነበር፡፡ ይህንን ማጣት የቤተሰቡን አባላት በከፍተኛ ደረጃ ይጎዳል፡፡ ውብሸት በመታሰሩም እርሱን ለመጠየቅ ትራንስፖርት መጠቀም ግድ ይላል፡፡ በአጠቃላይ ለእኛ ነገሩ በጣም ፈታኝ ነው፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት በታሰረበት ወቅት ይሰራበት የነበረው ጋዜጣ ደሞዙን በፍጥነት ማቋረጡ ይነገራል፡፡ ይህ ምን ያህል እውነት ነው ? የጋዜጣው ባልደረቦች በዚህ በኩል ያደረጉት ነገርስ ምንድን ነው ?
ብርሃኔ ፡- ውብሸት ከታሰረ በኋላ ጋዜጣውም ብዙ መቀጠል አልቻለም፡፡ ቢሮ በመቀያየር ብዙ ወጪ በማውጣታቸውም ለእኛ የተለየ ነገር እንዳያደርጉ እንቅፋት ሳይፈጥርባቸው አልቀረም፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት በቅርቡ ወደ ዝዋይ እንዲዘዋወር ተደርጓል፡፡ የሚገኝበት ማረሚያ ቤት እየራቀ መምጣቱም ለተጨማሪ የትራንስፖርት ወጪ የሚዳርግ ይሆናል፡፡ እናስ ምንድን ነው ያቀድሽው ? 
ብርሃኔ ፡- ቂሊንጦ እያለ ለትራንስፖርት የሚከፈል በማጣቴ የተነሳ አይኑን ለማየት ልጁን በመያዝ የምሄደው በሳምንት አንድ ቀን ነበር፡፡ ወደ ዝዋይ እንደሄደም የሰማሁት ከሰዎች ነው፡፡
ላይፍ ፡- ወደ ዝዋይ እንደሚሄድ ቀደም ብላሽ አላወቅሽም ነበር ? ማረሚያ ቤቱስ ለታራሚዎቹ ቤተሰቦች መረጃ አይሰጥም ?
ብርሃኔ ፡- እሁድ እለት ሰዎች ደውለው ‹‹ውብሸት ዝዋይ ተወስጃለሁ›› ብሎሻል በማለት ነገሩኝ፡፡ በቃ ምንም አማራጭ ስላልነበረኝ ወደተባለው ቦታ ሄድኩኝ፡፡ የዝዋይ መንገድ በጣም አድካሚ ነው፡፡ ከአዲስ አበባ 160 ኪሎ ሜትር ይርቃል፡፡ የቂሊንጦን ሶስት አራት እጥፍ ይሆናል፡፡ ወጪውም የዚያኑ ያህል ነው፡፡ ጠዋት 11፡00 ወጥቼ እቤቴ የገባሁት ምሽት ነው፡፡ በራሱ እዚያ ድረስ መሄድ ትልቅ መከራ ነው፡፡ ዝዋይ ድረስ የአራት አመት ህጻን ይዞ መመላለስ ምን ያህል አስቸጋሪ እንደሚሆን ያልደረሰበት ያውቀዋል ለማለት እቸገራለሁ፡፡ የቂሊንጦ መንገድ በራሱ እንኳን ለህጻን ይቅርና ለትልቅ ሰው በጣም የሚያሰለች ነበር፡፡ ፍትህ አንደርስም ወይ እያለ እያለቀሰ ነበር የደረሰው፡፡
ላይፍ ፡- ፍትህ አባቱን ለመጠየቅ ወደ ማረሚያ ቤት እንደምትሄጂ ሲያውቅ ምን ይላል ?
ብርሃኔ ፡- አርብ ደርሶ ቅዳሜ ትምህርት እንደሚዘጋ ሲያውቅ ሁልጊዜም አባቢ ጋር ውሰጂኝ እያለ ያስጨንቀኛል፡፡ መንገዱ ሩቅ ነው ብለው ሊሰማኝ አይችልም፡፡ ያለኝ አማራጭ መውሰድ ብቻ ስለነበረ በመንገዱ ርቀት እየተማረረና እያለቀስም ቢሆን አድርሼው መጣሁ፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት በአሁኑ ሰአት የሚገኝበት የጤንነትና የስነ ልቦና ሁኔታ ምን ይመስላል ?
