Tuesday 30 August 2016

የአዲስ አበባ ዝብ ለምን በአደባባይ ተቃውሞውን ማሰማት ልቻለም በኤልሳቤጥ ግርም ፣ ኖርዌይ

ህዝባዊ ተቃውሞው ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ በሁሉም አካባቢዎች ማለት ይቻላል የወያኔን አንባ ገነናዊ አገዛዝ ተገዳድሮታል። በተለይ  በኦሮሚያ አካባቢ የተቀጣጠለው ህዝባዊ አመፅ ወደ አማራ ክልል በመስፋፋቱ ህወሓትን መድረሻ አሳጥቶታል። የህወሓት ባለስልጣናትንና በሥሩ ካሉት ካድሬዎቻቸው ሳይቀር ከመቸውም በላይ እንቅልፍ ነስቷቸዋል። ስልጣናቸው አደጋ ውስጥ እንዳለ በሚገባ ተረድተዋል። ለዚህም ማሳያ የሚሆነን በዘረፋ የሰበሰቡትን ንብረት እንዲሁም ቤተሰቦቻቸውን ማሸሽ ጀምረዋል። እድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ልጆቻቸውን እንኳን ቀደም ብለው ወደ ኢሲያና አውሮፓ ልከው በትምህርት ስም የወደፊት ኑሯቸውን እንዲያደላድሉ ማድረጋቸው ሳይጠቅማቸው የቀረ አይመስለኝም። 
የወያኔ ሃርነት ትግራይ ነጻ አውጪ ቡድን ህዝባዊ ተቃውሞው መቆጣጠር ከሚችሉት አቅም በላይ ተጧጡፏል፤ ሽንፈትንና ውርደትን አከናንቧቸዋል። ለስልጣኔ መከታ ይሆናል ብሎ ለዘመናት ያቋቋመው የአግዓዚ ጦር ህዝባዊ ተቃውሞውን ማክሸፍ አለመቻሉ እጅግ  ፍራታቸውን እንዲጨምር አድርጎታል። ለ25 ዓመታት ሥልጣናቸው እንዲቀጥል ያደረገው የከፋፍለህ ግዛው ስልትም ዛሬ ላይ ውጤታማ ሊያደርጋቸው አልቻለም። ህዝብ ከወያኔ ሌላ ጠላት የለንም፤ በየትም አካባቢ በግፍ  በአደባባይ የሚፈሰው ደም የእኛም ደም ነው ብሎ ድምጹን ከፍ አድርጎ  ማሰማት ጀመረ። ይህ ለወያኔ ትልቅ መርዶ ነው። ሚኒስቴር ተብዬው አቶ ጌታቸው ረዳ “ ሁለት አካላት እሳት እና ጭድ የሆኑ እንዴት አንድ ሊሆኑ ቻሉ” ብለው የተናገሩት የኦሮሞና የአማራ ተጋድሎ ቅንጅት ከፈጠረ የስርዓቱ ማብቂያ ሰዓቱ መድረሱን በግልጽ እየነገሩን ነው። የ1997 ዓም የአንድነት የህዝብ መአበል ሊረሱት ፈጽሞ አይችሉምና ሃገራዊ የህዝብ ድምጽን ሲሰሙ ያቅለሸልሻቸዋል።      
