Saturday 7 September 2013

አሳዛኝ የአውላቸው ሕይወት በአሜሪካ (ከኢየሩሳሌም አርአያ)

ሕይወት በአሜሪካ
አውላቸው ይባላል፤ ከአገር የወጣው በ21 አመት እድሜው ሲሆን፣ አሜሪካ መኖር ከጀመረ 41 አመት እንደሆነው ይናገራል። በ «bachelor of science in agriculture » ዲግሪውን አግኝቷል። በአትላንታ – ጆርጂያ ከአንዲት ጥቁር አሜሪካዊት ሁለት መንታ ሴት ልጆችን አፍርተዋል። የልጆቹ እድሜ 29 ሲሆን፣ አንዷ ልጁ ትዳር መስርታ ልጅ እንደወለደች ይናገራል። ትዳሩ ከፈረሰ በኋላ ልጆቹን አይቷቸው እንደማያውቅና ሳያያቸው 15 አመት ገደማ እንደሆነው በሃዘን ገለፀልኝ። ስለሁኔታው ሲናገር፥ « ለልጄ ስልክ ስደውልላት አግብታ መውለዷን ነገረችኝ። ከዛም እንዳልደውልባት ተናግራ በቁጣ ስልኩን ዘጋችብኝ፤….እባክህ ስለዚህ ጉዳይ ማንሳት አልፈልግም፤ ወላድ ይፍረደኝ! » አለኝ። አውላቸው እንደሚለው ለልጆቹ የከፈለው መስዋእትነት ከንቱ መቅረቱና ትዳሩን ማጣቱ ህይወቱን እንዳመሳቀለበት ይገልፃል። በዲሲ አብዛኛው ሃበሻ ያውቀዋል። ማዶ አሻግሮ አንድ ታዋቂ የሃበሻ ሬስቶራንት እያመለከተኝና የባለቤቱን ስም እየጠቀሰ፥ « እንዲህ እንደዛሬው ሕይወት ሳትቀየርብኝ በፊት፣ በነበረኝ ጊዜ ይህ ሰው የቅርብ ጓደኛዬ ነበር። ዛሬ ግን እንኳን ሰላምታ ሊሰጠኝ ይቅርና ሬስቶራንቱ እንዳልገባ ማቀብ አድርጎብኛል። አያሳዝንም!?..»የፌዝ ፈገግታ እያሳየ ጠየቀኝና በእጁ የያዘውን ቢራ ተጎነጨ። አውላቸው በዲሲ በሚገኙ ታዋቂ ራዲዮ ጣቢያዎች ቃለ መጠይቅ ተደርጎለታል። በቪኦኤ የአማርኛ ፕሮግራም ቀርቧል። …እርሱ ግን « በመጠጥ ውስጥ ተደብቄ ..የመጨረሻዋን ቀን እየጠበቅኩ ነው፤ ገባህ?… » አለኝ። … አውላቸውን ተሰናብቼው ዞር ስል ፀጉሩ የተንጨባረረ፣ የነተበና የተቀዳደደ ልብስ ቢጤ ጣል ያደረገ ሃበሻ ድምፁን ከፍ አድርጎ ሲለፈልፍ ተመለከትኩ።…አእምሮው እንደተነካ ያስታውቃል። …”አወይ ወገኖቼ..” አልኩ በውስጤ፤ እመለስበታለሁ።
( የ62 አመት አዛውንቱ አውላቸው ይኸውላችሁ)

No comments:

Post a Comment