ብርሃኔ ፡- ቂሊንጦ እያለ የማረሚያ ቤቱን መጻኅፍት እየተጠቀመ ያነብ ነበር፡፡ ትምህርታቸውን በተለያዩ ምክንያቶች ያቋረጡ ታራሚዎችንም ያስተምር ነበር፡፡ ጊዜውን በስራ ያሳልፍ ስለነበር ጭንቀት አልነበረበትም፡፡ አሁን ግን ሁሉ ነገር ለእርሱ አዲስ ነው፡፡ ያለውን ሁኔታ እስኪላመድ ድረስም መቸገሩ አይቀርም፡፡ እንደነገርኩህ እኔ ተማሪ ነኝ፡፡ ልጁም የተሻለና ጥሩ ትምህርት ቤት መማር አለበት፡፡ እነዚህ ነገሮች ያስጨንቁታል፡፡
ላይፍ ፡- ፍትህን ውብሸት ጋር ስትወስጂው አባቴ ለምን እኛ ጋር አይመጣም በማለት አይጠይቅሽም ? 
ብርሃኔ ፡- ፍትህ ውብሸት እስር ቤት ስለመሆኑ አያውቅም፡፡ አባቴ ትምህርት ቤት ነው ብሎ ነው የሚያምነው፡፡ ከመጀመሪያው ጀምሮ ሁለታችንም ታሰረ የሚለውን ነገር እንዳይሰማ ትልቅ ጥንቃቄ አድርገናል፡፡ ውብሸትም ትምህርቴን ስጨርስ እመጣለሁ ይለዋል፡፡ ህጻኑ የሚገኝበት የዕድሜ ክልልም ስለ እስር ቤት ለማወቅ የሚያስችለው አይደለም፡፡ አሁን የእኛ ስጋት የውብሸት ራቅ ያለ ቦታ መታሰር እንደነገርኩህ ከትራንስፖርት ችግር የተነሳ በየሳምንቱ በመሄድ ልጠይቀው አልችልም፡፡ በወር አንድ ጊዜም ማየት ከቻልኩ ትልቅ ነገር ነው፡፡ አራትና ሶስት ሳምንት ፍትህ አባቱን ማየት ካልቻለ ምን እንደምለው አላውቅም፡፡ ዝዋይ ወባ አለ፣ ልጁ በሚመላለስበት ወቅት ትንኝ ነክሳው በወባ ሊያዝ ይችላል የሚል ስጋትም ውብሸት እየተሰማው ይገኛል፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት የታሰረበት ማረሚያ ቤት እናንተ ከምትገኙበት አካባቢ ሩቅ መሆኑን በመጥቀስ በአቅራቢያው በሚገኝ ማረሚያ ቤት እንዲታሰር ጥያቄ አላቀረብሽም ?
ብርሃኔ ፡- በፍትህ ሚኒስትር በኩል ጥያቄዬን አቅርቢያለሁ፡፡ ሌላው ቢቀር የዚህ ህጻን አባቱን የማግኘት መብት ሊከበር ይገባዋል፡፡ ቤተሰቡ ካለበት ችግር አንጻር ውብሸት ቅርብ ቦታ እንዲሆንልን በቻልኩት መጠን እየተማጸንኩ እገኛለሁ፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት ፍትህን በማረሚያ ቤት ሲያገኘው አቅፎት እንዲስመውና የልጅነት ትንፋሹን እንዲያሸተው ይፈቀድለታል ?
ብርሃኔ ፡- በአጠያየቅ ደረጃ ከዝዋይ ይልቅ ቂሊንጦ የተሻለ ነበር፡፡ ቂሊንጦ እያለ ውብሸት ልጁን አቅፎ ወደ ውስጥ አስገብቶት እንዲያጫውተው ይፈቀድለታል፡፡በዝዋይ ግን እንዲህ አይነት ነገር አይፈቀድም፡፡ ባለፈው ይዤው ሄጄ ውብሸት ስፍሰፍ ብሎ ሊያቅፈው ሲል ፖሊሶቹ አይቻልም በማለት ከልክለውታል፡፡ ያለኝ አማራጭ ልጁን ማባባል በመሆኑ እንደምንም ብዬ ነገሩን እንዲረሳው አድርጌዋለሁ፡፡
ላይፍ ፡- ከአዲስ አበባ ዝዋይ ከደረስሽ በኋላ ከውበሸት ጋር ለመነጋገር የሚፈቀድልሽ ምን ያህል ደቂቃ ነው ?
ብርሃኔ፡- የሚበዛውን ሰዓት በመንገድ የምጨርሰው በመሆኑ ውብሸትን እንደ ልብ ለማዋራት የሚያስችለኝን ጊዜ አላገኝም፡፡ 5፡30 ከደረስኩ ለ30 ደቂቃ ያህል አውርቼው ስድስት ሰዓት ሲሆን እንድወጣ እደርጋለሁ፡፡ ከሁሉም በላይ የሚያስቆጨኝ ልጁን አቅፎ በአባትነት ፍቅር እንዳይደባብሰው እንኳ አለመፍቀዱ ነው፡፡  ህጻኑ አባቱን ለመሳም እንደናፈቀ በመካከላቸው በቆመው አጥር ምክንያት ምኞቱን ሳይፈጽም መመለሱን ማየት ትልቅ ህመም ነው፡፡
ላይፍ ፡- ሁለቱ የስዊዲን ጋዜጠኞች በተለቀቁ ሰሞን ውብሸትም ሊወጣ እንደሚችል በስፋት ይነገር ነበር፡፡ ነገር ግን እስካሁን ብዙዎች ተስፋ ያደረጉት ነገር እውን መሆን አልቻለም፡፡ ባለቤትሽ ያልተፈታበትን ምክንያት ለማወቅ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን ሰዎች አነጋግረሻል ?
ብርሃኔ ፡- ሁሉም ሰው ገምቶት እንደነበረው የስዊዲን ጋዜጠኞች ሲወጡ ሰዎች እየደወሉ እንኳን ደስ ያለሽ ይሉኝ ነበር፡፡ እኔም ከተፈቱት ጋዜጠኞች ተለይቶ ማረሚያ ቤት እንዲቆይ ይደረጋል የሚል እምነት አልነበረኝም፡፡ የጋዜጠኞቹን መፈታት የሰማሁት በሸገር ራዲዮ ነበር፡፡ ከአሁን አሁን የውብሸትን ስም ይጠሩታል በማለት ስጠብቅ ነበር፡፡ በዜግነት ቦታ ተሰጥቶን ቅድሚያ አግኝተን የተሻለ ነገር ሊደረግልን ሲገባ እንዲህ መደረጉ አስገርሞኛል፡፡ የስዊዲን ጋዜጠኞች በመፈታታቸው አላዘንኩም፡፡ ምክንያቱም በእነርሱ መፈታት ደስተኛ የሆነና ከጭንቀት የዳነ ቤተሰብ አለ፡፡ ፍትህ ሚኒስትር ሄጄ ስጠይቅ አጥጋቢና ትክክለኛ ምላሽ አላገኝም፡፡ አንዳንዴ ነገሩ ሚኒስትሩ ጋር ቀርቧል፣ ተመልክተውታል ይሉኛል፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ ገና ሊቀርብ ነው ይሉኛል፡፡ አንድ አይነት ምላሽ ባለመኖሩም የሚባለውን ነገር ለማመን ተቸግሪያለሁ፡፡
ላይፍ ፡- አሁን ተስፋ የምታደርጊው ነገር ምንድን ነው ? ጉዳዩ ቶሎ አልቆ ውብሸትን እቤት አገኘዋለሁ ትያለሽ ?
ብርሃኔ ፡- ብዙ ነገሮች ጠብቀሃቸው ከቦታቸው ሳታገኛቸው ስትቀር ተስፋ ለማድረግ ትቸገራለህ፡፡ ስለዚህ እኔ ተስፋ የማደርገው ነገር የለም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመሞቱ የሆነ የተንዛዛ ነገር እንደተፈጠረ ሰምቺያለሁ፡፡ ነገር ግን አሁን ተተኪው ቦታውን በመያዛቸው ነገሮች እንደተረጋጉ ይሰማኛል፡፡ ስለዚህ የሚያደርጉትን በትእግስት መጠበቅ ነው፡፡
ላይፍ ፡- ልጃችሁን ፍትህ በማለት የሰየመው ማን ነው ? ትርጉሙስ ምን ይሆን ? 