በተለይ ከ1997 ብሄራዊ ምርጫ በኋላ ኢትዮጵያ የለውጥ ጎዳና ላይ መሆኗን በወያኔም ሆነ በተቃዋሚው በኩል ሲነገር መስማት አዲስ ነገር አይደለም። ሁለቱም በተረዱትና በእራሳቸው እውነታዊ ዓለም ተነስተው የሀገራችንን በለውጥ ጎዳና መጓዝ በግልጽ መናገራቸው ምንም ስህተት የለባቸውም። ምክንያቱም ከወያኔም እውነት ስለማንጠብቅ ከህዝብ ደግሞ ውሸት ስለማይጠበቅ ሁለቱም ትክክል ናቸው። ለምን ቢባል በወያኔ አነጋገር ኢትዮጵያ በለውጥ ጎዳና ላይ ናት ሲሉ ለስልጣናቸው መራዘም ያልፈነቀሉት ድንጋይ፣ ያልገነቡት አጥር ስለሌ ኢትዮጵያን በመከፋፈልና ህዝቧን ለከፋ ስቃይና መከራ በመዳረጋቸው ይህም የለውጥ አካል ነው፤ እንዲሁም ሰባዊ፣ ዲሞክራሲያዊና ተፈጥሮአዊ መብቶች ሙሉ በሙሉ ከህዝብ በወያኔ በመገፈፋቸው ሌላው ትልቁ ለውጥ ነው። አካባቢን መሰረት አድርጎ  ህዝብን በመያዝና አንድ ለ5 በቡድን ጠርንፎ የወያኔ ደጋፊ ለማድረግ የተሞከረው ሙከራም ቀላል የሃገሪቱ ለውጥ አይደለም።
ርዕስ ወደ አደረኩት የአዲስ አበባን ህዝብ የተቃውሞ ሁኔታ ስንመለከት አንዱና ትልቁ ጉዳይ ከ1997 ምርጫ በኋላ የተደረጉ ድርጊቶችን በአጽንኦት መመልከቱ እጅግ ጠቃሚ እንደሆነ ሊሰመርበት ይገባል። በመጀመርያ በእውነት የአዲስ አበባ ህዝብ ተቃውሞ እያሰማ ነው ወይስ አይደለም የሚለው መልስ የሚሻ ጥያቄ ይመስለኛል። እኔ እንደምገነዘበው ከሆነ የአዲስ አበባ ህዝብ የወያኔን ጥላቻ በተለያየ ጊዜና መንገድ በደንብ አሳይቷል ብዬ አስባለሁ፤ የሰላም እንቅልፍ የተኛበትን ወቅት ፈጽሞ አላስታውስም። ወያኔ ለሃገር እንደማይበጅና የማስተዳደር ብቃትም ሆነ አቅም እንደሌለው በ1997 በሚገባ ለዓለም አሳይቷል። ዛሬ ላይ በህብረት ወጥቶ ማሰማት ያልቻለበት የተለያዩ ምክንያቶች ቢኖሩትም ከወያኔ ጋር ግን አብሮ መቀጠል እንደማይፈልግ የተለየ ማስረጃ አያሻንም።
የአዲስ አበባ ህዝብ በወያኔ አንባ-ዘር ገነን አገዛዝ ልጆቹን በእስር፣ በስደትና በሞት የተነጠቀበትን አሰቃቂና ዘግናኝ  የቀን ከቀን ድርጊት ረስቶ ከወያኔ ጋር ህብረት ይኖረዋል ብሎ  የሚያስብ ሰው ይኖራል ብዬ በፍጹም አላስብም። በንግድ እንቅስቃሴውም ሆነ በህንፃ ግንባታው ወያኔዎች/ህወሓታዊያን ሙሉ በሙሉ የተቆጣጠሩበትን የማንአለብኝነት እኩይ ተግባር እንደ አዲስ አበባ ህዝብ ያየ ህብረተሰብም የለም። ለዚህ ደግሞ በሁሉም  ክፍለ ከተሞች፣ ወረዳዎችና ቀበሌ ነዋሪዎች ህያው ምስክሮች ናቸው። ምስኪኑ ህብረተሰብ በጠራራ ፀሃይ ካለተመጣጣኝ ካሳና ክፍያ ከቤት ወጥቶ  ሲወረወር በከተማ ልማት ስም አንዱ የህወሓት አሽከር ፎቅ ሲገነባ እንደ ማየት፣ ምስኪኑ ኗሪ የጀመረውን ግንባታና ንግድ አስቁሞ አንዱ የጠገበ የህወሓት አባል ትግሬ ነጥቆ  የራሱን ድርጅት ሲያቋቁም እንደማየት ሌላ ምን የሚዘገንን ነገር አለ።  
