Thursday 4 July 2013

የኩማ አስተዳደር የመጨረሻውን የስንብት ጉባዔ ሊያደርግ ነው

ሰኔ ፳፮ (ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና :-አዲስ አበባን ለ5 አመታት ሲመራ የነበረው የኩማ አስተዳደር  ሐሙስ ሰኔ 27 ጀምሮ  ለአዲሱ ኢህአዴግ መራሽ ካቢኔ ሥልጣኑን እንደሚያስረክብ ተጠቆመ፡፡
በመልካም አስተዳደር ችግር፣ በሙስናና ብልሹ አሰራር የሚተቸው የኩማ አስተዳደር የምርጫ 97 ቀውስን ተከትሎ ከተመሰረተው የባለአደራ አስተዳደር ስልጣኑን በግንቦት ወር 2000 ዓ.ም በምርጫ ስም የተረከበ ሲሆን ባለፉት አምስት ዓመታት የከተማዋን ሕዝብ የሚያረካ ሥራ ሳያከናውን ለመሰናበት መብቃቱን ለአስተዳደሩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
የኩማ አስተዳደር ስራ እንደጀመረ መልካም አስተዳደርን ለማስፈን በሚል የኢህአዴግ አባላትና
ደጋፊ ለሆኑ በሺ የሚቆጠሩ ጀማሪ ምሩቃን ተማሪዎችን በመቅጠርና ያለልምድ በከፍተኛ ኃላፊነቶች ጭምር ማሰቀመጡ ነባሩን ሠራተኞች ከማስከፋቱም በተጨማሪ አብዛኛዎቹ ወጣቶች በሙስናና ብልሹ አሰራር ውስጥ በመጠለፋቸው ዕቅዱ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
የአስተዳደሩ ምክር ቤት ከሰኔ 27 እስከ 29 ድረስ ምክር ቤቱ በሚያደርገው ስብሰባ ላይ የአስተዳደሩን የአምስት አፈፃጸምና የ2006 በጀት ጨምሮ በስምንት አጀንዳዎች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል ። በጉባዔው ማጠቃለያ ሰኔ 29 ነባሮቹን የምክር ቤት አባላት የምስክር ወረቀት አሰጣጥ ሥነሥርዓት ከተከናወነ በሃላ አዲሱ ምክር ቤት ስልጣን እንዲረከብ ይደረጋል ።
አዲሱ ምክርቤትም  ከንቲባውንና ምክትል ከንቲባውን ይመርጣል። አዲሱ ከንቲባም ካቢኔያቸውን በመሰየም ስራቸውን ይጀምራሉ ተብሎ ይጠበቃል። በመምረጥ ሥራውን ይጀምራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በአ/አ አስተዳደር ውስጥ ከፌዴራል መንግስት ከፍተኛ ሹማምንት መካከል   የፌዴራል ፖሊስ ኮምሽነር ወርቅነህ ገበየሁ ፣  የትራንስፖርት ሚኒስትር ድሪባ ኩማ  ፣ የከተማ ልማት ፣ኮንስትራክሽንና ቤቶች
ሚኒስትር አቶ መኩሪያ ኃይሌ   ፣ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ባለቤትና የፓርላማ አባል  ወ/ሮ አዜብ መስፍን  እንደሚገኙበትታውቋል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ ፓርላማው በዛሬ፣ በነገ እና አርብ ውሎው የ2006 በጀት ላይ ተወያይቶ ጠ/ሚ ሃ/ማርያም ደሳለኝ በተገኙበት ያጸድቃል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን በተጨማሪም ወደ አዲስአበባ በምርጫ ስም እንዲዛወሩ በተደረጉት ሹማምንት ምትክ  እንዲሁም ለአዲሶቹ መ/ቤቶች ማለትም ለመረጃና ደህንነት መስሪያቤት ፣ ለፍትህ ሚኒስቴር እና ለአካባቢና ደን ሚኒስቴር አዳዲስ ሚኒስትሮችን ይሾማል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ተጨማሪ የስልጣን ሽግሽግ ሊኖር እንደሚችልም ይጠበቃል።
በመተካካት ስም የኦህዴድ ፓርቲ ስልጣናቸውን ያጡት አቶ ኩማ ደመቅሳ በአቶ ሃ/ማርያም ካቢኔ ውስጥ የሚኒስትርነት ቦታ ያገኛሉ የሚሉ ግምቶች አሉ።
ፎርቹን ጋዜጣ በእሁድ  ዘገባው እንደገለጸው በአለቃ ጸጋየ በርሄ ተይዞ የነበረውን በጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮ የጸጥታ ዘርፍ ሃላፊነቱን ስልጣን አቶ በረከት ስምኦን ይረከባሉ ተብሎ ይጠበቃል። አቶ በረከት ስልጣኑን ከተረከቡ ቦታው ለመጀመሪያ ጊዜ ከህወሀት ውጭ ባለ ሰው ይያዛል። የደህንነት ሹሙ ስልጣናቸውን አስረክበው ከህወሀት ውች ባለ ሰው ከተተኩ፣ እነ አቶ በረከት ሀይላቸውን ቀስ በቀስ እያጠናከሩ ነው በሚል ለሚሰጠው አስተያየት ትክክለኛነት ማረጋገጫ ሊሆን ይችላል በማለት አስተያየታቸውን የሚሰጡ ወገኖች እንዳሉ የአዲስ አበባው ዘጋቢ ከላከልን መረጃ ለመረዳት ይቻላል።

No comments:

Post a Comment