ብርሃኔ ፡- ፍትህ በማለት የሰየመው ውብሸት ነው፡፡ ፍትህ ምኞት ነው፡፡ የልጁ አንድ አመት በተከበረበት ወቅት ውብሸት ‹‹አንተና የአንተ ትውልድ አባላት ፍትህ በሰፈነባት አገር እንደትኖሩ መልካም ምኞታችን ነው ›› በማለት ተናግሮ ነበር፡፡ መቼም ጥሩ ነገር የማይመኝ የለም፡፡ ከዚህ አንጻር ውብሸት ዜጎቿ የማያለቅሱባት፣ መልካም ነገሮች የሚገኙባት አገር እንደትኖረን በመመኘት ልጁን ፍትህ በማለት ሰይሞታል፡፡
ላይፍ ፡- ይህንን መልካም ነገር ለአገሩ የተመኘ ጋዜጠኛ ታስሮ ነገር ግን ፍትህ ልጅ ሆኖ ስታገኚው ምንድን ነው የሚሰማሽ ?
ብርሃኔ ፡- ወብሸት ምኞቱን የገለፀው ለልጁ ትውልድ በሙሉ ነው፡፡ ፍትህ ልጅ ሆኖ አጠገቤ መገኘቱ ለእኔ በራሱ ትልቅ ፍትህን እንደማግኘት ነው፡፡ እስኪ አስበው ውብሸት ታስሮ ብቻዬን ብሆን ኖሮ ምን ይውጠኝ ነበር? ፍትህ አጠገቤ በመሆኑ ግን እፅናናለሁ፡፡
ላይፍ ፡- ጋዜጠኛ ርዕዮት አለሙ በቅርቡ የዩኔስኮን አለም አቀፍ ሽልማት አግኝታለች፡፡ ውብሸት በርዕዮት መሸለም የተሰማው ምንድን ነው ?
ብርሃኔ ፡ - እጅግ በጣም ተደስቷል፡፡ የተሰማውን ደስታም ለርዕዮት ለመግለጽ ሰዎችን ልኳል፡፡ እውነቱን ለመናገር ሽልማቱ ‹‹ለካ አለም አልረሳንም›› የሚል ስሜት እንዲፈጠርበት አድርጎታል፡፡ ሽልማቱ የታሳሪዎቹን ሞራል በመገንባቱ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበርክት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
ላይፍ ፡- የውብሸት ባለቤትና የልጁ እናት በመሆንሽ ምንድን ነው የሚሰማሽ ?
ብርሃኔ ፡- ይህንን የምለው ሁልጊዜም ነው፡፡ የውብሸት ባለቤት በመሆኔ እድለኛ ነኝ፡፡ ውብሸት እኔን ወደ ሙሉነት የቀየረኝ ሰው ነው፡፡ እርሱ ለእኔ አባቴና እናቴ ነው፡፡ ከትምህርት ቤት ወደ ቤት ስመጣ እርሱ ቀድሞኝ እቤት ከደረሰ ልጁን ይዞ እኔን ለመቀበል ወደ ውጪ ይወጣ ነበር፡፡ እነዚህ ነገሮች ሁልጊዜም በእርሱ ደስተኛ እንድሆን አድርገውኛል፡፡
ላይፍ ፡- ውብሸት ከመታሰሩ በፊት ይጽፋቸው በነበሩ ጽሁፎች የተነሳ ሊታሰር ይችላል የሚል ስጋት ነበረሽ?
ብርሃኔ ፡- እኔ ብዙም ጠልቄ አላውቅም፡፡ ነገር ግን ጋዜጠኝነት በራሱ የሆነ አደጋ እንዳለው ይታወቀኝ ነበር፡፡ ይህም ቢሆን ግን አንድ ቀን እንኳን ስራውን እንዲያቆም ተጭኜው ወይም ተናግሬው አላውቅም፡፡ ምክንያቱም የሚሰራው የሚወደውን ነገር እንደሆነ አውቃለሁ፡፡
ላይፍ ፡-  ነገ ፍትህ አድጎ የአባቱን መንገድ በመከተል ጋዜጠኛ ቢወጣው ምክርሽ ምንድን ነው የሚሆነው ?
ብርሃኔ ፡- የተሻለ ነገር እንዲሰራ በመምከር እንዲበረታታ ከጎኑ እቆማለሁ፡፡