የአዲስ አበባ  ህዝብ በቤት እጦትና በኑሮ  ውድነት ከመቸውም በላይ የሚሰቃይ በህወሓት ዘመነ ግዛት ነው። በአፍሪካ  መዲና በሆነችው ዋና ከተማ እየኖረ መብራትና ውሃ በፈረቃ የሚጠቀም ምስኪን ህዝብ ቢኖር የአዲስ አበባ ህዝብ ነው። በሙስናው፣ በመልካም አስተዳደር እጦት በአጠቃላይ ጭቆናው፣ እንግልቱ፣ መከራውና ስቃዩ በአዲስ አበባ ህዝብ ይብሳል። ህወሓት ወያኔ በማነኛውም መልኩ ክንዱን አጠንክሮ ለመግዛት የሚሞክረው የአዲስ አበባ ህዝብ በነቂስ ከወጣ ለስልጣኔ“ጣ” ላልቶ ይነበብ አደጋ ነው ብሎ  በማሰብ እንደሆነ ጥርጥር የለዉም። እውነት ነው የአዲስ አበባ ህዝብ በአንድነት ከወጣ ወያኔን ከተቀመጠበት ቤተ መንግሥት አስወጥቶ ደደቢት በርሃ የማስገባት አቅም አለው።

በተለያዩ  አካባቢዎች ህዝባዊ አመጹ ሲቀጣጠል የአዲስ አበባ ህዝብ ለምን ዝምታን መረጠ????


በዚህ ዙርያ በርካታ ምንክንያቶች ቢኖሩም የተወሰኑ ነጥቦችን ማንሳት ተገቢ በመሆኑ በእኔ እይታ ምክንያት ናቸው ያልኳቸውን ነጥቦች እንደሚከተለው ላስቀምጥ፤ ቀሪውን እናንተ እንደምትጨምሩበት እርግጠኛ ነኝ። 
·         ህዝቡ ህብረብሄር ስለሆነ
ህዝቡ በወያኔ ስርዓት መቀጠል እንደማይፈልግ የአደባባይ ምስጢር ነው። ጥያቄው በምን እና እንዴት ባለ መልኩ ስርዓቱን ዳግም ላይመለስ ማስወገድ ይቻላል የሚለው ነው ህዝቡ ቆም ብሎ እንዲያስብ ያደረገው። አዲስ አበባ ከተለያዩ ቦታ፣ ባህል፣ ሃይማኖት፣ እውቀትና ፍላጎት የተወጣጣ ህብረተሰብ የሚኖርባት ከተማ እንደመሆኗ መጠን ህዝቡ አንድን ነገር ለመቃወምም ሆነ ለመደገፍ፣ ለመተቸትም ሆነ ለማሞገስ፣ ለመትከልም ሆነ ለመንቀል የሚያስብበት፣ የሚነጋገርበትና የሚወስንበት ጊዜ ያስፈልገዋል። ህብረብሄር መሆኑ ትልቅ ውበት ቢኖረውም በቀላሉ ደግሞ  በአንድ አጀንዳ እንደ አንድ አካባቢ ህዝብ መወሰንና ማጽደቅ ይቸገራል። ወያኔን ለመጣል ወይም ለማስወገድ ቢስማማም በምን መልኩ እናስወግደው በጦር ወይስ በጎራዴ፣ በሰላም ወይስ በሃይል፣ በምክር ወይስ በተግሳፅ በማለት ብዙ ሊከራከር ይችላል፤ ለምን ህዝቡ ህብረብሄር ስለሆነ አስተሳሰቡም በዚያው ልክ የየቅል ነውና። ስለዚህም በኦሮሚያ የተነሳውን ህዝባዊ አመፅ በልቡ ይዞ እያዘነ ነገር ግን በአደባባይ መቃወም እና ዛሬም በአማራ ክልል የተቀጣጠለውን ህዝባዊ እምቢተኝነት በተግባር መቀላቀል ያልቻለበት ምክንያት አስተሳሰቡና አመለካከቱ በተወሰነም ደረጃ ቢሆን ልዩነት ስላለው ነው። የአዲስ አበባን ህዝብ በነቂስ ለማስነሳት ህብረብሄራዊ/ሃገራዊ አጀንዳ ያስፈልገዋል። እንደ ግለሰብ ሁሉም ሰው ወያኔ ለአንድ ቀንም እድሜ እንዲኖረው አይፈልግም ነገር ግን በህብረት ወጥቶ  በቃን ለማለት ከአንዳንድ አካባቢ ከሚነሱ አጀንዳዎች በላይ ኢትዮጵያዊነት የተላበሰ አጀንዳ፣ ሃገራዊ ጉዳይ የሚዳስሱ ጥያቄዎች እና አንድነትን የሚሰብኩ ጉዳዮች እንዲነሱ ይፈልጋል፤ ለምን አዲስ አበባ የብሄር ብሄረሰቦች መቀመጫ ናትና።
·         ከወያኔ ለውጥ በኋላ ፍጹም ዲሞክራሲያዊ መንግስት ስለሚፈልግ
እርግጥ ነው ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ከዚህ አረመኔያዊ አገዛዝ ውድቀት በኋላ እውነተኛና ዘላቂ ሰላም ሊያሰፍንና ሊያረጋግጥ የሚችል ዲሞክራሲያዊ መንግሥት/ስርዓት ይፈልጋል። የኢትዮጵያ ህዝብ አንባ ገነናዊ ስርዓት ምን ያክል ለሃገር እንደማይጠቅም ከ 4 አስርት አመታት በላይ አይቶታል። የሚመጣው ስርዓት ፍጹም ኢትዮጵያዊነትን የተላበሰ፣ ክብሯንና ሰንደቅ ዓላማዋን ሊያስከብር የሚችል፣ ዳር ድንበሯን፣ ዜጎቿን፣ ንብረትና ታሪኳን ሊጠብቅ ሊያስጠብቅ የሚችል አካል መሆኑን ከለውጥ በፊት እርግጠኛ መሆንን ይፈልጋል። ከሁሉም በፊት የህዝብን መብት ሊያከብር የሚችል፣ የህዝብን ጥቅም ሊያስቀድም የሚችል፣ እወነተኛ ፍትህንና ነጻነትን ሊያጎናጽፍ  የሚችል ስርዓት ይናፍቃል። የማይከዳው፣ ቃሉን የሚጠብቅ፣ በህግና በስራት የሚመራ ፓርቲ ይሻል። እንደ 1997ቱ የቅንጅት መሪዎች ሳይጀመር ክፍፍልን መስማትም ማየትም አይፈልግም። ዛሬም እንደምናያቸው ከወያኔ የማይሻሉ አንዳንድ የተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች ስልጣንን ሙጭጭ ብለው አንለቅም የሚሉ ግለሰቦችን ወደ ሥልጣን ማንገስ የአዲስ አበባ ህዝብ በፍጹም አይፈልግም። እነዚህና መሰል ነገሮች ባይዙት ኑሮ የአዲስ አበባ ህዝብ በአንድነት ወጥቶ ለዓለም ህዝብ  በመስቀል አደባባይ በቃኝ ወያኔ በማለት ይገልጽ ነበር፤ በአግዓዚ ጦርና በመከላከያ ሰራዊት ብዛት ከቤት ባልተቀመጠም ነበር። ለወያኔም የሥልጣን ማብቂያው የአዲስ አበባ ህዝብ በቃኝ  “እምቢ አልገዛም” “ሞት ለወያኔ” “የስርዓት ለውጥ ያስፈልጋል” ብሎ በግልጽ ሲቃዎም ነው።  
·         ማህበራዊ ግንኙነቱ የላላ ስለሆነና ለሚስጢራዊ ውይይት አስቸጋሪ መሆኑ
ህወሓት ወያኔ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የአዲስ አበባን ህዝብ በከተማ ልማት ስምና በተለያዩ ምክንያቶች ከለመደው ቀየ እያፈናቀለ ወደ ማያውቀው አካባቢ በማዘዋወሩ ህብረተሰቡ እንደድሮው የጠነከረ ማህብራዊ ግንኙነት የለውም። ብዙ ጎረቤታሞች የማይተዋወቁ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ በመተማመን ላይ የተመሰረተ ውይይት ማድረግ ይቸግራቸዋል። ማን ምን እንደሆነም ለማዎቅ በጣም ከባድ ነው፤ ጆሮ ጠቢ ይሁን ጤነኛ፣ ባንዳ ይሁን ሰው፣ ተላላኪ ይሁን መልእክተኛ፣ ሰላይ ይሁን ተሰላይ መለየት አስቸጋሪ ነው። የጠነከረ ማህበራዊ ግንኙነት አይደለም ለሀገር ጉዳይ ለቤተሰብ ጉዳይም ትልቅ ፋይዳ አለው። ስለዚህ በማህበራዊ ግንኙነተ  መሳሳት የተነሳ ሰዎች እንደልባቸው እንዳይወያዩ  አድርጓቸዋል፤ ወያኔንም በነቂስ ወጥቶ እንዳይቃዎም አንዱ እንቅፋት የማህበራዊ ግንኙነት መዳከም ነው።
·         ወሓት ወያኔ በአዲስ አበባ ላይ ይበልጥ የበላይነቱን ስለያዘ
በዚህ ላይ ብዙ ነገር መናገር አስፈላጊ አይመስለኝም። ከቀበሌ እስከ ክፍለ ከተማ፣ በሚኔስተርም ሆነ መለስተኛ ስልጣን የህወሓት ነው። ለይምሰል ካልሆነ በቀር ምንም አይነት ስልጣን ለሌላ አካል ተላልፎ አይሰጥም። ከአንድ ሚኔስተር ለሌላ ብሄር ይልቅ አንድ ተራ የህወሓት ካድሬ በከተማዋ ብሎም በሃገር ጉዳይ ፈላጭ ቆራጭ ነው። አንድ ወያኔ መጥቶ  የፈለገውን ማድረግ ይችላል፤ በንግዱም፣ በትምህርቱም፣ በግብርናውም፣ በግንባታዉም መስክ እነርሱ ብቻ ተቆጣጥረውታል። መርካቶን የገብያ መዓከል ለአብነት ብንመለከት ነባር ነጋዴዎች ከጨዋታ ውጪ እየሆኑ ህውሓታዊያን ተቆጣጥረውታል። ስለዚህ አዲስ አበባን ወያኔ በፖለቲካውም ሆነ በኢኮኖሚው ዘርፍ ስለጠቆጣጠሩት በሁሉም ቦታ እነርሱ አሉ። ይህን ሰብሮ  ለመውጣት ህዝቡ የተቸገረ ይመስላል። ግን ለጊዜው ነው እንጂ የወያኔ  የበላይነት ህዝቡን ከተቃውሞ ሊያስቀረው አይችልም።  
·         የኑሮ ውድነቱ ፡ ከነጻነቱ ይልቅ ለእለት ዳቦ ፍለጋ መሮጥ
የኑሮ ውድነት በማህበራዊም ይሁን ፖለቲካዊ ዘርፍ ቀላል የሚባል ተጽኖ አያሳድርም። ሰው በልቶ ለማደር እንኳ እጅግ ከባድ የሆነባት ከተማ ሆናለች አዲስ አበባ። በውሸት ፕሮፓጋንዳ  11% እድገት አስመዝግባለች የምትባል ኢትዮጵያ በኢቢሲ/EBC ህዝቡን ከማሰልቸት   በስተቀር አንድም ጠብ ያለ ነገር የለም። ብዙዎች የእለት ዳቦ  እንኳ ለመብላት እጅግ አዳጋች ሆኖባቸዋል። ይህን ደግሞ  ያደረገው ህወሓት ሆን ብሎ  አንድም የአዲስ አበባን ህዝብ የ1997 ቁጭትና ንዴት ለመበቀል፤ አንድም ህዝቡ በችግር ሲጠበስ ለእለት ጉርሱ እንጂ ለመብትና ነጻነቱ ለመታገል አቅምም ጊዜም አይኖረውም ብሎ አስቦ ነው። በሌላ መልኩ ደግሞ  የእራሱ ሰዎች በሃብት የበለጸጉ ከሆኑ በሃብታቸው እንደፈለጉ ማድረግ የሚችሉ መስሎ ስለሚታያቸው ነው። ይህ ግን የሞኝነትና የቅዥት ህልም መሆኑን ገና ወያኔዎች የተረዱ አይመስልም። ዛሬም በቁም ቅዥት ይዋኛሉ። ሆኖም ግን ለጊዜው የአዲስ አበባን ህዝብ በአንድነት ለተቃውሞ እንዳይወጣ የኑሮ ውድነቱ በቂ ባይሆንም እንደምክንያት የሚናገሩ ጥቂቶች አይደሉም። ግን የኑሮ ውድነትም ይሁን ድህነት ህዝብን ከተቃውሞ አያግደውም።
·         ወጣቱ በአነስተኛና ጥቃቅን አደረጃጀት ስም ስለወደቀ
ህወሓት ወያኔ  በተለይ ከ1997 ዓም ወዲህ ማንኛውንም የህብረተሰብ ክፍል አፍኖ ለመያዝ፣ ለመደለል፣ በተለያዩ ማሰርያ መንገዶች ለማጥመድ ያልፈነቀለው ድንጋይ የለም። የወጣቶች ሊግ፣ የሴቶች ሊግ፣ ጥቃቅንና አነስተኛ ፣ አንድ ለአምስት፣ በአጋር ድርጅት ተብየዎች ብአዴን፣ ኦህዴድ፣ ደህዴን፣ ህወሓትበማለት ህብረተሰቡን ለመያዝ ሙከራ አድርጓል። ዘረኛውና አንባ ገነኑ ወያኔ የተሳካለት እስኪመስል ድረስ ብዙ አባላት እንዳሉት ሲናገር መስማት አዲስ ነገር አይደም።
ምንም ይሁን ምን በተለያየ መንገድ የተወሰኑ ወጣቶችን ሊባል በማይችል መልኩ ለማጥመድ ሞክሯል በተለይ በአዲስ አበባ። እነዚህ ወጣቶች ከልባቸው ወያኔን ደግፈው እንዳልሆነ እርግጠኛ ሆኖ  መናገር ይቻላል፤ ነገር ግን ጊዜያዊ የስጋ ምኞትን ለማሳካት፣ ለመብላት፣ ለመጠጣትና ሆዳቸውን ሞልተው ለማደር ሲሉ የወያኔ ተላላኪ ሆነዋል። ይህ ደግሞ ለሀገራቸው ቆርጠው የሚታገሉ ጀግና ወጣቶች ላይ የሞት ፍርድ መፍረድ ነው። በርካታ ወጣቶች በእስርና በእንግልት ለነጻነት የሚታገሉትን ለፍርፋሪና ለጥቅማጥቅም ብለው አሳልፈው ሰጧቸው። የትም ለማያደርስ ነገር በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተው የወያኔን ተልዕኮ  ፈጻሚ ሆነዋል በወጣትነት እድሜቸው። የአዲስ አበባ ወጣቶች ብቻ በአንድነት ቢወጡ ወያኔን ድራሹን ማጥፋት የሚችል አቅም ነበራቸው።
ወጣቶች ደግሞ  በቀላሉ እርስ በእርሳቸው መግባባት ይችላሉ። ለማህበራዊ መገናኛ ዜዴዎች እጅግ ቅርብ ስለሆኑ መረጃም ሆነ  ማስረጃ በቀላሉ ማግኘት ይችላሉ። ስለዚህ ወጣቶች ሆይ እራሳችሁን በመፈተሽ ነግ በነጻነት የምትኖርባትን ሀገር ገንባ። የአማራና የኦሮሚያ ወጣቶች እየሞቱ ያሉት ለነጻነት ነው። ከወንድሞችህ ጋር ቶሎ ብለህ ህዝባዊ አመጹን ተቀላቀል   
በአጠቃላይ የአዲስ አበባ ህዝብ የተለያዩ ምክንያቶችን ወደጎን በመተው ህዝባዊ አመጹን በአስቸኳይ መቀላቀል አለበት። በመጀመርያ አረመኔያዊ፣ ዘረኛና ጎጠኛ አንባገነን አገዛዝን ከስሩ ነቅሎ መጣልና ቀጣይ ሀገሪቱ ላይ ምን አይነት ስርዓት መምጣት አለበት ለሚለው ወሳኝ ጥያቄ የሁሉም አካባቢ ህዝብ የሚወስነው ጉዳይ ነው። የሽግርግር መንግስት መስርቶ  ሀገራችን ዘላቂ የሆነ ሰላም፣ ዲሞክራሲና ፍትህ የሰፈነባት እንድትሆን ማድረግ ይቻላል። ከዚያ በፊት ግን ወያኔን አሽቆንጥሮ መጣል ያስፈልጋል።  እንደ ሌሎች አካባቢዎች ወያኔ በቃ በማለት ክፍለ ከተሞችንና ቀበሌዎችን ከወያኔ ማጽዳት ለነግ የማይባል ተግባር ነው። በጎበዝ አለቃም ለማስተዳደር ወስኖ መነሳትም ሌላኛው አማራጭ ነው።
ህልም ተፈርቶ  ሳይተኛ አይታደርም እንዲሉ አግዓዚ፣ መከላከያ ሰራዊት፣ ወታደር፣ ፖሊስ ፈርተን ነጻነታችንን አጥተን መኖር የለብንም። የጀግና ሞት ሞተንም ቢሆን ለወገናችን ነጻነትን ለማውረስ ቆርጠን መነሳት ይገባል። ይህ ደግሞ  ለአዲስ አበባ ህዝብ ከባድ የሚሆን አይመስለኝም። የንግድ እንቅስቃሴውን ለአንድ ሳምንት ቢያቆም ወያኔን ሽባ አድርጎ ከጥቅም ውጭ ማድረግ ይችላል። አዲስ አበባ ለዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን እጅግ ቅርብ ስለሆነች የዓለምን ትኩረት በቀላሉ የመግዛት እድል ይኖረናል። ስለዚህ ሙሉ ኃይላችንን አጠናክረን ነጻነትን ለመቀዳጀት መነሳት ይኖርብናል፤ ለሌሎች ህዝባዊ አመጾችም ድጋፋችንን እናሳይ።
ስለሆነም ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል
Ø  የቤት ውስጥ አድማ
Ø  የንግድ እንቅስቃሴን ማቆም
Ø  የስልክ አገልግሎት ሙሉ በሙሉ ለተወሰነ ቀናት ማቆም
Ø  ምንም አይነት የትራንስፖርት አገልግሎት አለመስጠት፣ አለመጠቀም
Ø  በየክፍለ ከተማው ህዝባዊ አመጽ መጀመር እና የመሳሰሉ የትግል ስልቶችን ማድረግ በአስቸኳይ ከአዲስ አበባ ህዝብ ይጠበቃል።


ማንኛውንም አስተያየት በ “ ezewege@gmail.com ” ለመቀበል ዝግጁ ነኝ

No comments:

Post a Comment